መሳጭ የቅዱስ ቁርባን ታሪኮች - ክፍል - ፩

መሳጭ የቅዱስ ቁርባን ታሪኮች

ቅዱስ ቁርባናዊ ሴቶችና ቅ.ቁርባን በሶቪየት ኅብረት የአፈና ዘመን

(Dominus Est ከሚል በረዳት ጳጳስ አታናሲየስ ሽኔይደር መጽሐፍ የተወሰደ)

Eucharistic Womenከ1917-1990 ዓ.ም. ድረስ የቆየው የሶቪየት ኅብረት ኮሚኒስታዊ አገዛዝ በምድር ላይ ገነትን መመሥረት የሚመስል ሃሳብ ነበረው። ሆኖም ግን ይህ አገዛዝ በውሸት ላይ፣ በሰብአዊ ክብር ጥሰት፣ እግዚአብሔርንና ቤተ ክርስቲያኑን በመካድና ብሎም በመጥላት ላይ የተመሠረተ ነበርና ብዙም ሊዘልቅ አልቻለም። በዚህ አገዛዝ ሥር ምንም ዓይነት መንፈሳዊ እሴቶች ቦታ ሊኖራቸው አይችልም፣ አልቻለምም ነበር። ሰውን ስለ እግዚአብሔር ህላዌ፣ ስለ ክርስቶስ፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን የሚያስታውሱ ነገሮች ሁሉ ከሕዝቡ ሕይወት እንዲጠፋና ከሰዎች እይታ እንዲርቅ ተደርጎ ነበር። ቢሆንም ግን ሰዎችን ስለ እግዚአብሔር መኖር የሚያስታውስ እውነታ ነበር፤ ይህም የካህን መኖር ነበር። ሰዎች ካህንን ሲያዩ የእግዚአብሔርን ህላዌ ሊያስታውሱ ግድ ነበርና እግዚአብሔር የሚለውን ሃሳብ ከሰዎች ለመፋቅ ካህንም ለሰዎች መታየት የለበትም፣ ከመኖር መወገድ አለበት።

የክርስቶስና የቤተ ክርስቲያን አሳዳጆች በውስጣቸው ካህን ብቻ እግዚአብሔርን ለሰዎች መስጠት እንደሚችል፣ ክርስቶስን በቀጥታና በተጨባጭ መልኩ ማለትም በቅዱስ ቁርባን ለሰዎች መስጠቱን ስለሚያውቁ ካህንን ከሁሉ የበለጠ አደገኛ ሰው አድርገው ይቆጥሩት ነበር። በዚህ ምክንያት መሥዋዕተ ቅዳሴን መቀደስ ክልክል ነበር። ይህ ሁሉ ቢደረግም ቅሉ፣ በቤተ ክርስቲያን በተለይም ደግሞ በምሥጢራት በኩል በሥራ ላይ የነበረውን መለኮታዊ ኃይል ማንኛውም ዓይነት የሰው ኃይል ሊያስቀረው አልቻለም።

በነዚያ ጨለማ ዓመታት በሰፊው የሶቪየት ኅብረት ግዛት ቤተ ክርስቲያን በድብቅ ውስጥ ውስጡን መኖርን ተገድዳ ነበር፤ ምንም እንኳ ሊታዩ የሚችሉ ገሃዳዊ መዋቅርና ሕንጻዎች ባይኖሯትም፣ እጅግ ከፍተኛ የሆነ የአገልጋይ ካህናት ቁጥር እጥረት ቢኖርም ወሳኝ ነገሩ ግን ቤ/ያን ሕያው ነበረች፣ እንደውም እጅጉን ሕያው ነበረች። ቤ/ያን እንዲህ ሕያው የሆነችው ቅዱስ ቅርባንን በቋሚነት አላጣችም ነበር፤ ምንም እንኳ ምእመናን ብዙ ጊዜ የመቁረብ እድል ባይኖራቸውም በምሥጢረ ቅዱስ ቁርባን ላይ የተደላደለ እምነት ያላቸውን ምእመናን ቤ/ያን አላጣችም ነበር፤ ባብዛኛው እናቶችና አያቶች የነበሩ በክህነታዊ እምነት ነፍሳቸው የታነጸች ቅ. ቀርባንን ከጥቃትና ከመጥፋት የሚከላከሉ እንዲሁም ላቅ ባለ ፍቅር፣ ክብርና በሚቻላቸው ሁሉ ተገቢውን ጥንቃቄ በማድረግ፤ በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን የክርስቲያኖች መንፈስ የተሞሉና «በፍቅርና በፍርሃት» ቅዱስ ቁርባንን ለሌሎች የሚያድሉ አማኝ ሴቶችን ቤ/ያን አላጣችም ነበር።

በጊዜው በሶቪየት ኅብረት ድብቋ ቤ/ያን ውስጥ ከነበሩት ብዙ ተምሳሌውያት ሴትች ቅዱስ ቁርባናዊ ሴቶች መካከል የሦስቱን ሕይወት እናያለን። እነርሱም ማሪያ ሽኔይደር፣ ፑልኬሪያ ኮችና ማሪያ ስታንግ ይባላሉ።

ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ የስታሊን አገዛዝ ብዙ ጀርመናውያንን ለጉልበት ሥራ በማለት ጥቁር ባሕር ከሚባለው አካባቢ ወደ ቮልጋ ወንዝ አጋዛቸው። ከከተማ በተገለለና በደኸየ ኑሮም ይገቡ ዘንድ ተገደዱ፤ በነዚህም ውስጥ በጥቂት ሺህ የሚቆጠሩ ካቶሊካውያን ነበሩ። አንዳንድ ካህናት የራሳቸውን ሕይወት በሚያሰጋ ሁኔታ ውስጥም አስገብተው ቢሆንም እንኳ በድብቃዊ ሁኔታ ለነዚህ ጀርመናውያን ካቶሊኮች ምሥጢራትን በማደል ያገለግሉ ነበር። በዚህ ሁኔታ አዘውትረው ይመጡ ከነበሩት ካህናት መካከል እ.ኤ.አ. በጥቅምት 1963 ዓ.ም.  ካራጋንዳ በሚባል አካባቢ አቅራቢያ በሰማዕትነት ያረፉት ዩክሬናዊው ካህን አባ አሌክሲጅ ሳሪትስኪ ይገኙበታል፤ እኚሁ ካህን እ.ኤ.አ. በ2001 ዓ.ም. በቅ. ዮሐንስ ጳውሎስ ዳግማዊ ብፅእናቸው ታውጇል።

እኚህን ሰማዕት ካህን በዚያ ሁኔታ ውስጥ እየመጡ ያገለግሏቸው የነበሩ ክርስቲያኖች ይወዷቸው ነበር እናም «የእግዚአብሔር ወሮበላ» ብለውም ይጠሯቸው ነበር። እ.ኤ.አ. ጥር 1958 ዓ.ም. በስደት ከሚኖሩበት አካባቢ በድንገት ተደብቀው ካዛክስታን ውስጥ ወዳለችው ወደ ካራጋንዳ ከተማ መጡ። አባ አሌክሲጅ በተቻለ መጠን ብዙ ምእመናን ይቆርቡ ዘንድ ያለምግብና ያለእንቅልፍ ቀን ከሌሊት ያናዝዙ ነበር፤ ምእመናኖቹም «አባ፣ መብላትና መጠጣት አለበዎት» ሲሏቸው የእርሳቸው መልስ «አልችልም፣ ምክንያቱም ፖሊሶች በየትኛውም ሰዓት ሊመጡ ይችላሉ፤ ይሄ ማለት ደግሞ መናዘዝና መቁረብ የነበረባቸው ሰዎች ይህን ሊያጡት ነው» የሚል ነበር።

መናዘዝ የሚፈልጉ ምእመናን ሁሉ ከተናዘዙ በኋላ አባ አሌክሲጅ መሥዋዕተ ቅዳሴ ማሳረግን እንደጀመሩ «ፖሊሶቹ መጡ!» የሚል ድምፅ አስተጋባ። በዚያ ከሚገኙት ምእመናኖቹ ውስጥ ማሪያ ሽኔይደር አንዷ ነበረችና አባን «እንሂድ አባ! እኔጋ ይደበቃሉ፤ እናምልጥ!» አለቻቸው። ስለዚህም ይህች ሴት አባን ከዚያ አካባቢ ራቅ ወዳለ አንድ ቤት ወስዳ በአንድ ክፍል እንዲሸሸጉ አደረገች፤ ወዲያውኑም ምግብ እያቀረበችላቸው «አሁን እንኳ መብላትና ትንሽም ማረፍ ይችላሉ፤ መሸትሸት ማለት ሲጀምር በአቅራቢያ ወደሚገኘው ከተማ እናመልጣለን» አለቻቸው። ቅዳሴ እንደተጀመረ ፖሊሶቹ በመምጣታቸው በመቋረጡ ምንም እንኳ ሰዎቹ የተናዘዙ ቢሆንም ባለመቁረባቸው ምክንያት አባ አሌክሲጅ አዝነዋል። ማሪያ «አባ! ምእመናኖቹ ሁሉ በትልቅ እምነትና መንፈሳዊነት መንፈሳዊ ቁርባን ይሳተፋሉ፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ ተመልሰው እንደሚያቆርቡን ተስፋ እናደርጋለን» አለቻቸው።

ዕለቱ ማመሻሸት ሲጀምር ለሽሽቱ ዝግጅት ተጀመረ፤ ማሪያ የሁለት ዓመትና የስድስት ወር ልጆቿን ከእናቷ ጋር በቤቷ ትታ ፑልኬሪያ የተባለች ሌላ ሴት ዘመዷን በመጥራት አባ አሌክሲጅን በጫካ ውስጥ ከዜሮ በታች ሠላሳ ዲግሪ በሆነ ከባድ በረዷማ ቅዝቃዜ አሥራ ሁለት ኪ.ሜ. በመጓዝ ወደተባለችው ከተማ ሦስቱም ደረሱ። በዚያም ወደ አንድ ባቡር ጣቢያ ሄደው ሁለቱ ሴቶች ለአባ የጉዞ ቲኬትን ገዙላቸው፤ በመጠበቂያ ክፍልም ባቡሩን መጠበቅ ጀመሩ። አንድ ፖሊስ ወደዚያ ክፍል ገባና በቀጥታ አባን «ወዴት እየሄዱ ነው?» ብሎ ሲጠይቃቸው አባ ከድንጋጤ የተነሣ በፍጥነት መልስ መስጠት አልተቻላቸውም ነበር። ይህም የሆነው ስለራሳቸው ሕይወት ያይደለ አብራቸው ስላለችው የልጆች እናት የሆነችው ወጣቷ ስለማሪያ ሕይወት እጣ ፈንታ በማሰብ ነበር። ይህች ወጣት ራሷ ለፖሊሱ «እሳቸው ወዳጃችን ናቸው፤ እኛም እየሸኘናቸው ነው፤ ይኸው ቲኬታቸውን ተመልከት» በማለት ቲኬቱን ሰጠችው። ፖሊሱም ቲኬቱን ከተመለከተ በኋላ አባን «የባቡሩ የመጨረሻ ፉርጎ በሚቀጥለው ፌርማታ ተገንጥሎ ስለሚቀር እዚያ ላይ እንዳይሳፈሩ! መልካም ጉዞ!» በማለት ክፍሉን ለቆ ወጣ። አባ አሌክሲጅም ማሪያን እየተመለከቱ እንዲህ አሏት «እግዚአብሔር መልአክ አድርጎ አንቺን ላከልኝ! ለእኔ ያደረግሽውን በፍጹም አልረሳውም፤ የአምላክ ፈቃድ ከሆነ ሁላችሁንም ለማቁረብ ተመልሼ እመጣለሁ፤ በእያንዳንዷም ቅዳሴዬ ላንቺና ለልጆችሽ እጸልያለሁ።»

ይህ ከሆነ ከአንድ ዓመት በኋላ ማሪያ ወደምትገኝበት ወደ ክራስኖካምስክ አባ አሌክሲጅ መመለስ ቻሉ፤ አሁን መሥዋዕተ ቅዳሴ መቀደስና ምእመናንን ማቁረብ ችለዋል። ማሪያ ግን አባን አንድ ውለታ ያደርጉላት ዘንድ ጠየቀቻቸው፤ እንዲህ ብላ «አባ! እናቴ በጣም ታማ ነው ያለችው፣ ከመሞቷ በፊት ትቆርብ ዘንድ ለርሷ የሚሆን ቅ.ቁርባንን ሊሰጡኝ ይችሉ ይሆን?» አባም ማሪያ ለእናቷ የሚቻላትን ጥንቃቄ ሁሉ አድርጋ በሚገባው ክብር ማቁረብ የምትችል ከሆነ ጠይቀዋት ተስማምተው ቅ. ቁርባንን ሰጧት። ማሪያም የታመሙ እናቷን ለማቁረብ በእጇ ላይ ነጭ ጓንት አጠለቀች፣ ቅ. ቁርባኑን በወረንጦ ነገር ይዛም አቆረበቻቸው፤ ከዚያም በኋላ ተጠቅልሎበት የነበረውን ወረቀት አቃጠለችው።

የማሪያና የፑልኬሪያ ቤተሰቦች ወደ ኪርጊሰታን መኖሪያቸውን ቀየሩ። እ.ኤ.አ. በ1962 ዓ.ም. አባ አሌክሲጅ ወደዚች ከተማ በድብቅ መጥተው ማሪያና ፑልኬሪያን አገኟቸው፤ አንዴ በማሪያ ሌላ ጊዜም በፑልኬሪያ ቤት ቀደሱ። አባም በዚያ በረዷማ መሽት ያን ሁሉ አደጋ ተጋፍጠው የሸኟቸውን የእምነት ውለታ አስታውሰው፤  ከግልጽ መመሪያ ጋር ለፑልኬሪያ ቅ. ቁርባንን ትትውላት ለመሄድ ወሰኑና እንዲህ አሏት «ቅ. ቁርባንን ትቼልሽ እሄዳለሁ፤ ለዘጠኝ ተከታታይ ወራት በመጀመሪያዎቹ ዓርቦች ለኢየሱስ ቅዱስ ልብ አክብሮት መንፈሳዊነትን አድርጉ። የወሩ መጀመሪያ ዓርብ ሲሆን በቤትሽ ቅ. ቁርባንን በመግለጥ በሚታይ መልኩ ከፍ አድርገሽ በማስቀመጥ በሁሉ ነገሮች ታማኝ የሆኑና ምሥጢር የሚጠብቁ ምእመናንን ጠርተሽ አብራችው እንዲሰግዱ ጋብዢ። ዘጠኝ ወር በዚህ መልኩ ከተካሄደ በኋላ ቁረቢው፤ ግን በጥልቅ አክብሮት ይሁን።» እንደተነገራት ሁሉ ነገር ተከናወነ። ለዘጠኝ ወራት በዚያ ቤት ድብቅ የቅ. ቁርባን ስግደት ተደረገ፤ ማሪያም ከሰጋጅ ሴቶች አንዷ ነበረች።

እነዚህ ቅ. ቁርባናዊ ሴቶች (ለቅ. ቁርባን ልዩ መንፈሳዊነትና አክብሮት የነበራቸው ሴቶች) በዚያ ቅዱስ ቁርባን ፊት በአምልኮ በሰገዱ ቁጥር ጥልቅ የሆነ የመቁረብ ምኞት ነበራቸው። ሆኖም ግን ይህ ፍላጎት የነበራቸው ሴቶች ቁጥርና የቅ. ቁርባኑ ብዛት ያለመመጣጠን ይህን አልፈቀደም፤ አባ አሌክሲጅ በዘጠነኛው ወር መጨረሻ ላይ ፑልኬሪያ ብቻ እንድትቆርብና የተቀሩት ደግሞ መንፈሳዊ ተሳትፎ እንዲያደረጉ የወሰኑበት ምክንያትም ይኸው ነበር። ይህም ቢሆን እነዚህ ሴቶች ሁሉ ለቅ. ቁርባን ያላቸው መሰጠት ልዩ ነበር፤ ሁሉም ለልጆቻቸው የቅ. ቁርባንን ጥልቅ እምነት ልክ እንደ እናታዊ ወተት ለልጆቻቸው ለማስተላለፍ በቅተዋል። 

(ይቀጥላል)