እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

ዋጋችን ስንት ነው?

ዋጋችን ስንት ነው?

Holy Cross 2015 ecበሕይወታችን ውስጥ የምንገለገልባቸው ቁሳዊ ነገሮች አብዛኞቹ በዋጋ የሚተመኑ ናቸው፤ ምናልባትም የሁሉን ዋጋ ባናውቅም እንደየዝንባሌያችን የተወሰኑ ነገሮችን ዋጋዎች እናውቃለን፤ በተመሳሳይ መልኩም እንደየዋጋቸው ክብደት ወይም ርካሽነት ነገሮችን ጥንቃቄ እንሰጣቸዋለን ወይም እንነፍጋቸዋለን። እንዲሁም ያለ እነርሱ መኖር እንደማንችል የምናውቃቸው ነገር ግን ደግሞ የዋጋ ተመን የሌላቸው እንዲሁ በነጻ የምንጠቀምባቸው አምላክ በቸርነቱ የሰጠንም ነገሮች አሉ፤ ዋጋ እንተምንላቸው ብንል አቅመ ቢስ የሚያደርጉን እውነታዎች! ለምሳሌም አየር፣ የፀሐይ ብርሃን፣ ወንዝ፣ ባህር… ወዘተ።

ከላይ ከጠቀስናቸው ነገሮች ደግሞ እልፍ ስንል አንዳንዴ በዋጋም ማሰቡ ሞኝነት የሚያስመስል፤ በተቃራኒው ደግሞ ዋጋውንም ያለማሰቡ በተመሳሳይ ደረጃ ሞኝነት የሚያስመስል እውነታ አለ፤ ሰው። አንዳንድ ሰው ቢገዛም ባይገዛም ራሱን እስኪያዞረው የሚያስፈልጉትንም የማያስፈልጉትንም የቁሳቁሶች ዋጋ መጠየቅ ይጠናወተዋል፤ ብዙ ሰው ደግሞ ሰው የመሆኑን ዋጋ ሳይጠይቅ እድሜውን ሊኖር ይችላል፤ ዋጋውን ካላወቀ ተገቢውን ክብርና ጥንቃቄ ሊነፍገው የሚችል “ሰው” ነት እንዳለውም ሊዘነጋ ይችላል።

ታዲያ የሰው ዋጋው ስንት ነው? እስቲ ረጋ ብለን በማሰብ ዋጋችን ስንት ወይም ምን ሊሆን ይችላል ብለን እናስብ። አንዳንዴ አንዳንድ ሰው ምንም ዋጋ የሌለው፣ እንደው ዝም ብሎ የሚተነፍስ፣ የሚንቀሳቀስ፣ የሚኖር ይመስለው ይሆናል፤እናም ዋጋህን ገምት ሲባል ከግኡዛዊነት ያልዘለለ ቦታን በመያዝ ብቻ መለያቸው ከሆነ ከማዕድን (ከድንጋይ፣ ከብረት…)፣ ወይም ዝም ብሎ ባለበት የማደግና የመተንፈስ መገለጫ ከአትክልትና (ከእፅዋት) እንዲሁም በደመ ነፍስ ከወዲህ ወዲያ መንቀሳቀስ ከሚችሉት ከእንስሳትም ያነሰ ዋጋ ያለው ሊመስለው ይችላል። አንዳንዴም ሰውና ሁኔታዎች ባዶ እንደሆንን፣ ዋጋ እንደሌለን፣ የሆነ ሰው ሲከዳን፣ ዝቅ ሲያደርገን ራስችንን ባዶ አድርጎ የማሰብ ፈተና ሊገጥመን ይችላል።

በርግጥ ለሰው ለራሱ ዋጋውን መተመን ከባድ ነው፤ በትክክል የሰውን ዋጋ የሚተምነው ፈጥሮታልና ፈጣሪው ብቻ ነው፤ ሰውም የሚጠበቅበት የወጣለትን ዋጋ ማወቅና ክብሩን መጠበቅ ነው። ወደ እምነታችን ስንመጣ ይህንን የተራ ገበያ ቋንቋ ዋጋ ብለን የተጠቀምንበትን ሀሳብ “ቤዛ” በሚል ቃል መጠቀም እንችላለን። ቤዛ ስንል ሰው በኃጢአት ከጸጋ ወደ ኃጢአት ሕይወት በመውደቁ ፍጹም ሰው የሆነልን አምላክ ለእኛ በመሞት ካሣን የከፈለበት እውነታ ነው። ስለዚህም ክርስቲያን እንደመሆናችን ዋጋ ያልወጣበት ማንነት የለንም፤ ተከፍሎብናል፣ ተክፍሎልናል፤ ቅዱስ ጳውሎስ “በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም” (1ቆሮ 6:20) ይለናል።  

መስቀልን ማክበር የእኛን ዋጋ ማክበር ነው፤ የተገዛንበትን ያለመዘንጋት ነው፤ “ከአባቶቻችሁ ከወረሳችሁት ከከንቱ ኑሮአችሁ በሚያልፍ ነገር በብር ወይም በወርቅ ሳይሆን፥ ነውርና እድፍ እንደ ሌለው እንደ በግ ደም በክቡር የክርስቶስ ደም እንደ ተዋጃችሁ ታውቃላችሁ።” (1ጴጥ 1:19) እንደ ሰው ከሕይወት ተራ ወጥተን ኑሮ ትርጉም ሊያጣብን የሚችለው በውስጣችን ትርጉም ስናጣ ነው፤ መኖራችን ወፍ ዘራሻዊ ሲመስለን ያለመኖራችንም አይደንቀንም። የማንነት ንጽጽራችንን፣ መርሳት የሌለብንን ስንረሳ ሕይወት ለዛ ቢስ ትሆናለች፤ ስለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ “የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው?” ይለናል (ገላ 3:1)።

የአንድ ሰው ነፍስ ከዓለም ሁሉ የበለጠ ዋጋ አላት፤ የያንዳዳችን ነፍስ ዋጋዋ ከክርስቶስ ዘንድ ነው። “ሰው ዓለምን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል? ሰውስ ስለ ነፍሱ ቤዛ ምን ይሰጣል?” (ማር 8:36-37)። ነፍሳችን ነፍስ ተላልፎ የተሰጠላት ናት! “አባት ሆይ፥ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ አለ። ይህንም ብሎ ነፍሱን ሰጠ።” (ሉቃስ 23:46)።

ስለዚህም በነገሮች መካከል፣ በሕይወት ውጣ ውረድ ውስጥ ሆነን  የክርስቶስን መስቀል ስናይ ደስታችን፣ እውነተኛ ነጻነታችን፣ ምስጋናችንና ሰላማችንን እናገኝለን፤ ሁሉ ነገራችን በመስቀል ላይ “ተፈጸመ”፤ እኛ እንከፍል ዘንድ አንበቃምና እሱ በመስቀል ላይ የእኛን ዋጋ ከፈለ፤ “ተፈጸመ አለ፥ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ።” (ዮሐ 19:30)። አዎን! ዋጋችን፣ ቤዛችን ክርስቶስ ነው!

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት