እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

መላእክት ምንድን ናችው?

መላእክት

the annunciation Webመላእክት በመጽሐፍ ቅዱስ እና በታሪክ ውስጥ ታላቅ ሚና አላቸው። ብሉይ ኪዳን ብዙ ጊዜ ስለመላእክት ይጠቅሳል። አዲስ ኪዳንም መላእክት በክርስቲያናዊ ሕይወት ውስጥ ያላችውን ስፍራ ይጠቁመናል። ኢየሱስም በወንጌል ውስጥ ከመላእክት ጋር ግንኙነት እንዳለው ይናገራል።

ስለዚህ መላእክት ምንድን ናችው?

በካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ትምህርተ ክርስቲያን ቁጥር 329 ውስጥ እንደተጠቀሰው ቅዱስ አውጉስጢኖስ እንዲህ ይላል “መላእክት የሚለው ቃል ተግባራችውን የሚያስረዳ ነው። ተፈጥሮአቸው ግን መንፈስ ነው። ስራችው መላእክት ያስብላቸዋል በተፈጥሮአችው ደግሞ መንፈሳውያን ናቸው። መላእክት የእግዚአብሔር አገልጋዮች እና መልክተኞች ናቸው። መላእክቶች መንፈሳውያን ፍጥረታት እንደመሆናቸው መጠን ማስተዋል (intelligence) እና ፈቃድ (will) አላቸው። መላእክት የማይሞቱ መንፈሳውያን ፍጥረታት ናቸው። እንደ ቤተ ክርስቲያን አስተምሕሮ መላእክት እግዚአብሔርን ለማገልገል የተፈጠሩ መንፈሳውያን ፍጥረታት ናቸው። እነዚህ መላእክት በሰው መልክ ተገልጠው ከሰው ልጆች ጋር ሊገናኙ ይችላሉ።

የመላእክት ፋይዳ ምንድን ነው?

የመላእክት ተግባር እግዚአብሔርን ማገልገል፣ እርሱን ማመስገን፣ እርሱን መወደስ፣ ለክብሩ አምልኮና ስግደት ማቅረብ ነው (ኢሳ 6:3 ፤ ራዕይ 4:8) ። እግዚአብሔርን ከማገልገል ጎን ለጎን እኛን ይጠብቁናል፣ ይጸልዩልናል፣ በመንፈሳዊ ጉዟችን ይመሩናል፣ ያበረታቱናልም። በካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ትምህርተ ክርስቲያን ቁጥር 336 ላይ እንደተገለጸው " ከልደት እስከ ሞት ድረስ የሰው ሕይወት በመላእክት ጥበቃ እና አማላጅነት የታጠረ ነው። ጠባቂ መልአክ ከእያንዳንዳችን ጎን ሆኖ እንደ ብርቱ ጠባቂ እና እረኛ ወደ በጎ ነገር እና ወደ ሕይወት ይመራናል" ። እያንዳንዳችን በእግዚአብሔር ቸርነት ለጠባቂ መላእክት ስለተሰጠን ጠባቂ መላእክቶቻችን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እስከ ዕለተ ሞታችን ድረስ ከክፉ ነገር ሁሉ ይጠብቁናል።

መላእክት ከጠባቂነታቸው ባሻገር በሰማያት ከሚገኙት ቅዱሳን ጋር በአንድ ድምጽ ሆነው ”ቅዱስ፤ቅዱስ፤ቅዱስ” እያሉ በእግዚአብሔር ፊት ስለእኛ ይማልዳሉ (ይጸልዩልናል) (ጦቢት 12:12 ፤ ራዕይ 5:8 እና 8:3)። ይህም ስለሆነ ኢየሱስ ‘’ከእነዚህ ከታናናሾቹ አንዱንም እንዳትንቁ ተጠንቀቁ፤ መላእክቶቻቸው በሰማያት ዘወትር በሰማያት ያለውን የአባቴን ፊት ያያሉ እላችኋለሁ” (ማቴ 18፤10) እያለ ስለመላእክት ተግባር በግልጽ ይናገራል።

መላእክት ልዩ ልዩ አገልግሎትና ተግባራት አሏቸው። መጽሐፍ ቅዱስ በልዩ ልዩ ስፍራዎች የገለጠውን ተከትለው የነገረ መለኮት ሊቃውንት እንደሚያስተምሩን በሰማያዊ ሥልጣናቸው ቅደም ተከተል መሰረት ዘጠኝ ነገደ መላእክት አሉ። እነዚህም ፩. ሡራፌል፤ ፪. ኪሩቤል፤ ፫. መናብርት፤ ፬. ገዢዎች ፤ ፭. ኃይላት ፤ ፮. ሥልጣናት ፯. አለቆች (ሠራዊት)፤ ፰. ሊቃነ መላእክት፤ ፱. መላእክት ናቸው።

ሡራፌል፤ ኪሩቤል፤ መናብርት እግዚአብሔርን በጥበቡ፤ በፍርዱ እና በዙፋኑ ክብር የሚወድሱት፤ የሚሰግዱለትና የሚያመልኩት ናቸው።.

ገዢዎች፤ ኃይላትና፤ ሥልጣናት ደግሞ ባጠቃላይ የተፈጥሮን ኃይላት ሁሉ የሚያስተዳድሩ ናቸው።

አለቆች (ሠራዊት) አህጉራትንና ከተሞችን የሚጠብቁ ናቸው።

ሊቃነ መላእክት የተመረጡ ሰዎች ጠባቂዎች ሲሆኑ ከእነዚህ መካከል ሶስት ሊቃነ መላእክት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በስማቸው ተጠቅሰው እናገኛለን፤ እነዚህም ሚካኤል፤ ገብርኤል እና ሩፋኤል ናቸው ( ጦቢት12:15፤ ዳን 12:1፤ ዳን 8፡16፤ ዳን 9፡21 )

መላእክት ደግሞ ለሁላችን የተሰጡ ጠባቂዎችና መልክተኞች ናቸው። ከዚህ በታች የቀረቡትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች በማንበብ ስለ መላእክት ያለንን ግንዛቤ እንድናሳድግ እና በመንፈሳዊ ሕይወታችን የእነርሱን ረድኤትና ትሩፋት አግኝተን እንድንበለጽግ እግዚአብሔር ጸጋውን ይሰጠን ዘንድ በሊቀ መልአኩ በቅዱስ ገብርኤል አማላጅነት እንለምናለን!!!.

መልካም በዓል!!!

ዘፍ 19:1-17፤ መዝ 91፤ ዕብ 1:1-14፤ ዕብ13:1-2፤ ሉቃ 22:,39-43

ወጣት ሳምሶን ደቦጭ ከጀርመን

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት