እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

ኦ ቅዱስ ቁርባን! የኢየሱስ ቅዱስ ልብ ትርታ!

ኦ ቅዱስ ቁርባን! የኢየሱስ ቅዱስ ልብ ትርታ!

Libeyesus Kurbanኢየሱስ በምድር ከሐዋርያት ጋር ይመላለስ በነበረበት ቆይታው እንደ ነገ ዓርብ ከመሰቀሉ በፊት ሐሙስ ምሽት የመጨረሻው ራት ዝግጅት ላይ ብዙ ጥልቅ ትርጉም ያላቸውን ተግባሮች አከናውኗል፤ ፎጣ አሸርጦ የሐዋርያቱን እግር ጎንበስ ብሎ አጥቦ ከእነርሱ ጋር የነገ ስቅላቱንና መስዋእትነቱን እያሰበ ማእድን ተቋደሰ። በዚህ ማእድ ዙሪያ የተደረጉ ነገሮችና ንግግሮች ልብን የሚነኩ ነበሩ። ሐዋርያት ጌታና መምህር የሚሉት በውስጣቸው ብዙ ልእልናን የሰጡት እርሱ ጎንበስ ብሎ ሲያጥባቸው “ጌታ ሆይ፥ አንተ የእኔን እግር ታጥባለህን?” ቢሉትም ጌታ ብቻም ያይደል መምህርም ነውና አደረገው።

ቀጥሎም በውስጡ ከአባቱ ፈቃድ ጋር የሚያታግለው መስቀልን የሚያስበው የልቡ ትርታ በውስጥ እየቀጠለ ኢየሱስ ለደቀ መዛምርቱ ልዩ ማእድን አዘጋጀ! በዚህ ማእድ ላይ ተላልፎ እንደሚሰጥ፣ ያም ሰው እዛው ማእድ ላይ እንዳለ ነገር ግን ይህ ቢሆንም ቅሉ በዚያች ምሽትና ማእድ እርሱ እነርሱን እስከ ዘላለም እንደሚያፈቅራቸውና የዚህ ፍቅር መገለጫ የሚሆነውንም በቅዱስ ሥጋውና ደሙ ከእነርሱ ጋር በቀጣይነት የሚገኝበትን የቅዱስ ቁርባን ምሥጢር ሠራላቸው፣ ሠራልን።

ይህ ሁሉ ሲሆን የውስጥ የልብ ትርታውን የሚሰማ አንድ ደቀ መዝሙር ነበር፤ “ኢየሱስም ይወደው የነበረ ከደቀ መዛሙርቱ አንዱ በኢየሱስ ደረት ላይ ተጠጋ፤ ስለዚህ ስምዖን ጴጥሮስ እርሱን ጠቅሶ። ስለማን እንደ ተናገረ ንገረን አለው። እርሱም በኢየሱስ ደረት እንዲህ ተጠግቶ። ጌታ ሆይ፥ ማን ነው? አለው። ኢየሱስም። እኔ ቍራሽ አጥቅሼ የምሰጠው እርሱ ነው ብሎ መለሰለት። ቍራሽም አጥቅሶ ለአስቆሮቱ ለስምዖን ልጅ ለይሁዳ ሰጠው። ቍራሽም ከተቀበለ በኋላ ያን ጊዜ ሰይጣን ገባበት። እንግዲህ ኢየሱስ። የምታደርገውን ቶሎ ብለህ አድርግ አለው።” /ዮሐ 13:23-27/

ይህ በኢየሱስ ደረት ተጠግቶ የነበረ ሐዋርያ ያዳምጥ የነበረው ከኢየሱስ አንደበት የሚወጣውን ቃል ብቻ ሳይሆን የኢየሱስንም የልብ ትርታ እንደነበር ማሰብ እንችላለን፤ ስለዚህም ከቃሉ በላይ የቃሉን ንዝረትና ሕይወት ሰጪ የሆነውን የኢየሱስን ደም ዝውውር ያዳምጥ ነበር። በዚህ ልብ ውስጥ የሚረጨው ደም ምን ዓይነት ይሆን ብሎም አስቦ ተመስጦ ይሆናል። ያ በቅፍርናሆም በምኩራብ ኢየሱስ “ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ የዘላለም ሕይወት አለው፥ እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ። ሥጋዬ እውነተኛ መብል ደሜም እውነተኛ መጠጥ ነውና። ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ በእኔ ይኖራል እኔም በእርሱ እኖራለሁ። ሕያው አብ እንደ ላከኝ እኔም ከአብ የተነሣ ሕያው እንደምሆን፥ እንዲሁ የሚበላኝ ደግሞ ከእኔ የተነሣ ሕያው ይሆናል። ከሰማይ የወረደ እንጀራ ይህ ነው፤ አባቶቻችሁ መና በልተው እንደ ሞቱ አይደለም፤ ይህን እንጀራ የሚበላ ለዘላለም ይኖራል” /ዮሐ 6:54-55/ በማለት ያስተማረውን ሐዋርያው እየዘከረ ከደረቱ የዚያን ክቡር ደም እንቅስቃሴ አስተውሏል። ግን አ’እምሮው እንዴት ይሆን ይህ በኢየሱስ ልብ በመረጨትና በአካሉ ውስጥ የሚዞረውን እኔ ልጠጣ የምችለው ብሎም በውስጡ ጠይቋል።

ብዙም አልቆየም ኢየሱስ በዚያው ማእድ ለደቀ መዝሙሩ ግልጽ መልስ ሰጠው፤ ቃሉ እንደሚለን “ሲበሉም ኢየሱስ እንጀራን አንሥቶ ባረከ ቈርሶም ሰጣቸውና። እንካችሁ፤ ይህ ሥጋዬ ነው አለ። ጽዋንም አንሥቶ አመስግኖም ሰጣቸው፥ ሁሉም ከእርሱ ጠጡ። እርሱም። ይህ ስለ ብዙዎች የሚፈስ የአዲስ ኪዳን ደሜ ነው።” /ማር 14:22-24/። ራሱ በግልጽ ይህን ደምካልጠጣችሁ የዘላለም ሕይወት የላችሁም ብሏልና እንግዲህ ከኢየሱስ ልብ ትርታ የሚመነጨውን ይህን ደም በቅዱስ ቁርባን መቀበል መቻል ምንኛ መታደል ነው!

ያ በኢየሱስ ደረት ላይ ተንተርሶ የቅዱስ ልቡን ትርታ ያዳመጠ ሐዋርያ ቅ. ዮሐንስ ሌላም ድንቅ ነገር መሰከረልን “አይሁድም የማዘጋጀት ቀን ስለ ሆነ ያ ሰንበት ትልቅ ነበረና ሥጋቸው በሰንበት በመስቀል ላይ እንዳይኖር፥ ጭናቸውን ሰብረው እንዲያወርዱአቸው ጲላጦስን ለመኑት። ጭፍሮችም መጥተው የፊተኛውን ጭን ከእርሱም ጋር የተሰቀለውን የሌላውን ጭን ሰበሩ፤ ወደ ኢየሱስ በመጡ ጊዜ ግን እርሱ ፈጽሞ እንደ ሞተ አይተው ጭኑን አልሰበሩም፤ ነገር ግን ከጭፍሮች አንዱ ጎኑን በጦር ወጋው፤ ወዲያውም ደምና ውኃ ወጣ። ያየውም መስክሮአል፤ ምስክሩም እውነት ነው፤ እናንተም ደግሞ ታምኑ ዘንድ እርሱ እውነት እንዲናገር ያውቃል።” /ዮሐ 19:31-35/።

ይህ የተወጋው የኢየሱስ ጎን የቅዱስ ልቡ መስኮት ነበር! በዚያ በኩል ውሃና ደም ወጣ፤ የጥምቀታችንና የቅ. ቁርባን በር! ጥምቀት የእግዚአብሔር ልጆች የምንሆንብት ምስጢርና ክቡር ደሙ /ቅ. ቁርባን/ እንደ እግዚአብሔር ልጅነታችን ለማደግ የምንመግብበት! ስለዚህ የኢየሱስ ቅዱስ ልብ እንደ ክርስቲያን የህልውናችን ምንጭና ግብ ነው፤ እንደ ካቶሊክነታችን ቅዱስ ቁርባን በሕይወታችን ትልቁን ቦታ መያዝ እንዳለበት የምንመኘውም ለዚሁ የወንጌል እውነት ነው። የክርስቶስ ክቡር ደም ሁሌም ሕያው ነውና እርሱ ከእኛ ጋር አንድ መሆንን የመረጠበትም መንገድም ነውና በማያወላዳ መልኩ በግልጽ እኔን ካልጠጣችሁ ሕይወት የላችሁም ብሎናል፤ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ የሰውን ልጅ ሥጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም።” /ዮሐ 6:53/።

በአንድ አጋጣሚ ከዚህ ክቡር ምሥጢር ማለትም ሥጋሁ ወደሙ ተሳትፎ የሚያውቅ አሁን ግን በተለያየ ምክንያት ከቅ. ቁርባን ለራቁ ልበ ኢየሱስ ዛሬም ይጣራል፤ የልቡን ትርታ ጠጋ ብላችሁ አዳምጡ በማለት ይጋብዛል። ስለዚህ ከዚህ ምሥጢር ለራቁት እየጸለይን እኛም የዚህን ድንቅ ምሥጢር ትርጉም ማለትም ፍቅርን፣ ምሕረትን፣ ይቅርታን፣ ትእግሥትን፣ ገርነትን፣ ቸርነትን...ከሌሎች ጋር እየተካፈልን ለመኖር እንትጋ።

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት