፭ - “በደላችንን ይቅር በለን፤ እኛም የበደሉንን ይቅር እንደምንል”

    ፭ - “በደላችንን ይቅር በለን፤ እኛም የበደሉንን ይቅር እንደምንል”

ይህ ልመና አስደናቂ ነው፡፡ ልመናው “በደላችንን ይቅር በለን” የሚለውን የመጀመሪያውን ሐረግ ብቻ ቢይዝ ኖሮ በተዘዋዋሪ በመጀመሪያዎቹ በሦስቱ የጌታ ጸሎት ውስጥ በተካተተ ነበር፤ የክርስቶስ መስዋዕት “ስርየት ኃጢአትን” በለስገኘት ነውና፡፡ ነገር ግን በሁለኛው ሐረግ መሠረት እኛ በቅድሚያ ጥብቅ ግዴታን ካላሟላን በስተቀር ልመናችን ተደማጭነት ሊያገኝ አይችልም፡፡ ልመናችን የሚመለከተው የወደፊቱን ጉዳይ ቢሆንም የእኛ ምላሽ ቀድሞ መታየት አለበት፡፡ ሁለቱ የልመናው ክፍሎች የሚተሳሰሩት “እንደ” በሚለው ቃል ነው፡፡

በደላችንን ይቅር በለን …

ወደ አባታችን መጸለይ የጀመርነው በሙሉ ልብ ነው፡፡ ስሙ እንዲቀደሰ ስንለምን በእርግጥ የምንጠይቀው እኛው ራሳችን ሁል ጊዜ ይበልጥ የተቀደስን እንድንሆን ነው፡፡ ምንም እንኳን የምስጢረ ጥምቀትን ልብስ የለበስን ብንሆንም ኃጢአትን ከመሥራትና ከእግዚአብሔር ከመራቀ አልተቆጠብንም፡፡ በዚህ አዲስ ልመና እንደኮብላዩና አባካኙ ልጅ ወደ እርሱ እንመለሳለን እንደቀራጩም በፊቱ ኃጢአተኞች መሆናችን እንገነዘባለን፡፡ ልመናችን ችግረኛነታችንን እና ምሕረቱን በ “መናዘዝ” ይጀምራል፡፡ እኛ በልጁ “ቤዛነታችንን፣ የኃጢአታችንን ስርየት ስለአገኘን፤” ተስፋችን የጸና ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያኑም ምስጢራት ውጤታማና ትክክለኛ የሆነ የምሕረቱን ምልክት እናገኛለን፡፡

እነሆ አሁን ነገሩ እጅግ አስቸጋሪ ነው - ይህ የምሕረት ፍሰት የበደሉንን ይቅር እስካላልን ድረስ ልቦቻችንን ዘልቆ መግባት አይቻለውም፡፡ እንደ ክርስቶስ ሥጋም ፍቅርም የማይከፋፈል ነው፡፡ የምናያቸውም ወንድማችንና እኀታችንን የማንወድ ከሆነ የማናየውን እግዚአብሔርን መውደድ አንችልም፡፡ ለወንድሞቻችንና ለእህቶቻችን ይቅርታ በመከልከል ልቦቻችን ይዘጋሉ፡፡ ድንዳኔያቸውም የአብን መሐሪ ፍቅር እንዳይቀበሉ ያግዳቸዋል፡፡ ነገር ግን ኃጢአታችንን ስንናዘዝ ልቦቻችን ለጸጋው ክፍት ይሆናሉ፡፡

ይህ ልመና እጅግ አስፈላጊ ከመሆኑ የተነሣ እግዚአብሔር መልሶ በተራራው ስብከት በግልጽ የሚያበለጽገው ብቸኛ ልመና ነው፡፡ ይህ የኪዳኑ ምስጢር ወሳኝ ጥያቄ ለሰው የማይቻል ነው፡፡ ይሁን እንጂ “በእግዚአብሔር ዘንድ ሁሉ ነገር ይቻላል፡፡” ማቴ 19፡27


እኛም የበደሉንን ይቅር እንደምንል …

ይህ “እንደ” የሚለው ቃል በኢየሱስ ትምህርት ውስጥ ልዩ ነገር አይደለም፡፡ “እንግዲህ የሰማዩ አባታችሁ ፍጹም እንደሆነ እናንተም ፍጹማን ሁኑ፡፡” “አባታችሁ ርኅሩኅ እንደሆነ እናንተ ሩኅሩኅ ሁኑ፡፡” “ምርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ እንደወደድኋችሁ እናንተ ደግሞ እርስ በእርሳችሁ ትዋደድ ዘንድ አዲስ ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ፡፡ ይላል፡፡ መለኮታዊውን ምሳሌ ከውጭ በመከተል የጌታን ትዕዛዝ መፈጸም አይቻልም፤ የአምላካችን ቅድስና፣ ምሕረትና ፍቅር ከልብ ያመነ ሕያው ተሳትፎን ይጠይቃል፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረውን አሳብ “የእኛ” ማድረግ የሚችለው የሚኖረን መንፈስ ነው፡፡ ያንጊዜ የይቅርታ አንድነት እውን ሆኖ እኛ ራሳችንን “እግዚአብሔር በክርስቶስ ይቅር እንዳለን ይቅር ስንባባል” እናገኘዋለን፡፡

በዚህም መሠረት እስከመጨረሻው ስለሚወደው ፍቅር ስለምሕረት የሚያወሳው የጌታ ቃል ሕያው እውነታ ይሆናል፡፡ ጌታ ስለ ቤተ ክርስቲያናዊ ሱታፌ የሰጠው ትምህርት መደምደሚያ የሆነው የጨካኙ ባሪያ ታሪክ ከእናንተ እያንዳንዱ ወንድሙን ከልቡ ይቅር ካላለ እንዲሁ ደግሞ የሰማዩ አባቴ ያደርግባችኋል፡፡ በሚሉ ቃላት ይደመደማል፡፡ በእውነትም ሁሉ ነገር የሚታሰረውና የሚፈታለ “በልብ ጥልቅ” ውስጥ ነው፡፡ በደልን መርሳት ወይም አለማሰብ ከአቅማችን በላይ ነው፡፡ ነገር ግን ራሱን ለመንፈስ ቅዱስ የሚያቀርብ ልብ ጉዳትን ወደ ርኀራኄ በመለወጥ፣ ሕመምን ወደ ምልጃ በማሸጋገር ትውስታን ያነጻል፡፡

ክርስቲያናዊ ጸሎት ጠላትን ይቅር እስከማለት ይደርሳል፡፡ ጸሎቱ ደቀመዝሙሩን በመለወጥ መምህሩን በመለወጥ መምህሩን እንደመስል ያደርገዋል፡፡ ይቅርታ በክርስቲያናዊ ጸሎት የላቀ ደረጃ አለው፡፡ የጸሎትን ፍሬ መቀበል የሚችሉ ከእግዚአብሔር ርኀራኄ ጋር የሚስማሙ ልቦች ብቻ ናቸው፡፡ በዓለማችን ከኃጢአት ይልቅ ፍቅር እንደሚጠነክር ይቅርታ የመሰክራል፡፡ የትላንትናዎቹና ከዛሬዎቹ ሰማዕታት ለኢየሱስ ይህንኑ ምስክርነት ይሰጣሉ፡፡ ይቅርታ የእግዚብሔር ልጆች ከአባታቸው ጋር እንዲሁም ሰዎች እርስ በርሳቸው ይታረቁ ዘንድ የሚያስፈልግ መሠረታዊ ሁኔታ ነው፡፡

ማንም ሉቃስ 11፡4 ላይ እንደተጠቀሰው ስለ “ኃጢአቶች” ቢናገር ወይም ማቴዎስ 6፡12 ላይ እንደሰፈረው ስለ “በደሎች” ቢያወሳ ይህ በመሠረቱ መለኮታዊ የሆነ ምሕረት ወሰን ወይም ልክ የለውም እኛ ሁልጊዜ በደለኞች ነን፡- “እርስ በእርሳችሁ ከመዋደድ በቀር ለማንም ዕዳ አይኑርባችሁ፡፡” ሮሜ 13፡8 የቅድስት ሥላሴ ሱታፌ በማንኛውም ዓይነት ግንኙነት የእውነት ምንጭና መስፈርት ነው፡፡ ይህም ሱታፌ በጸሎትና ቅዱስ ቁርባን ያለማቋረጥ ይኖራል፡፡

እግዚአብሔር መለያየትን የሚዘራ ሰው የሚያቀርበውን መስዋዕት አይቀበልም፤ ነገር ግን መጀመሪያ ከወንድሙ ጋር ይታረቅ ዘንድ ከመሠዊያው እንዲርቅ ያዝዘዋል፡፡ እግዚአብሔር ደስ የሚሰኘሙ ሰላምን በሚያደርጉ ጸሎቶች ብቻ ነው፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ከሁሉ የበለጠ መስዋዕት ሰላም፣ በወንድማማቾች መካከል የሚደረግ ስምምነት እንዲሁም በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ አንድነት አንድ የሆነ ሕዝብ ነው፡፡

/የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ ከቁጥር 2838-2845/