የዓለም ውበት፣ ሥርዓትና ውኅደት
- Category: አንቀጽ ፭ - ሰማይና ምድር
- Published: Saturday, 21 July 2012 07:24
- Written by Super User
- Hits: 1959
- 21 Jul
ግዙፉ ዓለም
ግዙፉን ዓለምን በተለያየ መልኩ፣ ዓይነቱና ሥርዓቱ የፈጠረው እግዚአብሔር ራሱ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የፈጣሪን ሥራ በምሳሌያዊ መልክ ለስድስት ተከታታይ ቀናት ተካሄዶ፣ በሰባተኛው ቀን "ዕረፍት" እንደ ተጠናቀቀ መለከታዊ አድርጎ ያቀርብልናል፡፡ የፍጥረትን ርእሰ ጉዳይ በተመለከተ መጽሐፍ ቅድስ ለድኅነታችን በእግዚአብሔር የተገለጡልንን እሴቶች "የመላውን ፍጥረት ውስጣዊ ባሕርይ" እሴትና አደረጃጀት ተገንዝበን ለእግዚአብሔር ምስጋና እናውል ዘንድ ያስተምረናል"
ሕላዌውን በፈጣሪ አምላክ ላይ ያልመሠረተ ከቶ ምንም ነገር አይኖርም፡- ዓለም የተጀመረው የእግዚአብሔር ቃል ከምንም ነገር /ካለመኖር ወደ መኖር/ ሲያመጣው ነው፤ ሕልውና ያላቸው ፍጥረታት ሁሉ፣ ተፈጥሮ በሙሉና መላው የሰው ልጅ ታሪክ የተመሠረቱት የዓለም መገናኛ የጊዜ መጀመሪያ ከሆነው ከዚህ ጥንተ ሁኔታ ነው፡፡
እያንዳንዱ ፍጥረት ልዩ የሆነ የራሱ በጎነት ፍጽምና አለው፡- ከ "ስድስቱ ቀናት" ሥራዎች እያንዳንዱን "እግዚአብሔር መልካም እንደሆነ አየ "ተብሏል፡፡ "በፍጥረት ልዩ ባሕርይ ምክንያት፣ ቁሳዊ ሕላዌ የራሱን ጽናት እውነትና ጥራት እንዲሁም ሥርዓትና ሕግ ታድሏል" እያንዳንዱም ፍጡር ከራሱ ሕላዌ በሚመነጭ በራሱ መንገድ የእግዚአብሔርን ወሰን የለሽ ጥበብና መልካምነት ያንጸባርቃል፡፡ ስለዚህ ሰው ነገሮችን ከእግዚአብሔር ፍቃድ ውጭ ያለ አግባብ በመጠቀም እግዚአብሔርን ንቆ በራሱና በአካባቢው ላይ አደጋ እንዳያስከትል የእያንዳንዱን ፍጥረት ልዩ መልካምነት ማክበር አለበት፡፡
እግዚአብሔር የፍጥረታትን እርስ በእርስ መደጋገፍ ይፈልጋል፡- ፀሐይና ጨረቃ፣ የጥድ ዛፍና ትንሿ አበባ፣ ንስርና ድንቢጥ ሥፍር ቁጥር የሌለው ልዩነታቸውና አለመመጣጠናቸው ማንም ፍጥረት ራሱን በራሱ እንደማይችል ያሳየናል፡፡ ፍጡራን ሊኖሩ የሚችሉት እርስ በእርስ በመደጋገፍ አንዱ ሌላውን ምሉዕ ለማድረግ አንዱ ሌላኛውን በማገልገል ብቻ ነው፡፡
የዓለም ውበት፡- ዓለም የሥርዓት እና ውሑድነት፣ በፍጥረታት መካከል ያሉት ልዩነቶችና ዝምድናዎች ውጤት ነው፡፡ ሰው እነዚህን እንደ ተፈጥሮ ሕግ ደረጃ በደረጃ ይገነዘባቸዋል፡፡ ተመራማሪዎች አድናቆታቸውን ይቸሯቸዋል፡፡ የፍጥረት ውበት ወሰን የሌለው የፈጣሪን ውበት ያንጸባርቃልና የሰው ልጅን ፈቃድና አዕምሮ ገዝቶ ከበሬታን ማትረፍ ይኖርበታል፡፡
የፍጥረት ቅደም ተከተል፣ አነስተኛ ፍጽምና ካለው አንስቶ የበለጠ ፍጽምና እስከተቀዳጀው ድረስ በ "ስድስቱ ቀናት" የተፈጣጠር ሥርዓት ሂደት ይገለጻል፡፡ እግዚአብሔር ፍጥረታቱን ሁሉ ይወዳል፤ እያንዳንዱንም ፍጥረት ድንቢጥን እንኳ ሳይቀር ይንከባከባል፡፡ ይሁን እንጂ ኢየሱስ "እናንተ አኮ ከብዙ ድንቢጦች ትበልጣላችሁ፤" ወይም እንደገና "ታዲያ ከበግ ሰው አንዴት አይበልጥም?"ሉቃስ 12፡6-7፤ ማቴ 12፡12 ብሏል፡፡
በመንፈስ አነሳሽነት የቀረበው ገለጻ የሰው አፈጣጠር ከሌሎች ፍጥረታት በመለየት እንደሚያስገነዝበው፣ ሰው የፈጣሪ ሥራ ጉልላት ነው፡፡ ሁሉም አንድ ፈጣሪ ያላቸውና ሁሉም የክብሩ ተገዥ ከመሆናቸው ሐቅ የተነሣ በሁሉም ፍጥረታት መካከል ኅብረት አለ፤
ጌታ ሆይ፣ በፍጥረታት ሁሉ፣ በተለይም ለቀን ብርሃን በሰጠኸን በእርሱ በወንድም ፀሐይ የተመሰገንህ ሁን፤ ታላቅ ድንቅን የሚያንፀባርቅና፣ የፍጥረታት ሁሉ ልዑል የሆንከውን፣ የአንተን ምልክት የሚሰጠን ምልክት የሚሰጠን ውብ ነገር ነውና...
ጌታ ሆይ፤ በጣም ጠቃሚና ትሑት፣ ክቡርና ድንግል ስለሆነችው፣ ስለእህት ውኃ፣ የተመሰገንህ ሁን...
ጌታዬ ሆይ፣ በወለደችንና በምትመግበን፣ ልዩ ልዩ ፍራፍሬዎችን፣ ያሸበረቁ አበቦችንና ሣሮችን ስለምታበቅለው ስለእኅታችን፣ ስለእናታችን መሬት የተመሰገንህ ሁን፡፡...
ጌታዬን አመስግኑት፤ ባርኩት፤ እያመሰገናችሁም በታላቅ ትሕትና አገልግሉት፡፡
ሰንበት- የስድስቱ ቀናት ሥራ ፍጻሜ፡- መጽሐፍ ቅዱስ "እግዚአብሔር የሠራውን ሥራ በሰባተኛው ቀን ፈጸመ፤" "የሰማይንና የምድርን መፍጠር ፈጽሞ፤" እግዚአብሔር በዚህ ቀን "ዐረፈ"፤ ቀደሰው፤ ባረከውም፡፡ እነዚህ በመንፈስ የተጻፉ ቃላት ታላቅ ትምህርትን ያዘሉ ናቸው፡፡
እግዚአብሔር በፍጥረት አማካይነት አማኝ በሙሉ ልብ የሚመካበት መሠረቱን ጣለ፤ ጽኑ ሆነው የሚኖሩትን ሕግጋቱንም ደነገገ፤ የእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ጽናትና ታማኝነት ምልክትና ዋስትና ናቸውና፡፡ ሰውም በበኩሉ ለዚህ መሠረት ታማኝነቱን ጠብቆ መኖርና ፈጣሪ በውስጡ የጻፋቸውን ሕግጋት ማክበር አለበት፡፡
ፍጥረት የተሠራው ዕለተ ሰንበትን በማሰብ፣ እግዚአብሔርን እንዲያመልክና ለእርሱ እንዲሰግድ ነው፡፡ አምልኮ በፍጥረት ሥርዓት ተዘግቧል፡፡ የአቡኑ ብሩክ ሕግ እንደሚለው፣ ምንም ነገር "ከእግዚአብሔር ሥራ" ማለትም ከአምልኮ መቅደም አይኖርበትም፡፡ ይህ እንግዲህ የሰውን ጭንቅ ትክክለኛ ቅደም ተከተል ይጠቁማል፡፡
ዕለተ ሰንበት የእስራኤል ሕግ ዕምብርት ነው፡፡ ትእዛዛቱን መጠበቅ፣ በፈጥረት ሥራው እንደ ተገለጸው ከእግዚአብሔር ጥበብና ፈቃድ መስማማት ነው፡፡
ስምንተኛው ቀን፡- ለእኛ ግን አዲስ ቀን ነግቶልናል፤ ይኸውም የክርስቶሰ ዕለተ ትንሣኤ ነው፡፡ ሰባተኛው ቀን የመጀመሪያውን ፍጥረት ይፈጽማል፡፡ ስምንተኛው ቀን አዲሱን ፍጥረት ይጀምራል፡፡ በመሆኑም የፍጥረት ሥራ የሚፈጸመው በታላቁ የድኅነት ሥራ ነው፡፡ የመጀመሪያው ፍጥረት ትርጉሙን የሚያገኘውና ከጫፍ የሚደርሰው፣ በሞገሱ ከመጀመሪያው ፍጥረት በሚልቀው፣ በክርስቶስ በሆነው በአዲሱ ፍጥረት ነው፡፡
ምን ጭ:- አዲሱ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ