የእግዚአብሔር መንግሥት
- Category: የተለያዩ አስተንትኖዎችና አስተምህሮዎች
- Published: Wednesday, 08 December 2010 22:16
- Written by Super User
- Hits: 3851
- 08 Dec
የእግዚአብሔር መንግሥት
ኢየሱስ ብዙ ጊዜ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት (አልፎ አልፎ መንግሥተ ሰማይ ብሎ ይጠራዋል) ይናገራል፡፡ ይህ መንግሥተ ሰማይ የሚለውን ሐረግ ምንአልባት ከሞት በኋላ አንድ ቀን እግዚአብሔርን ፊት ለፊት እንደምናየው ተስፋ የምናደርግበት ሕይወት ይመስለን ይሆናል፡፡ ነገር ግን ኢየሱስ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ወይም ስለ መንግሥተ ሰማይ ሲናገር ከሞት በኋላ (ከዚህ ምድራዊ ሕይወት በኋላ) ስላለው ሕይወት ብቻ አያመለክትም፡፡
የእግዚአብሔር መንግሥት የምድር ላይ ሕይወታችንን መመዘን የሚችል እውነታ ነው፡፡ የእግዚአብሔር መንግሥት ማለት እግዚአብሔር እኛንና ሁሉንም ተፈጥሮ የሚያስተዳድርበት የሕይወት ሁናቴ ነው፡፡ እግዚአብሔር በአንተ ላይ ለማድረግ የፈለገውን መፈፀም ከቻለ ማለትም ከአንተ ምንም ዓይነት መከላከል ካልገጠመው አንተ በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ አለህ(ትኖራለህ) ማለት ነው፡፡ በጌታ ፀሎት (አቡነ ዘበሰማያት) “መንግሥትህ ትምጣ” ቀጥለን ደግሞ “ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነ እንዲሁም በምድር ይሁን” በማለት እንፀልያለን፡፡ የእግዚአብሔር ፈቃድ በሰማይ በምልአት እና በነፃነት እንደሆነ ሁሉ በእኛ ውስጥም ልክ እንደዚያው ሲሆን የእግዚአብሔር መንግሥትም ይመጣል፡፡
የእግዚአብሔር መንግሥት እንዲመጣ መጸለይ ማለት “አምላክ ሆይ! ንጉሴና ጌታዬ ሁን መጥተህም ግዛኝ፡፡” እንደማለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር እመቤታችን ቅድሥት ድንግል ማርያም እንዳለችው “እነሆ!እኔ የጌታ አገልጋይ ነኝ አንተ እንዳልክ ይሁንልኝ፡፡” (ሉቃስ 1፡38) ማለት ነው፡፡
እግዚአብሔር ሁለንተናችንን እንዲያስተዳድር ከመናፈቅና በሁኔታዎች ያልተወሰነ እሺታን ለእርሱ ከመስጠት የላቀ ምንም ነገር የለም፡፡
ዲያቆን ተሻለ ንማኒ - ሲታዊ - ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ አ.አ.
(source:- This is the day the Lord has made. by Wilfrid Stinissen Nov. 25)