ክፍል 8 - ቅዱስ አውጎስጢኖስና መናፍቃን
- Category: የቅዱስ አውጎስጢኖስ የሕይወት ታሪክ
- Published: Saturday, 12 September 2009 13:29
- Written by Super User
- Hits: 5724
- 12 Sep
ቅዱስ አውጎስጢኖስና መናፍቃን
በቅ. አውጎስጢኖስ ዘመን ቤተ ክርስቲያንን ያጎሳቀሉ ማኒ፣ ዶናቱስና ፔላጊዮስ የተባሉ ሦስት ዋነኛ የቤተ ክርስቲያን ጠላቶች የጠነሰሱትን ልማድና ትምህርት የሚከተሉ መናፍቃንና አላውያን (ሐሰተኞች) ነበሩ። እነዚህ በታሪክ ገነው የሚታወሱትን ለመጥቀስ ያህል ነው እንጂ ሌሎችም ሐሳውያን እንደነበሩ ይታወቃል። በዚህ ምክንያት በአንድ ስበካ ውስጥ ሦስትና አራት የሚሆኑ የተለያዩ እይታና ልማዶችን ይከተሉ የነበሩ አቡኖች ተነሥተው እውነተኛው የሐዋርያት ተተኪ እኔ ነኝ እኔ ነኝ በመባባል ሁከት ይፈጥሩ ነበር።
አውጎስጢኖስ ወደ ክርስትና ሲገባ ሐሰተኛ የሆነውን የማኒ ትምህርት መቃወም ጀመረ፤ በዚህም እምነት ውስጥ ዘጠኝ ዓመታት የዋኘበትና ጉድለቱንና ይዘቱን በሙሉ ያወቀው ስለነበር አንድ በአንድ ዕርቃኑን በማስቀረት በሕዝቡ ፊት የተጠላና ዋጋ ቢስ እንዲሆን አደረገው።
ይህ ከመልዕልተ ባሕርይና (መለኮታዊ ስጦታ) ከባህርያዊ ችሎታውም የመነጨ ብርቱ ተቃውሞው የማኒ ትምህርትን የሚከተሉ ሰዎችን አፍ አስያዛቸው ዕረፍትንም አሳጣቸው፤ እየተዳከሙ መሄድም ግድ ሆነባቸው።
ከዚህም ቀጥሎም በዚያን ዘመን በካርቴጅ ውስጥ ዶናቱስ የተባለ ሰው የተሳሳተ ትምህርትን ጀምሮ ነበር ፤ ዶናቲዝም (የዶናቱስ ትምህርተ) ወይም ልምድ ቤተክርስቲያን ነቀፋ ያለባቸውን ምእመን መቃወም አለባት፤ ነገስታትና አስተዳዳሪዎችም በቤተክርስቲያን ጉዳይ ውስጥ እጃቸውን ማስገባት የለባቸውም ይላል። እንደዚሁም በሃይማኖት ስደት ጊዜ እምነታቸውን የካዱ፣ ንዋይ ቅድሳትን አሳልፈው የሰጡ፣ የተቀደሰ ነገርን ከሚዳፈሩ ወገኖች ጋር የሚተባበሩ ምእመናን ሁሉ ባለፈ ድርጊታቸው ቢጸጸቱም ብርቱና አሰቃቂ ቅጣት መቀበል አለባቸው፤ እንደዚሁም በሕይወታቸው ትንሽም ቢሆን ጉድለት ያላቸው ኢፍጹማን ካህናትና የቤተክርስቲያን መሪዎች የሚፈጽሙት የቤተክርስቲያን ሥርዓትና ምስጢራት ሁሉ በአምላክ ፊት ዋጋና ፍሬ የለውም በሚል መሠረተ ሐሳብ የቆመ ነው። በዚያን ጊዜ አውጎስጢኖስ ሰይፍ ቃሉንና ስል ብዕሩን በዶናቲዝም ላይ እንዲያተኩር በማድረግ የሰው ልጅ በትምህርት በመረዳት እግዚአብሔርን እንዲያመልክ ማድረግ እንጂ በማስፈራራትና አሰቃቂነት ባለው ቅጣት ማስገደድ አይገባም……..ወዘተ በማለት በጥብቅ ተሟገተ።
እ.ኤ.አ በ411 ዓ.ም. በካርቴጅ ውስጥ በተደረገው ጉባኤ አውጎስጢኖስ ያለበት ወገን እውነተኛ ትምህርትና ዓላማን የተከተሉ 286 አቡኖች የዶናቱስ ደጋፊዎች ደግሞ 275 አቡኖች ለክርክር ቀረቡ። ከሦስት ቀን በኋላ የዶናቱስ ተከታዮች ብትንትናቸው ወጣ ተወገዙም፤ ትምህርታቸውን እንዳያስፋፉ በምድራዊ ንጉሡ በቄሣርም ታገዱ፤ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እያነሱ ሄደው እስከ 7ኛው ክፍለ ዘመን ድረስ አልፎ አልፎ በአንዳንድ ሀገሮች ውስጥ ለስም ያህል እንደነበሩ ቢነገርም ተዳክመው ቀርተዋል።
አውጉስጢኖስ ከተቃወማቸው መናፍቃን ውስጥ ሦስተኛ ቦታን የያዘው ፔላጊዮን በተባለ እ.ኤ.አ. በ370 ዓ.ም. በነበረ እንግሊዛዊ የሚመራ ቡድን ነው። ፔላጊዮስ ጽኑና ጥብቅ በሆነ የምንኩስና ሕይወት የታወቀ ሰው ነበር፤ በአውጎስጢኖስ ጊዜ በመጀመሪያ ከእንግሊዝ አገር ወደ ሮም ቀጥሎም ወደ ሂፖ(ሰሜን አሜሪካ) በመሄድ ትምህርቱን ዘረጋ።
የትምህርቱ መሠረተ ሐሳብ ወይም ጭበጥ እንበለው፤ “ሰው ከአዳም የወረሰው ኃጢአት ወይም ፍዳ የለውም፤ ነፍስ ወከፍ ሰው ከተፈጠረ ጀምሮ ክፉ ነገርን ለማድረግ ሙሉ ነጻነትና ችሎታ አለው። ስለዚህም የሰው ልጅ ያለ ኃጢአት ሊኖርና ፍጽምና ላይ ሊደርስበት ይችላል። የሚሰጠው ርዳታ የለም፤ አያስፈልገውምም፤ እንደዚሁም ሕጻናት የወረሱት ኃጢአት ስለሌላቸው መጠመቅ አያስፈልጋቸውም። በክርስቶስ ላይ ያለን እምነት ደግሞ እሱን እንደ አርአያነት እንድንጠቀምበት ይረዳናል እንጂ በሕገ ወንጌል ከእግዚአብሔር ጸጋና ድኅነትን በክርስቶስ እንድናገኝ አይደለም……የደኅንነታችን ምንጭ ራሳችን ነን።” የሚል ነው።
በዚህም ዓይነት መሠረታዊና ዋነኛ የሆኑትን አዕማደ ሃይማኖት መንጥሮ ለመጣልና የቤተክርስቲያንን ትምህርት ለማፋለስ የተነሣው ፒላጊያኒዝም ተወገዘ፤ አውጎስጢኖስና ሌሎችም አበው በሚያስደንቅ ጀግንነትና ብርቱ ጥንካሬ ተቃወሙት። በ431 ዓ.ም ደግሞ በኤፌሶን ጉባኤ ፔላጊያኒዝም በይፋ ተወገዘ፤ አውጎስጢኖስ በፔላጊዮስ ላይ ባደረገው ክርክር ብዕሩ እየሾለ ጽሁፉም እየሰፋ ስለሄደ ያኔ ስለ ጸጋና ስለኃጢአት ስለ ደኅንነትም የጻፋቸው ድርሳናት ከቅዱሳት መጻሕፍት ለጥቆ የበለጠ የነገረ መለኮት (የቲዎሎጊያ) ዋና ምንጭ ሆነው እስከ ዛሬ ድረስ ሊቃውንትና የቴዎሎጊያ ተማሪዎች እውነተኛ እውቀትን የሚቀዱባቸው ምንጮች ናቸው።