እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

ከአንድ ሺህ ኪ.ሜ. በላይ አስቸጋሪ ጉዞ ቅዱስ ቁርባንን ፍለጋ!

መሳጭ የቅዱስ ቁርባን ታሪኮች - ክፍል ፪

ቅዱስ ቁርባናዊ ሴቶችና ቅ.ቁርባን በሶቪየት ኅብረት የአፈና ዘመን

(Dominus Est ከሚል በረዳት ጳጳስ አታናሲየስ ሽኔይደር መጽሐፍ የተወሰደ)

ከ መሳጭ የቅዱስ ቁርባን ታሪኮች - ክፍል - ፩ የቀጠለ

Eucharistic Women 2ለፑልኬሪያ ቅ. ቁርባንን ለመስጠት የሄዱበት ወቅት ለአባ አሌክሲጅ የመጨረሻ ሐዋርያዊ አገልግሎት ነበር፤ ከዚያን ጊዜ በኋላ ወደዚያ አልተመለሱም። ከዚያ ቦታ ወደ ካራጋንዳ እ.ኤ.አ. በሚያዝያ 1962 ዓ.ም. እንደተመለሱ በድብቅ ፖሊሶች ተይዘው አባ ዶሊነካ ወደሚባል ማጎርያ ካምፕ እንዲገቡ ተደረገ። ከብዙ እንግልትና መዋረድ በኋላ አባ አሌክሲጅ ከእስር ቤት ስቃይ ብዛት የተነሣ እ.ኤ.አ. በጥቅምት 1963 ዓ.ም. የሰማዕትነትን ሞት ተጎናፀፉ፣ ብፅእናቸውም በዚሁ ቀን ይከበራል። ቅ. ቁርባናዊ ቅዱስ ካህን በመሆናቸውም መሰል እናቶችን አፍርተዋል። እነዚህ ቅ. ቁርባናዊ ሴቶች ጨለማና ምድረ በዳ በሆነ ድብቅ አናኗር እንዳበቡ አበባዎች ሆነው ቤተ ክርስቲያን እጅጉን ሕያው እንድትሆን አብቅተዋታል።
ሦስተኛዋ ቅ. ቁርባናዊ ሴት ማሪያ ስታንግ ትባላለች፤ እርሷም ከጀርመን አገር ወደ ካዛክስታን የተጋዘች ናት። ይህች ቅድስት የሆነች አያት ሊታመን የማይችል ቀጣይ የሆነ የስቃይ፣ ራስን የመካድና የመስዋዕትነት ሕይወት ነበራት። ገና ከልጅነቷ ጀምሮ ሕይወቷን ለእግዚአብሔር ማስገዛት ትመኝ ነበር። ሕይወቷም እንዲህ የመከራ ጉዞ የሆነባት ከኮሙኒስታዊ ግዞትና ስድት የተነሣ ነው። በዜና መዋዕሏ ማሪያ እንደጻፈችው «ካህናትን አጠፏቸው፤ ከመንደራችን አቅራቢያ ቤ/ያን ነበር፣ ሆኖም በሚያሳዝን ሁኔታ ካህንም ሆነ ቅ. ቁርባን በዚያ አልነበሩም። ያለነዚህ ህላዌም ቤተ ክርስቲያኑ ዖና ነበር፤ ይህም እጅጉን ያስለቅሰኝ ነበር።» ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ማሪያ በየእለቱ የራሷን መሥዋዕት እያቀረበች እንዲህ በማለት በእግዚአብሔር ፊት ጸሎቷን ታደርስ ነበር «ጌታ ሆይ! እባክህ ዳግም ካህናትን ስጠን! ቅ. ቁርባንንም ስጠን! እጅግ የተቀደስክ የኢየሱስ ልብ ሆይ! ስቃዮችን ሁሉ ስላንተ ፈቃድ ስል በጸጋ እቀበላቸዋለሁ።»
በግዞት በሄዱበት በሰፊው ምሥራቃዊው የካዛክስታን አካባቢ ማሪያ ስታንግ በየሰንበቱ በቤቷ ሌሎች ሴቶችን በድብቅ ለጸሎት ትስበስብ ነበር። በነዚህ የሰንበት መሰባሰቦች ሴቶቹ እንዲህ እያሉ አምርረው ይጸልዩ ነበር «እጅግ ተወዳጇ እናታችን ማርያም ሆይ! አሳዛኝነታችንን ተመልከቺ! ካህናትን፣ መምህራንንና እረኞችን ዳግም ስጪኝ!»
በስደት ያሉ ካቶሊክ ካህን በኪረጊስታን ስለነበሩ እ.ኤ.አ. ከ1965 ዓ.ም. ጀምሮ ማሪያ ስታንግ ከአንድ ሺህ ኪ.ሜ. በላይ ወደሚርቀው ወደዚያ መጓዝን ጀመረች፤ ምክንያቱም እርሷ በቋሚነት በምትኖርበት አካባቢ ያሉ ጀርመናውያን ስደተኞች ካህንን ካዩ ሃያ ዓመታት አልፈዋል። ስለዚህ እውነታ ማሪያ እንዲህ ጽፋለች «በኪርጊስታን ወደምትገኘው ፍሩንስ በደረስኩ ጊዜ ካህን አገኘሁ፤ ወደ ካህኑም ቤት ስገባ መንበረ ቁርባን አየሁ። ይህን ነገርና በቅ. ቁርባን ያለውን ጌታ ዳግም ማየቱ በሕይወቴ ይሆንልኛል ብዬ አስቤውም አላውቅም ነበር። በዚያ ተንበረከኩና ተንሰቅስቄ አለቀስኩ፤ ወደ መንበረ ቁርባኑም ቀርቤ ሳምኩት።»
ማሪያ ስታንግ ወደ ካዛክስታን መንደሯ ከመመለሷ በፊት ካህኑ በጻህል አድርገው ቅ. ቁርባንን ሰጧት። እነዚያ በየሰንበቱ በቤቷ የሚሰበሰቡ ሴቶች ለመጀመሪያ ጊዜ በቅ. ቁርባን ዙሪያ ተሰባሰቡ፤ ማሪያም እንዲህ አለቻቸው «ማንም ሊገምተው የማይቻለው ደስታና ርካታ አለን፤ ጌታ በቅ. ቁርባን አብሮን ነው እናም እርሱን መቀበል እንችላለን»። ነገር ግን በዚያ የነበሩ ሴቶች ምሥጢረ ኑዛዜን ካደረጉ በጣም ስለቆዩ «ለብዙ ዓመታት ኑዛዜ አላደረግንም እናም መቁረብ አንችልም» አሏት። ከዚህ በኋላ ስብሰባ አደረጉና መከሩ፤ የሚከተለውንም ሃሳብ ወሰኑ «ያለንበት ሁኔታ እንደፈለግነው ለመናዘዝ የማይመች ነው፤ ቅ. ቁርባንም ስለኛ ከሺህ ኪ.ሜ. ርቀት በላይ ተጉዞ እዚህ ይገኛል፤ እግዚአብሔር ይህ ሁሉ ይረዳዋልና ይምረናል። በመንፈስ ራሳችንን ወደ ምሥጢረ ኑዛዜ እናቅርብ፤ ባደረግናቸውም ኃጢአቶች ከልብ እንጸጸት፤ እያንዳንዳችንም ራሳችን ላይ ያመንበትን ካሣ »(ቀኖና) እንፈጽም»። በዚህም መሠረት ሁሉም የተስማሙበትን አከናወኑ፤ በመቀጠልም በእንባ ሆነው ተንበርክከው ቅ ቁርባንን ተቀበሉ። እንባቸው የንስሐና የደስታ በአንድ ነበር!
ማሪያ ስታንግ ለሠላሳ ዓመታት አማኝ ሴቶቹን በየሰንበቱ በቤቷ መሰብሰቡንና መጸለዩን፣ ለሕፃናትና አዋቂዎች ትምህርተ ክርስቶስ ማስተማሩን፣ ለምሥጢረ ተክሊል ማዘጋጀትን፣ የቀብር ሥርዓት መፈጸምንና ቅ. ቁርባን ማደሉን ቀጠለች። ቅዱስ ቁርባንን ዘወትር በእምነት በተቀጣጠለ ልብና አክብሮታዊ ፍርሃት በተሞላበት መንፈስ ታድል ነበር። እርሷ ካህናዊ ነፍስ ያላት ቅ. ቁርባናዊት ሴት ነበረች።

መሳጭ የቅዱስ ቁርባን ታሪኮች - ክፍል - ፩

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት