እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

የምሕረት በር ተከፍቷል

የምሕረት በር ተከፍቷል
Mercyበካቶሊክ ቤተክርስቲያን ከአስራ አምስተኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ የቅዱስ ጴጥሮስ ካቴድራል ታላቁን በር የመክፈት ልምድ አለ፡፡ ይህ ታላቁ የካቴድራሉ በር የተቀደሰ የምሕረት በር ነው፡፡ በዚህ በር የመከፈት ምሳሌነት ትልቁ የእግዚአብሔርን ምሕረት እናስታውሳለን፡፡ በተከፈተው በር ውስጥ አልፈው ወደ ካቴድራሉ መቅደስ የሚገቡ ሁሉ ከቀድሞው የኃጢአት ማንነታቸው ወደ ጸጋ ይገባሉ፤ በሩ ከኃጢአት ወደ ጽድቅ የሚያሻግረው የእግዚአብሄር ምሕረት ምሳሌ ነው፡፡
በሩ ትክክለኛ ትርጉሙን የሚያገኘው ምዕመናን በሩን ከክርስቶስ ማንነት ጋር አዋህደው ሲገነዘቡ ነው፡፡ በሩ ኢየሱስ ነው! ር.ሊ.ጳ. ፍራንቺስኮስ እንደሚያስተምሩን ከእግዚአብሔር ጋር በሕይወት ወደ መኖር የሚያደርሰን በሰፊው የተከፈተ አንድ እውነተኛ በር አለ፤ እርሱም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እርሱ አንዱ እና ፍጹም የሆነው የመዳን መንገድ ነው፡፡ የመዝሙረኛው ቃላት በፍጹም ትክክለኛነት የሚገልጡት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ኢየሱስ ክርሰቶስ ጻድቃን የሚገቡበት የእግዚአብሔር በር ነው (መዝ 118፡20)፡፡
ጌታችን ስለራሱ ሲናገር “በሩ እኔ ነኝ” (ዮሐ 10፡7) ይላል ፡፡ ስለዚህ በዚህ በር በኩል ካልሆነ በስተቀር ማንም ወደ አብ የሚደርስ የለም፡፡ ምክንያቱም ዓለምን ለማዳን የተላከ የእግዚአብሔር የፍጸሜ ቃል እርሱ ነው፡፡ በሰፊው የሚከፈተው በር በመስቀል ላይ ሳለ በአይሁድ ጦር የተከፈተው የቅዱስ ልቡ ምሳሌ ነው፡፡
በዚህ ዓመት ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱሱን በር የከፈቱት በጽንሰተ ማርያም ክብረ በዓል ዕለት ህዳር 28 ቀን 2008 ዓ.ም. ነው፡፡ በዚህ ዕለት የተከፈተው በር ለሁሉም የሰው ልጆች የተሰጠ የጸጋ ስጦታ ነው፤ በበሩ በኩል ወደ ውስጥ የሚዘልቅ ሰው ሁሉ የእግዚአብሔርን ፍቅር ይቀምሳል ፣ ፍቅሩ የሚያጽናና፣ ምሕረት የሚያደርግ፣ በተስፋ የሚሞላ ፍቅር ነው፡፡ በዓለም ዙርያ የሁሉም ካቴድራሎች ምሕረት በሮች በዚህ በምሕረት ዓመት ይከፈታሉ፡፡
እኛም ሁላችን በተከፈተው በር እንግባ ፤ ከኃጢአት ወደ ጸጋ፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን፣ የኋላውን ትተን የፊቱን ክብር ለመውረስ እንጓዝ፡፡ በዚህ በር በኩል ሰፊውን የእግዚአብሔር ምሕረት እንካፈል፤ በዚህ በር በኩል ስንገባ እኛ ከእግዚአብሔር ምሕረት የምንለምን ሁሉ የእኛን ምሕረት ፈልገው ይቅርታ እንድናደርግላቸው ለሚጠይቁን ሁሉ እና በድለውን ይቅርታ መጠየቅ ለከበዳቸው ሁሉ ምሕረት እናድርግ ፡፡ እግዚአብሔር አባታችን እያንዳዳችንን ይቅር እንደሚለን እናምናለን፤ ነገር ግን ይህ የበለጠ ፍጹም የሚሆነው እኛም ደግሞ ለበደሉን ሁሉ ምንም ነገር ሳንጠብቅ ከልብ ምሕረት ስናደርግ ነው፡፡ የቤተክርስቲያን ህይወት ምሕረትን የማወጅ፣ ምሕረትን የመቀበል እና የመስጠት ህይወት ነው፡፡ የቤተክርስቲያን ጥሪ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ምሕረት በህዝቡ መካከል መግለጥ እና መኖር ነው፡፡
ምሕረት ቤተክርስቲያን የሕልውና መሰረት ነው፡፡ ሐዋርያዊ ሥራዎቿ በሙሉ የክርስቶስን ርህራሄ የሚያንጸባርቁ መሆን አለባቸው፡፡ ምሕረት ያልተሞላበት አገልግሎት የትኛውንም ያህል ስኬታማ ቢሆን ክርስቲያናዊ አልግሎት ነው ሊባል አይችልም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ምሕረትን ለሰው ልጆች ለመግለጥ ማለቂያ የሌለው ጥማት አላት ፡፡ ለሕይወታችን ፍትህ እንዲኖር የምንታገለውን ያህል ምሕረት እንዲኖር መታገል አለብን፡፡
ምሕረት የሌለበት ሕይወት ፍሬ አልባ እና ተስፋ ቢስ ሕይወት ነው፡፡ ዓለም እርስ በእርሱ ለበቀል በተነሳበት እና የምሕረት ለዛ በጠፋበት በዚህ ወቅት እናት ቤተክርስቲያን ልጆቿን ሁሉ ትጠራለች፤ ቤተክርስቲያን ለሰው ልጆች ሁሉ የይቅርታ እና የምሕህረት ጥሪዋን የምታሰማበት የተወደደው ሰዓት ደርሷል፡፡ አሁን ምሕረት የሚሰበክበት የወንድሞቻችን እና የእህቶቻችንን ደካማ ጎኖች ከክርስቶስ መስቀል ጋር አስተባብረን የምንሸከምበት ጊዜ ነው፡፡ ምሕረት የአዲስ የሕይወት መንገድ ጀማሮ ነው፤ የወደፊቱን በታመነ ተስፋ የምንጠባበቅበት ኃይል ነው፡፡
ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔር ምሕረት አምባሳደር ነች፡፡ የወንጌልን የልብ ትርታ በሰው ልጆች ልብ እና አዕምሮ ውስጥ ማሰማት ጥሪዋ ነው፡፡ የክርስቶስ ሙሽራ እንደመሆኗ መጠን ሙሽራውን ተከትላ ያለልዩነት ሁሉንም የሰው ልጆች ለመቀበል መውጣት አለባት፡፡ ቤተክርስቲያን አዲሱን ስብከተ ወንጌል በጀመረችበት በዚህ ወቅት የእግዚአብሔር ምሕረት በቃል እና በተግባር ያለማቋረጥ መስበክ አለበት፡፡ መልእክቷ የታመነ ይሆን ዘንድ አስቀድማ እርሷ እራሷ ምሕረትን በተግባር በመኖር ቀዳሚ ምስክር መሆን አለባት ፡፡ ቋንቋዋ እና ድርጊቷ ሁሉ የእግዚአብሔር ምሕረት ነጸብራቅ መሆን አለበት በዚህ ዓይነት ሰዎች ወደ እግዚአብሔር ዕቅፍ የሚመለሱበት መንገድ ያገኛሉ፡፡ የቤተክርስቲያን የመጀመሪያ እውነት የክርስቶስ ፍቅር ሕያውነት ነው፡፡ ቤተክርስቲያን የዚህ ፍቅር ባለ ዐደራ አገልጋይ ነች፡፡ ይህ ፍቅር ምሕረት የሚያደርግ እና ራሱን ለሌሎች አሳልፎ የሚሰጥ ፍቅር ነው፡፡ ስለዚህ ቤተክርስያን ባለችበት ቦታ ሁሉ የእግዚአብሔር አብ ምሕረት በተግባር መገለጥ አለበት፡፡ በቁምስናዎቻችን፣ በተቋሞቻችን፣ በየማህበሮቻችን እና እንቅስቃሴዎቻችን ውስጥ ሁሉ፣ ወይም በአንድ ሐሳብ ለመጠቅለል፣ ክርስቲያኖች ባሉበት ሥፍራ ሁሉ የምሕረት መዓዛ መኖር አለበት፡፡
ር.ሊ.ጳ ፍራንቺስኮስ
ትርጉም በወጣት ሳምሶን ደቦጭ ቅ. ዮሴፍ ቁምስና ዘሲታውያን አ.አ.

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት