“ቅዱስ ቁርባን ቤተክርስቲያንን ይሠራል፤ ያንጻል፤ ቤ/ያን ደግሞ ቅ. ቁርባንን ትሠራለች”

“ቅዱስ ቁርባን ቤተክርስቲያንን ይሠራል፤ ያንጻል፤ ቤ/ያን ደግሞ ቅ. ቁርባንን ትሠራለች” ካርዲናል ሄንሪ ዴ ሉባክ - ኢየሱሳዊ /1896-1991/

Eucharist Churchአንዳንድ ጊዜ ቤተ ክርስቲያንን እንደ ሰው ሠራሽ ተቋም ብቻ የሚያስቡ ሰዎች “ክርስቶስ እምነትን፣ ሕይወትን እንጂ ሃይማኖትን/ቤተክርስቲያንን/የእምነት ተቋምን አላመጣም” እና መሰል ዓረፍተ ነገሮችን ሲናገሩ ይደመጣሉ። በርግጥ እንደነዚህ ዓይነት ሰዎች ይህን ለማለት እውነተኛ ምክንያታቸው ምን እንደሆነ ባናውቅም ስለራሳችን እምነት ካወራን ግን ኢየሱስ በተደራጁ ሰዎች (በሐዋርያት፣ በደቀመዛሙርት፣ በአርድእት...) መካከል እንደነበርና በዚያ መልኩም ይቀጥሉ ዘንድ እንዳዘዛቸውእናነባለን። ለምሣሌም በዮሐ 21፡15-17 ላይ ስምዖን ጴጥሮስን ክርስቶስ ግልገሎቹን፣ ጠቦቶቹንና በጎቹን እንዲያሰማራና እንዲጠብቅ አደራ እንደሰጠው ፤ እንዲሁም በማቴ 16፡18-19 ላይም «18 እኔም እልሃለሁ፥ አንተ ጴጥሮስ ነህ፥ በዚችም ዓለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሠራለሁ፥ የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም።19 የመንግሥተ ሰማያትንም መክፈቻዎች እሰጥሃለሁ፤ በምድር የምታስረው ሁሉ በሰማያት የታሰረ ይሆናል፥ በምድርም የምትፈታው ሁሉ በሰማያት የተፈታ ይሆናል።» ማለቱን ልብ ይሏል።

ሐዋርያቱም የዚህን አደራ ኀላፊነት ለመወጣት ሲሰባሰቡና ሲጸልዩ፤ ወሳኝ የእምነት አንቀጾችን ሲወስኑ፤ ከጌታ የተቀበሉትን አገልግሎታቸውን እነርሱም ለቀጣይ ትውልድ በአደራ ሲያስተላልፉና መሰል ትውፊቶችን አክብረው ሲያስከብሩ በሐዋርያት ሥራ እና በተለያዩ የአዲስ ኪዳን መልእክቶቻቸው ውስጥ እናነባለን። በርግጥ ክርስቶስ በአካል ከሰዎች ጋር ኑሮ እንዴት መኖር እንደሚገባ ኖሮ ያሳየ ፍጹም አምላክና ፍጹም ሰው እንጂ መንፈስ ብቻ ወይም የሆነ የአእምሮ ውልብታ ምትሐት አይደለም።

ይህንን እውነት ስንናገር በወንጌል ጊዜና በሐዋርያት ጊዜ ብቻ እንዲህ ነበር ለማለት አይደለም፤ ምክንያቱም ክርስቶስ በስሙ በሚሰበሰቡ ሰዎች መካከል ይገኛል «ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡበት በዚያ በመካከላቸው እሆናለሁና።» ማቴ 18፡20። ቤተ ክርስቲያናችን ይህን መገኘት በብዙ መልኩ ታስተምራለች። ከእነዚህም መገኘቶች መካከል ደግሞ ክርስቲያናዊ መሠረት አድርጋ የክርስቶስን በቅ. ቁርባን መገኘት ታስተምራለች፤ ምክንያቱም እሱ ራሱ ለዘለዓለማዊነታችን አንድ ዋስትናን ያደረገልን፣ በምንም መልኩ ሊቀየርና ሊደራደር የማይችለው ቅ. ቁርባን በመሆኑ ነው (ዮሐ 6)። እንደ ቤ/ያናችን እምነት ቤ/ያን በክርስቶስ ዙሪያ የሚሰባሰቡ የአማኞች ስብስብ ነው። ከዚህም እውነት የተነሣ “ቅዱስ ቁርባን ቤተክርስቲያንን ይሠራል” የሚለው ሃሳብ ግልጽ ነው። በክርስቶስ ሥጋና ደም ዙሪያ የእርሱ የሆኑት ይሰበሰባሉ፤ ያም የክርስቶሳውያን ስብስብ ናቸው።

በሌላ መልኩ ደግሞ እነዚህ በሥጋውና ደሙ ዙሪያ የሚሰበሰቡ ሰዎች ወይም ቅ. ቁርባንን የሚቀበሉ ሰዎች ኃይል ያለውን አካል ይቀበላሉና ወደ ክርስቶስ ወገንነት ይለወጣሉ፤ የክርስቶስ ፈቃድና ሕይወትን ይማራሉ፤ ከቃል በላይ የሆነውን ትስስርና ቅርበት ይቀምሳሉ። ቅዱስ ሥጋውና ደሙ ከአካላቸው ጋር በመዋሐድ ነፍሳቸውን ለበለጠ ፍጽምና ያነሣሣል፤ ይህን መሰል ሕይወትም እንዲቀጥል ቅ. ቁርባንን ዘወትር ይናፍቃሉ፤ ይሰባሰባሉ፤ ለቅ. ቁርባን መገኘት ራሳቸውን ያስገዛሉ። የሁለተኛው ቫቲካን ሰነድ “በቅ. ቁርባን ኅብስት የክርስቲያኖች አንድነት እውን ይሆናል፤ እነርሱም ከክርስቶስ አካል ጋር አንድ ይሆናሉ” ይላል /LG, ስለቤ/ያን ቀኖናዊ አቋም ቁ.3/። ይህም 1ቆሮ 10፡16-17ን ያንፀባርቃል፡- «የምንባርከው የበረከት ጽዋ ከክርስቶስ ደም ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? የምንቆርሰውስ እንጀራ ከክርስቶስ ሥጋ ጋር ኅብረት ያለው አይደለምን? 17 አንድ እንጀራ ስለ ሆነ፥ እኛ ብዙዎች ስንሆን አንድ ሥጋ ነን፤ ሁላችን ያን አንዱን እንጀራ እንካፈላለንና።»

ቅ. ቁርባን ቤ/ያንን ይሠራል ሲባል የክርስቶስ ህላዌ ክርስቲያኖችን የአካሉ ክፍል ያደርጋቸዋል ማለት ነው፤ ይህንን እውነት ማወቅ በራሱ በቤ/ያን ስም የሚከሠቱ ስህተቶችን እንድናስወግድ ያግዘናል። የአምልኮ ሥርዓታችን ምንጭና ግብ በቀራንዮ በመስቀል፣ በቅዱስ ቁርባን ዛሬም ራሱን የሰጠን ጌታ ነው። መጸለያችንና መሰባሰባችን በርሱና ለርሱ ትኩረትን በሰጠ ሁኔታ ነው። የመሰባሰባችን ግብም በቅዱስ ቁርባን ራሱን የሰጠንን ጌታ ለማምለክና በሕይወታችን ለማክበር ነው።

ቤ/ያን መቼውንም ቢሆን ከክርስቶስ ውጪ የእገሌ መሆን አትችልም፤ መሥራቿ፣ ማእከሏም ሆነ መድረሻዋ ራሱ ክርስቶስ ነው። ቅ. ጳውሎስ ይህን ትምህርት ጎላ በማድረግ ከሰዎች ጋር የተጣበቁ «ክርስቲያኖችን» እንዲላቀቁ ይገስፃቸዋል። ሰው የመከተል አባዜ ለተጠናወታቸው የቆሮንጦስ ክርስቲያኖች እውነቱን ለመናገር ምንም ያህል ጊዜ አላባከነም በመጀመሪያ መልእክቱ 1፡10-17 ላይ እንዲህ ይላቸዋል፤

«10 ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ሁላችሁ አንድ ንግግር እንድትናገሩ በአንድ ልብና በአንድ አሳብም የተባበራችሁ እንድትሆኑ እንጂ መለያየት በመካከላችሁ እንዳይሆን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እለምናችኋለሁ። 11 ወንድሞቼ ሆይ፥ በመካከላችሁ ክርክር እንዳለ ስለ እናንተ የቀሎዔ ቤተ ሰዎች አስታውቀውኛልና። 12 ይህንም እላለሁ። እያንዳንዳችሁ። እኔ የጳውሎስ ነኝ፥ እኔስ የአጵሎስ ነኝ፥ እኔ ግን የኬፋ ነኝ፥ እኔስ የክርስቶስ ነኝ ትላላችሁ። 13 ክርስቶስ ተከፍሎአልን? ጳውሎስስ ስለ እናንተ ተሰቀለን? ወይስ በጳውሎስ ስም ተጠመቃችሁን? 14-15 በስሜ እንደ ተጠመቃችሁ ማንም እንዳይል ከቀርስጶስና ከጋይዮስ በቀር ከእናንተ አንድን እንኳ ስላላጠመቅሁ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ። 16 የእስጢፋኖስንም ቤተ ሰዎች ደግሞ አጥምቄአለሁ፤ ጨምሬ ሌላ አጥምቄ እንደ ሆነ አላውቅም። 17 ለማጥመቅ ክርስቶስ አልላከኝምና፥ ወንጌልን ልሰብክ እንጂ፤ የክርስቶስ መስቀል ከንቱ እንዳይሆን በቃል ጥበብ አይደለም።»

እርሱ እንደተረዳው ከሆነ የቆሮንጦሷ ቤ/ያን የመከፋፈል ስጋት ከትምህርት ወይም ከሥርዓት ሐቀኛነት የተነሣ ሳይሆን የተለያዩ የቤ/ያን መሪዎች ጋር የመጣበቅ ዝንባሌ ያመጣው ነበር፤ ልክ ሐዋርያት በክርስቶስ ማንነት ተማርከው እንደተከተሉት ሁሉ አንዳንድ ክርስቲያኖችም ወደ ክርስቶስ ሊመሩ በሚገባቸው ሰዎች ብቻ ራሳቸውን ገድበው ወደ ክርስቶስ መዝለቁ ያዳግታቸዋል።

አጵሎስ በሐሥ 18፡24-28 ላይ የዮሐንስ መጥምቅ ተከታይ የነበረ መጽሐፍ ቅዱስን ጠንቅቆ የተማረና ጥሩ የመናገር ችሎታ ያለው አይሁድ መሆኑ ተጠቅሷል፤ በተጨማሪም ስለጌታ በመንፈስ የተቃጠለ ሆኖ በትክክል የሚሰብክና የሚያስተምር ነበር። ጵርስቅላና አቂላ ይበልጥ ወደ ክርስቲያናዊው መንገድ እንዲገባ አስተምረውት የቆሮንጦስ ቤ/ያንን ተቀላቅሏል። «ኬፋ» የተሰኘውም ጴጥሮስ፣ ስምዖን የዮና ልጅም ተብሎ የተጠራው ነው። ኬፋ የሚለው የአረማይስጥ ቃል ክርስቶስ ስምዖንን «ዓለት» «ጴጥሮስ» የሚለውን ትርጓሜ ለመስጠት የተጠቀመበት ስም ነው (ማቴ 16፡18)። ቅዱስ ጴጥሮስ በቆሮንጦስ አገልግሎ ባይሆንም ወይም እርሱ ከሰበከበት የመጡ ክርስቲያኖች በዚያ የሚገኙ ስለሆነ ቢሆንም ምናልባት ቅ. ጳውሎስ የኬፋን ስም የሚጠቅሰው የአማኞቹን እይታ ለማስፋት እንዲያግዝ ብሎ ይሆናል። ስለዚህ እንደ ሰው እይታ ከሆነ እነዚህ መሪዎች ሰው በቀላሉ ይከተላቸው ዘንድ የሚያበቃ ሰዋዊ መስፈርት ነበራቸው፤ ራሱ ቅዱስ ጳውሎስም ቢሆን በትምህርቱም ሆነ በሌሎች ብቃቱ ሰዎች ሊያነጻጽሩት የሚችል ዓይነት ሰው ነበር፤ ሆኖም ግን ይህ ዓይነት አካሄድ የክርስቶስ አካል የሆነችውን ቤተ ክርስቲያንን የሚያሰቃይ መሆኑን ጠንቅቆ ያውቃል፤ እንደ አንድ አካል የምትቆጠረው ቤተ ክርስቲያን አንድ ራስ ብቻ ይኖራት ዘንድ አግባብ ነው።

1ቆሮ 3፡1-9/4፡6-7 ላይ ለቆሮንጦስ ቤ/ያን የመከፋፈልን ጉዳት ያደረሰው የጳውሎስና አጵሎስ መሆኑ ግልፅ ነው። «1 እኔም፥ ወንድሞች ሆይ፥ የሥጋ እንደ መሆናችሁ፥ በክርስቶስም ሕፃናት እንደ መሆናችሁ እንጂ መንፈሳውያን እንደ መሆናችሁ ልናገራችሁ አልቻልሁም። 2 ገና ጽኑ መብል ለመብላት አትችሉም ነበርና ወተት ጋትኋችሁ፤ 3 ገና ሥጋውያን ናችሁና እስከ አሁን ድረስ ገና አትችሉም። ቅናትና ክርክር ስለሚገኝባችሁ ሥጋውያን መሆናችሁ አይደላችሁምን? እንደ ሰው ልማድስ አትመላለሱምን? 4 አንዱ። እኔ የጳውሎስ ነኝ፥ ሁለተኛውም። እኔ የአጵሎስ ነኝ ቢል ሰዎች ብቻ መሆናችሁ አይደለምን? 5 አጵሎስ እንግዲህ ምንድር ነው? ጳውሎስስ ምንድር ነው? በእነርሱ እጅ ያመናችሁ አገልጋዮች ናቸው፤ ለእያንዳንዳቸውም ጌታ እንደ ሰጣቸው ያገለግላሉ። 6 እኔ ተከልሁ አጵሎስም አጠጣ ነገር ግን እግዚአብሔር ያሳድግ ነበር፤ 7 እንግዲያስ የሚያሳድግ እግዚአብሔር እንጂ የሚተክል ቢሆን ወይም የሚያጠጣ ቢሆን አንዳች አይደለም። 8 የሚተክልና የሚያጠጣ አንድ ናቸው፥ ነገር ግን እያንዳንዱ እንደ ራሱ ድካም መጠን የራሱን ደመወዝ ይቀበላል። 9 የእግዚአብሔር እርሻ ናችሁ፤ የእግዚአብሔር ሕንፃ ናችሁ፤ ከእርሱ ጋር አብረን የምንሠራ ነንና።» ጳውሎስ እዚህ ላይ በክርስቶስ ሳይሆን በአገልጋዮች ላይ ትኩረታቸውን ያደረጉ ሰዎችን እንደ ሕፃናት እንጂ እንደ መንፈሳውያን ለማየት እንደሚቸገር ገልጿል፤ ቅ. ቁርባን የቤ/ያን ማእከል መሆኑን ማስተዋል ከዚህ ስህተት ይታደገናል። በተመሳሳይ ሁኔታም በክርስቶስ አገልጋይነት ስም ራሳቸው ላይ የስምና የቅጽል ብዛት ለሚከምሩት እንዲህ ይላል፡- 4፡6-7 «6 ወንድሞች ሆይ፥ ስለ አንዱ በአንዱ ላይ አንዳችሁም እንዳይታበዩ። ከተጻፈው አትለፍ የሚለውን በእኛ ትማሩ ዘንድ፥ ይህን በእናንተ ምክንያት ስለ ራሴና ስለ አጵሎስ እንደ ምሳሌ ተናገርሁ። 7 አንተ እንድትበልጥ ማን አድርጎሃል? ያልተቀበልኸውስ ምን አለህ? የተቀበልህ ከሆንህ ግን እንዳልተቀበልህ የምትመካ ስለ ምንድር ነው?» በዚህ መልኩ ሰዎች በእግዚአብሔር ስም በእነርሱ በኩል አንዳች ቢከናወን ምንጩ እግዚአብሔር መሆኑን መዘንጋት እንደሌለባቸው ያስተምራል፤ ከምንጭነቱም ባሻገር ክብሩ ሁሉም ወደ አንድ ግብ ማለትም ወደ እግዚአብሔር መቃኘት እንዳለበት ያሳያል፤ ለዚህም ነው ቅ. ቁርባን የነገሮቻችን ምንጭና ቁንጮ መሆኑን መዘንጋት የሌለብን።

ቅ. ጳውሎስ ሰው ዓይኑን ከክርስቶስ አንስቶ በሰው ላይ ማድረግ ከጀመረ «ክርስቲያን» ወይም የክርስቶስ ተከታይ ተብሎ መጠራቱ የማይስማማ መሆኑ ገብቶታል። በዚያው መልእክቱ 1፡12 ላይ የተጠቀሰው «እኔስ የክርስቶስ ነኝ ትላላችሁ» የሚለው አባባል ለማለት ብቻ እንደሚሉት እንጂ ሰው ላይ ማተኮራቸውን ለመግለፅ የተጠቀመበት ነው። ቅ. ቁርባንን መሠረት፣ ማእከልና መድረሻ አደረግን ማለት ሙላት እንጂ መጉደል እንዳልሆነ በጳውሎስ ንግግር ውስጥ ማየት እንችላለን «ማንም በሰው አይመካ። ነገር ሁሉ የእናንተ ነውና፤ 22 ጳውሎስ ቢሆን አጵሎስም ቢሆን ኬፋም ቢሆን ዓለምም ቢሆን ሕይወትም ቢሆን ሞትም ቢሆን ያለውም ቢሆን የሚመጣውም ቢሆን፥23 ሁሉ የእናንተ ነው፥ እናንተም የክርስቶስ ናችሁ ክርስቶስም የእግዚአብሔር ነው» 1ቆሮ 3፡21-23።