እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

የኢየሱስ ሕማማት

ኢየሩሳሌም በጠላቷ ተሸንፋ ስትወድቅ ኤርሚያስ በጣም አዝኖ በመንገድ ላይ ቁጭ ብሎ “እናንተ በመንገድ የምታልፉ ሁሉ… ሐዘኔን የሚመስል ሐዘን እንዳለ አስተውሉ” ሰቆ. ኤር. 1፡12 እያለ አምርሮ ያለቅስ ነበር፡፡

ቤተክርስቲያን በዚህ አጋጣሚ ይህንን የኤርምያስ ቃል እየጠቀሰች የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሐዘን፣ ስቃይና ሞት እንድናስብ ትጠራናለች፡፡ ቃሏን ሰምተን ወደ ኢየሱስ ሕማማት እንሂድ፡፡ ቅዱሳን  እንደሚሉት ከሁሉ የበለጠ የሐሳብ ጸሎትና ለመንፈሳችንም ጠቃሚው ልምምደ የኢየሱስን ሕማማት ማስተንተን ነው፡፡ “ከሁሉ የበለጠ ለደኅንነታችን የሚጠቅመንና ብዙ የሚረዳን ነገር የአምላክ ልጅ ስለ እኛ የተሰቃየውን ማሰብ ነው” ይላል ቅዱስ አጉስጢኖስ፡፡ “የሕሊናችንን ቁስል ለማከምና ነፍሳችንን ለማንጻት ከኢየሱስ ቁስሎችና ስቃይ ሞትን ከማሰብ የሚበልጥ የለም” በማለት ቅዱስ በርናርዶስም ይናገራል፡፡ ቅዱስ ቦናቨንቱራ ደግሞ “የኢየሱስን ሕይወት የተቀደሰ ሕማማቱን የሚያስብ የፈለገውን ያገኛል” ይላል፡፡ ኢየሱስ ራሱ ደግሞ ለቅድስት ዠልትሩድ “መስቀሌን በመንፈሳዊነት የሚመለከቱን እኔ በምሕረት ዓይኔ እመለከታቸዋለሁ” አላት፡፡ በእነዚህ መንፈሳዊ ምክሮች ተነሣሥተን ለእኛ ብሎ ተሰቃይቶ የሞተውን አምላክ ለማስታወስና ለመውደድ ትጉሆች እንሁን፡፡

በመንገድ የምታልፍ ሁሉ ሐዘኔን የሚመስል ሌላ ሐዘን እንዳለ አስቲ አስተውል፡፡ አዎ ኢየሩሳሌም ብዙ ግፍ ቀምሳ ተሰቃየች፡፡ ግን ይህ ሁሉ ኢየሱስ ከቀመሰው በእርሱ ላይ ከደረሰው ግፍና ስቃይ ሊወዳደር ሊስተካከል ፈጽሞ አይችልም፡፡ ቅዱሳንና ቴዎሎጂያውያን እንደሚያስተምሩን ኢየሱስ በሕማማቱ ጊዜ የተቀበለው ውርደት፣ ስቃይ፣ ሐዘን ታይቶና ተሰምቶ የማይታወቅ፣ ሰው በልዩ ጸጋ እንጂ በኃይሉ ሊሸከመው  የማይችል ነው፡፡ ይህ ስቃይ ለኢየሱስ ሰው እንደ መሆን መጠን ተሰማው፡፡ “አምላኬ ሆይ! አምላኬ ሆይ! ለምን ተውኸኝ?” ማቴ. 27፡47 እስከሚል ድረስ ተሰቃየ፡፡ “ባየነው ጊዜ እንወድደው ዘንድ ደም ግባት የለውም፡፡ የተጣለ ከሰውም የተናቀ፣ መከራ የደረሰበት የተዋረደ ሰው ነው… መከራችንን ተሸክሞ ስለ እኛ ተሰቃይቶ አይተናል፡፡ በኃጢአታችን ቆስሎ፣ ተሰቃይቶ ሰላማችን በእርሱ ሆነ፣ ይህን ሁሉ መከራ እግዚአብሔር ስለ ኃጢአታችን ብሎ ሰጠው፡፡ ከእግሩ እስከ ራሱ ድረስ የቆሰለ አካሉ ለምን” ይላል ኢሳ. 53፡3

የኢየሱስ ሕይወቱ ሙሉ ስቃይና መስቀል ነበር፡፡ ሲወለድ በስቃይ መሃል ተወለደ በስቃይ መሃል አደገ፣ ሲሞትም ሊነገር በማይችል ስቃይ ሞተ፡፡ “እኛ ሞት የማይገባው ሞትን ስቃይ የማይገባው ስቃይን በፈቃዱና በአባቱ ፈቃድ ነፍሱን ለሞት አሳልፎ እንደሰጠው እንናገራለን፡፡ የአምላክን ልጅ ይዘው አሠሩት፣ ወስደው ፍርድ ፊት አቆሙት፣ እንደ በደለኛ ከሰሱት፣ ሊያላግጡበት ብለው ሰገዱለት፣ በጥፊም መቱት፣ በሁለት ወንጀለኞችም መካከል ሰቀሉት” ይላል ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፡፡ ይህ ሁሉ ውርደት በፈጣሪ ላይ ወረደ፡፡ ይህ ሁሉ ስቃይ የሁሉ የነገሥታት ንጉሥ በሆነው በአምላክ ልጅ ላይ ወረደ፡፡ ፈጣሪ በፍጡሮች ተዋረደ፡፡ ይሁዳ አሳልፎ ሰጠው፣ አይሁዳውያን አሰቃዩት፣ ጲላጦስ ሞት ፈረደበት፣ ወታደሮቹ ገረፋት፣ በመስቀል ላይ ሰቀሉት፣ መንገደኛ ሁሉ ሰደበው፣ አላገጠበት፣ በክፉታችን ሰበብ ተሰቃየ፣ እኛን ከአባቱ ጋር ሊያስታርቅ ይህን ሁሉ መከራ ተቀበለ፡፡

ምንጭ:- መንፈሳዊ ማሳሰቢያ

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት