መሆን የሚገባን ክርስቲያናዊ ሕይወት

መሆን የሚገባን ክርስቲያናዊ ሕይወት

የክርስትና መሠረት የሆነው የልዑል እግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ በክርስትና ሕይወታችን ልንመራበትና ልንፈጽመው  የሚገባንን መልካም ነገር ሁሉ አስተምሮናል፤ አሳይቶናልም፡፡ ለእኛ መምጣቱ፣ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መወለዱ፣ ሁሉ ተሟልቶ እያለው ምንም እንደሌለው እንደ ምስኪን ድሃ ሆኖ በከብቶች በረት መወለዱ፤ ቀስ በቀስ በሕጻናት መጠን ማደጉ ለእናቱና ለወገኖቹ መታዘዙ፣ ከአይሁዳውያን የደረሰበትን መከራ መቀበሉ፣ መንገላታቱ በመጨረሻም ማንም የማያደርገውን ፍቅር በመስቀል ላይ መግለጹ እና ስለ ኃጢያታችን ቤዛ መሆኑ ለእኛ ያለውን ጥልቅ ፍቅር ያሳያል፡፡ ይህን ሁሉ በመገንዘብ እኛ ክርስቲያኖች እርሱን መከተልና ከእርሱም መማር እንዳለብን ፈልጐ “ከእኔ ተማሩ፤ እኔ የዋህ በልቤም ትሁት ነኝና” ብሏል /ማቴ. 11፡ 28-29/

አያሌ ፈተናና ችግር ባለበት በዚህ ዓለም ስንኖር ልናሸንፍ የምንችለው የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስ ቃል ስንፈጽም እና ስንመራበት ብቻ ነው፡፡ በዚህ ዓለም እየኖርን ደግሞ ለምን ፈተና መጣብን ማለት አንችልም፡፡ ይህንን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ ነግሮናል፡- “በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፡፡ ነገር ግን አይዟችሁ እኔ ዓለምን አሸንፌዋአለሁ” ብሏል  /ዮሐንስ 16፡33/፡፡ ስለዚህ መፍትሔው የእርሱን ኃይል መሻት ብቻ ነው፡፡ ደግሞም “ክርስቲያን” እንደመባላችን መጠን “ክርስቲያናዊ ሕይወት” ሊኖረን የግድ ነው፡፡

በመሠረቱ ሰው ወደዚህ ዓለም ሲመጣ በከንቱ ለከንቱመ አልመጣም፤ በራሱ ምኞትና ፈቃድም አልመጣም፤ ሁሉን በፈጠረ በእበግዚአብሔር ፈጣሪነት የተፈጠረ እንደሚሆኑ የተፈጠረበት ትልቅና ቅዱስ የሆነ ዓላማ  አለው፤ በዚህም መሠረት ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡ ክርስቲያን በተፈጠረበት ዓላማ መጽናት፣ የተፈጠረበትንም ግዴታ መሥራትና መወጣት ተገቢ ነው፡፡ ይህንንም ለመፈጸም አስቀድሞ የግዴታዎችን ስምና የአሠራሩን ስልት ለይቶ ማወቅና መረዳት ደግሞ በግድ ይኖርበታል፡፡ ከዚህ በኋላ ግን እንደዚያው መሄድ፣ በዚያም መጽናት፣ መፈፈምም ግዴታው ይሆናል፡፡ በመጀመሪያ ሰው ከሌላው ፍጥረት የተለየ ክቡር ፍጥረት እንደመሆኑ በበለጠ ስለ እግዚአብሔር የማወቅ፣ የመናገርም ኃይልም ያለው ስለሆነ ከሁሉም በተለይም ስለ እግዚአብሔር ፈቃድ ደህና አድርጐ ማወቅ፣ ያንንም መጠበቅና አምልኮን በየጊዜው ማቅረብ አለበት፡፡ ሁለተኛ እግዚአብሔር አምላክ ፈጣሪ እንደ  መሆኑ በፍጥረቱ ሁሉ ይመሰገን ዘንድ ይገባል፤ ሰው የመናገር ችሎታም ያለው እንደመሆኑ ደግሞ ከሁሉ የበለጠ ምሥጋና ለፈጣሪው ማቅረብ፣ መኖሩንም መመስከር፣ ቸርነቱን መናገር ግዴታው ይሆናል፡፡

 

የሰው የተፈጥሮ ግዴታው ሦስት መልክ ያለው ይሆናል፡-

1ኛ.  ስለ እግዚአብሔር ክብር የሚያደርገውና የሚፈጽመው ግዴታ / ዘዳ. 6፡ 4-5/

2ኛ.  ሰው ስለራሱ የሚያደርገውና የሚፈጽመው ግዴታ /ዮሐንስ 3፡3-6፤47/

3ኛ.  ሰው ለመሰሉ ለሰው ወይም ለባልንጀራው ሊያደርገው ሊፈጽመው የሚገባው ግዴታ ነው /ዮሐንስ 15፡12/

ክርስቲያን በዚህ ዓለም እስከኖረ ድረስ በነዚህ ግዴታዎች የተያዘ የታሰረም ነው፡፡ ከሦስቱም ግዴታዎች አንደኛው እንኳን ቢጓደል ያስፈርድበታል፤ ሌላውም እንደተሟላ አያስቆጥርም፡፡ በመጀመሪያ እግዚአብሔር አምላክ ሰው እንዲሠራው የሚፈቅደውም የሚያዘውም ግዴታ አለው /ሉቃስ 1ዐ፡29/ እንዲሁም የሚከለክለው የሚጠላውም አለ፡፡ ይህን ሰው ሁሉ ደግና በጎ አድርጐ ለይቶ አውቆ የሚሠራውን በትክክል መሥራትና ወዲያውም መፈጸም ግዴታው ነው፡፡ ሁለተኛ ሰው ይርቃቸው ይከለክላቸውም ዘንድ የታዘዙ ሕግጋትም ሆኖ የወጡ አሉ /ዘፀ. 2ዐ፡1-17/ እነዚያንም ደግሞ ፈጽሞ መሸሽ እና መራቅ ግዴታ ነው፡፡ ስለዚህም ነው የግብረገብ ሕግጋት “ሥሩና አትሥሩ” በሚል በሁለት መልክ የተከፈለው፡፡ እንግዲያውም “ሥሩ” የተባለው አንድ ክርስቲያን በምንም መልክ ሊያስቀረው ወይም ሊተወው አይችልም ደግሞም አይገባውም የአምላክ ትዕዛዝ ስለሆነ በግድ መፈጸም አለበት፡፡ በዚህም አንጻር “አትንካ አትሥራ” የተባለውን በምንም መልክ መንካትም መሥራትም ቀርቶ ማሰብም ተገቢ አይደለም እንደ ትዕዛዙ መፈጸም እንጂ፡፡ ይህ ካልሆነ ግን በደልን እንደፈጸመው እንደ አባታችን እንደ አዳም የሞት ፍርድ ይጠብቀዋል ማለት ነው / ዘፍ. 3፡19/

በሥነ ምግባራትም ውስጥ የጽድቅ ሥራዎች ወይም ለጽድቅ የሚያበቃ ተግባሮች ሲኖሩ የኃጢአትም ሥራዎች ወይንም ወደ ኃጢአትና ወደ ሞት የሚያደርስ የኃጢያት ስልቶች ብዙዎች አሉ፡፡ እንግዲህ እውነተኛው ክርስቲያን የጽድቅ መሣሪያ፣ የጽድቅ ሠራተኛ፣ የትሩፋቱም አበጋዝ ሆኖ መገኘት አለበት እንጂ ከሞት በክርስቶስ ደም ኪዳን በኋላ እንደና ወደ ዘለዓለማዊ ሞት የሚሔድ ሆኖ መገኘት የለበትም፡፡ እንደና ለእርሱ የሚደረግ የደኅንነት መሥዕዋት የለም፡፡ የዕብራውያን መጽሐፍ ጸሐፊ ሲናገር፡- “ከእምነት መንገድ የወጡትን ሰዎችወደ ንስሐ መመለስ እንዴት ይቻላል እነዚህ ሰዎች እኮ ከዚህ በፊት ብርሃን በርቶላቸው ነበር ሰማያዊውንም ስጦታ ቀምሰው ነበር የመንፈስ ቅዱስም ተካፋዮች ሆነው ነበር፣ የእግዚአብሔርን መልካም ቃልና የሚመጣውን ዓለም ኃይል ቀምሰው ነበር፣ ከዚህ ሁሉ በኋላ ከመንገድ ከወጡ እነርሱን ወደ ንስሐ መመለስ አይቻልም፣ ምክንያቱም እነርሱ የእግዚአብሔርን ልጅ እንደገና ይሰቅሉታል፣ ያዋርዱታልም” ስለዚህ በሥነ ምግባር ሕይወትን ማጌጥ፤ ሥነ ምግባራትን በየመልኩ የመሥራትና የመፈጸም ግዴታ ለሰው ሁሉ ተገቢ ሲሆን በተለይ ክርስቲያኑ ወገን በክርስቶስ ደም የተዋጀ ክርስቶስንም የሚከተል በክርስቶስም የሚያምን ስለሆነ እንደስሙ ወይም እንደመምህሩ የግብረ ገብ ፈጻሚ ሆኖ መገኘት ለሌለውም ምሳሌነትን መስጠት አለበት፡፡ /ምንጭ ከአባ መልከ ጸዴቅ “ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር” አዲስ አበባ 1983 ዓ.ም ገጽ 5-6/

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያዘዘንም ይህን  “ሰዎች መልካም ሥራችሁን አይተው የሰማይ አባታችሁን እንዲያመሰግኑ የእናንተም ብርሃን በሰው ፊት ይብራ” ብሏል /ማቴ 5፡16/፡፡ በዚሁ የጌታችን ቃል መሠረት ሕይወታችን በቃሉ መመራት አለበት፡፡ የክርስቶስ ህይወትም በመምሰል ክርስቲያናዊ መሆን አለበት፡፡ ሕይወታችን ክርስቲያናዊ መሆን አለበት ስንል የሥነ ምግባር ፈጻሚዎች መሆን አለብን ማለታችን ነው፡፡ የሥነ ምግባር ባለቤቶች ከሆንን ደግሞ በምንኖርበት አካባቢና ህብረተሰብ ዘንድ ከበሬታን፣ በሥራችን ዕድገትን፣ በአለቆቻችን ዘንድ መታመንን እና ከሁሉ በላይ ደግሞ ከእግዚአብሔር ዘንድ ክብርንና ሞገስን እናጐናጽፋለን፡፡ ስለዚህ መንፈሳዊና የሥነ ምበግባር ፈጻሚ መሆን ጠቀሜታው የጐላ ነው፡፡ መልካም የምንሰራ ሌላ ጊዜ ደግሞ የሚለቸን ሊሆን በፍጹም አይገባም፡፡ ምክንያቱም መንፈሳዊ ሕይወት ወደ እግዚአብሔር የሚደረግ ቋሚ ጉዞን መጨረሻ ወደ ሌለው ሕይወት ቀጣይ እድገት ስለሆነ ነው፡፡ በሕይወት ጉዞአችን አንዳንዶችን ወይም የተወሰኑ ደረጃዎች ብቻ ወጥተን መምንተወው እንዳልሆነ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ይመክራል፡- “በገዛ ራሱ ክብር በቸርነቱም የጠራንን በማወቃችን ምክንያት ለሕይወትና ለእውነተኛ መንፈሳዊነት የሚያስፈልጉንን ነገሮች ሁሉ በመለኮታዊ ሀይሉ ሰጥቶናል፡፡ በእነዚህ በተሰጡት ነገሮች አማካይነት በክፉ ምኞት ምክንያት በዓለም ላይ ካለው የሞራል ውድቀት አምልጣችሁ የመለኮታዊ ባሕሪ ተካፋዮች እንድትሆኑ ክቡርና እጅግ ታላቅ የሆነውን ተስፋ ተጥቶናል፡፡ በዚህ ምክንያት የሚከተሉት ነገሮች እንዲጨመሩላችሁ ትጉ፡- በእምነት ላይ ደግነትን፣ በደግነት ላይ እውቀትን፣ በእውቀት ላይ ራስ መቆጣጠርን፣ በራስ መቆጣጠር ላይ በትእግስት መጽናትን፣ በትእግስት መጽናት ላይ መንፈሳዊነትን፣ በመንፈሳዊነት ላይ ወንድማማችነትን፣ በወንድማማችነት ላይ ፍቅርን ጨምሩ፡፡

እነዚህ ነገሮች በብዛት ቢኖሩአችሁ ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ወደ ማወቅ ትደርሳላችሁ ሥራ ፈቶችና ፍሬ ሲሶችም አትሆኑም ” /2ጴጥ1፡3-8/ ይህንን የሐዋርያው ጴጥሮስ መመሪያ በጥልቀት ስንመለከት ክርስቲያን /ማንኛውም የእግዚአብሔር ፍጡር የሆነ ሰው/ በዚህ ዓለም እያለ የሚሰራው አንድ ጥሩ ነገር ብቻ ሊያኮራው እንደማይገባ፤ ይልቁንም በአንዱ ላይ ሌላኛውን በዚያም ላይ ቀጣዩን የሕይወት መመሪያ እና መሰላል ቀስ ብሎ እንዲወጣ የሚያስገነዝብ ነው፡፡ በአንድ ጊዜ ወደ ፍጹምነት አይወጣመ ወይም በአንድ ጊዜ ወደ ፍጹምነት አይወጣም፡፡ ወይም በአንድ ጊዜ ፍጹም ካልሆንኩ በብሎ እንዚህ ሁሉ ቅዱሳት ማዕረጋት አይዘለሉም ቀስ እያልን እንወጣባቸዋለን፡፡ በሕይወታችን እንመራባቸዋለን ከብዙ ጊዜ ጽናት በኋላ ክብርንና ጸጋን እንጐናጸፍባቸዋለን /ምንጭ፡ ከአምሳሉ ተፈራ “ሥነ ምግባር ለማን?” አዲስ አበባ 2ዐዐ1፣ ገጽ 35-38/፡፡ በተሰጠችን ምድር ስንኖር ለሚያጋጥመን ውጣ ውረድና የሕይወት ትርምስ ማስተካከያ መንገዷ በክርስትና ሕይወት መጽናት ብቻ ነው፡፡ ክርስትና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍቃድና የፍቅሩ መገለጫ ስለሆነ በእርሱ ስንመራ የእግዚአብሔርን ፍቅር እንረዳረን የፈጣሪያችንን ፍቅር ከተረዳን ደግሞ ለኃጢአት አንገዛም፣ ለኃጢአት ካልተገዛን በጽድቅና በእውነት ዓለምን እናሸንፋለን፡፡ ዓለምን የሚያሸንፈውም በክርስቶስ ያለን እምነታችን ነው /1ዮሐ. 5፡5/፡፡ ዳሩ ግን እኛ ክርስቲያኖች በዓለም ስንኖር እግዚአብሔርን እንድናምን ብቻ አልጠራንም፣ ስለስሙ መከራንም እንድንቀበል ጭምር እንጅ /ፊል. 1፡29/

መከራን መቀበል ማለትም እንደየሰው የእምነት ደረጃ እና እንደሁኔታው ብዙ አይነት ፍች አለው፡፡ በጥቅሉ ስለ እምነታችን ማንኛውንም መስዋዕትነት መቀበል ማለት ነው፡፡ ይህም በየእለቱ የሚያጋጥሙንን ስጋዊና መንፈሳዊ ውጊያዎች በድል ስንወጣ እናረጋግጣለን /ራእይ 3፡21/

ክቡር አባ ኃይለ ገብርኤል መላቈ ዘማኅበረ ካፑቺን በፍቅርና ሰላም የመስከረም እትም እንደጻፉት