የእግዚአብሔርን መንገድ አዘጋጁ

የእግዚአብሔርን መንገድ አዘጋጁ

ብዙ ዘመናት አስቀድሞ ኢሳያስ መሢሕ መድኃኒት ከመምጣቱ በፊት መልእክተኛ እንደሚመጣ ትንቢት ተናግሮ ነበር፡፡ ትንቢቱ እንዲፈጸም ክርስቶስ ያ ደኀንነት ከመጀመሩ በፊት የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ አባት ዘካርያስ  በትንቢት ተናግሮ እንደነበር እግዚአብሔር ለእስራኤል ልጆች ኢየሱስን መድኃኒታቸውን እንደቀበሉ ሰበከላቸው፡፡  የእግዚአብሔር መንግስት ቀርቦአልና ስንሐ ግቡ እያለ በበረሃ የሚጮህ የአዋጅ ቃል ለእግዚአብሔር የሚሆን መንገድ አዘጋጁ፣ መንገዶቹ አቅኑ፣ ጉድጓዶች ይሞሉ፣ ተራራና ኮረብታ ሁሉ ዝቅ ይበል፣ ዳገትና ቁልቁለቱ ሜዳ ይሁን፣ ወጣገባው መሬት ይደልደል፣ የእግዚአብሔር ክብር ሊገለጥ ነውና፡፡John_the_Baptist

ከእግዚአብሔር የሚመጣ ሁሉ በነፍስ ወከፍ ደኅንነት ያገኛል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር ተናግሮአል በማለት የኢሳይያስን ትንቢት እየጠቀሰ ለአይሁዳውያን የኢየሱስን መምጣት አስታወቃቸው፡፡ ሊያድናችሁ ከሰማይ የሚመጣውን መሢሕ በልባቸው አምነው እንዲቀበሉ መከራቸው፡፡ ከዓመት ዓመት ከዘመን ዘመን ቤተክርስቲያን ለእኛም የእግዚአብሔርን መንገድ አሰናዱ ጥረጉ የሚለውን የመጥምቁ ዮሐንስን አዋጅ አድጋሚ ትነግረናለች፡፡ እንዴት አድርገን ነው የምናዘጋጀው? ቅዱስ ዮሐንስ “ንስሐ ግቡ” እንዳለን ንስሐ ገብተን የእግዚአብሔርን መንገድ እናዘጋጅ፡፡

ሕፃኑ ኢየሱስ ወደ እኛ የሚመጣበትን መንገድ ልናዘጋጅ እርሱ የሚጠላውን የሚከለክለውን የኃጢአትን መንገድ ትተን የሚወደውንና ተደስቶ ወደ እኛ እንደመጣ የሚያደርገውን የጽድቅ መንገድ እንድንይዘ ያስፈልገናል፡፡ ወደ እኛ እንዳይመጣ የሚከለክል የኃጢአት ተራራ ጥል፣ ቅንዓት፣ ሁከት፣ ዝሙት፣ ቂም በንስሐ መደምሰስ አለብን፡፡ በውስጣችን የሚገኝ የመንፈስ ቅዝቃዜ የመንፈሳዊነት ጉድለት በጸሎት በተጋድሎ በበጐ ሥራ በትሕትና በፍቅር በየዋሕነት በምሕረት በትዕግስት በሃይማኖት በእምነት እንድንሞላው ያስፈልገናል፡፡ ጠመዝማዛ አሰተሳሰብና አረማመድ እንዲቀና ንግግራችንና ሥራችን የታረመ እንዲሆን ሕይወታችን በሙሉ ከእግዚአብሔር ፈቃድ ጋር እንዲስማማ አድርገን መዘጋጀት አለብን፡፡

እንደዚህ ያለ መንገድ ከጠረግን ሕፃን ኢየሱስ ተደስቶ ወደ እኛ በመምጣት ወደ ልባችን ይገባል፡፡ መለኮታዊውን ሕፃን በመንፈስ ንጹሐን ሆነን ተዘጋጅተን ከአገኘነው በኋላ በመንፈስ እንደገና እንደምንወለድ የልደቱን ጸጋ ያድለናል፡፡

ልደት ለነፍሳችን እንጂ ሥጋችንን እንዲጠቅም የተዘጋጀ አይደለም፡፡  ልደት በሥጋ የምንደሰትበት የምንጠጣበት የምንለብስበት በነፍስ ግን ተርበን ተጠምተን በጸጋ ራቁታችን የምንወጣበት የምንውልበትና ነፍሳችን የምትጐዳበት የምታዝንበት ቀን  ሊሆን አይገባም፡፡ ልደት የነፍስ በዓል ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ቀን ነፍሳችን በጸጋና በመንፈሳዊ ደስታ መሞላት አለበት፡፡ ይህን እንድናገኝ ደግሞ አስቀድመን በሚገባ ልንዘጋጅ ያስፈልጋል፡፡


ምንጭ፡- መንፈሳዊ ማሳሰቢያ

እህት እሌኒ ይሁኔ - ኦረሶላይን እህቶች- አዲስ አበባ