4. አባትና እናትህን አክብር

አራተኛይቱ ትአዛዝ

አባትና እናትህን አክብር

“አባትህንና እናትህን አክብር፤ እግዚአብሔር አምላክህ በሚሰጥህ ምድር ዕድሜህ እንደረዝም” ዘጸ. 12፡12፤ ዘዳ. 5፡16

“… ይታዘዛቸውም ነበር” ሉቃ. 2፡ 51

ጌታ ኢየሱስ የዚህን “የእግዚአብሔር ትእዛዝ” አስፈላጊነት ያስታውሳል፡፡ ሐዋርያውም፣ “ልጆች ሆይ ለመላጆቻችሁ በጌታ ታዘዙ፤ ይህ ተገቢ ነውና፡፡ አባትህንና እናትህን አክብር (ይህ ትእዛዝ የተስፋ ቃል ያለበት የመጀመሪያ ትእዛዝ ነው፡፡) ይህንንም ብታደርግ ሁሉ ነገር ይሰምርልሃል፣ ዕድሜህም ይረዝማል ሲል ያስተምራል፡፡” ኤፌ.6፡1-3

በዚህ ትእዛዝ መሠረት መፈጸም ያለባቸው ተግባራት የተገለጹት አዎንታዊ በሆነ መልክ ነው፡፡ አራተኛው ትእዛዝ በተለይ የሕይወትን ክብርነት ጋብቻ፣ ምድራዊ ሀብትንና ንግግርን የሚመለከቱትን ቀጣይ ትዕዛዛት ያስተዋውቃል ከቤተ ክርሰቲያን ማኅበራዊ ትምህርት መሠረቶች አንዱንም የያዘ ነው፡፡

አራተኛው ትእዛዝ ልጆች ከወላጆቻቸው ጋር ስላላቸው ግንኙነት በቀጥታ ለልጆች የቀረበ ነው፡፡ ምክንያቱም ይህ ግንኙነት ከሁሉም በላይ በየትም ዓለም ያለ ነውና፡፡ እንደዚሁም የቅርብ ዝምድና ያላቸውም የቤተሰብ አባላትም ይመለከታል፡፡ ይህ ግንኙነት አረጋውያንንና አባቶችን ማክበር፣ ማፍቀርና ማመስገን ይጠይቃል፡፡ በመጨረሻም፣ ተማሪዎች መምህራንን፣ ሠራተኞች አሠሪዎቻቸውን፣ የበታች መሪዎቻቸውን፣ ዜጐች አገራቸውን የሚያስተዳድሩ ባለሥልጣናትን ማክበር እንዳለባቸው ይገልጻል፡፡

ይህ ትእዛዝ የወላጆችን፣ የአሰልጣኞችን፣ የመምህራንን፣ የመሪዎችን፣ የዳኞችን፣ በማስተዳደር ሥራ ላይ የሚገኙ ሰዎችን፣ በሌሎች ሰዎች ላይ ወይም በማሕበር በሚኖሩ ሰዎች ላይ ሥልጣን ያላቸው ግለሰቦች ኃላፊነት ጭምር ይመለከታል፡፡

አራተኛውን ትእዛዝ ማክበር ዋጋን ያስገኛል፤ ይህም ማለት “አባትህንና እናትህን አክብር፤ እግዚአብሔር አምላክ በሚሰጥህ ምድር ዕድሜህ እንዲረዝም፡፡” ዘጸ. 2ዐ፡12፤ ዘዳ. 5፡16 ይህን ትእዛዝ ማክበር ከመንፈሳዊ ሀብት ጋር የሰላምና የብልፅግና ምድራዊ ፍሬዎችንም ያስገኛል፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ይህን ትእዛዝ አለማክበር በማሕበረሰቦችና በግለሰቦች ላይ ከባድ ጉዳትን ያስከትላል፡፡

ቤተሰብ በእግዚአብሔር ዕቅድ ውስጥ

የቤተሰብ ባሕርይ

የባለትዳሮች ማህበረሰብ የተመሠረተው ባልና ሚስት በሚያደርጉት ስምምነት ነው፡፡ ጋብቻውና ቤተሰብ የተሰረቱት ለባልና ሚስት ጥቅም፣ እንደዚሁም ልጆችን ለማፍራትና እነሱን በትምህርት ለማሳደግ ነው፡፡ የባልና የሚስት መዋደድና የልጆች መወለድ በእነዚህ ቤተሰቦች አባላት መካከል ግለሰባዊ ግንኙነቶችና መሰረታዊ ኃላፊነቶች ይፈጥራሉ፡፡

በጋብቻ ቃል ኪዳን የተሳሰሩ ወንድና ሴት ከነልጆቻቸው ቤተሰብ ይሆናሉ፡፡ ይህ ተቋም በመንግሥት መታወቅን ቢያገኝም ቅሉ ቀድሞውንም የነበረ ነው፡፡ የተለያዩ ቤተሰባዊ ግንኙነቶች የሚመዘኑበት መነሻ ነጥብም ተደርጐ መወሰድ አለበት፡፡

እግዚአብሔር ወንድና ሴትን በመፍጠር ሰብአዊ ቤተሰብን አቋቁሞ መሰረታዊ ሕግን ሰጠው፡፡ የቤተሰብ አባላት እኩል የሆነ ሰብአዊ ክብር ያላቸው ሰዎች ናቸው፡፡ ቤተሰብ የአባላቱንና የሕብረተሰብን የጋራ ጥቅም የሚያራምዱ የተለያዩ ኃላፊነቶች፣ መብቶችና ግዴታዎች አሉት፡፡

ክርስቲያናዊ ቤተሰብ

“ክርስቲያናዊ ቤተሰብ የቤተ ክርስቲያን ሱታፌ የሚገጥበትና ወደ ፍጻሜ የሚደርስበት ዋና መሠረት ስለሆነ “ታናሹ ጉባኤ” ተብሎ ሊጠራ ይችላል፣ መጠራትም አለበት፡፡” በአዲስ ኪዳን ውስጥ ጉልህ ሆኖ እንደሚታየው ክርስቲያናዊ ቤተሰብ በቤተክርስቲያን ዘንድ ብቸኛ የሆነ ታላቅነትን የያዘ የእምነት፣ የተስፋና የፍቅር ማኅበር ነው፡፡

ክርስቲያናዊ ቤተሰብ የሰዎች ህብረት ሲሆን፣ በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ መካከል ያለ አንድነት ምልክትና አምሳል የሆነ የሰዎች ማህበር ነው፡፡ ልጆችን የማፍራት እንዲሁም እነሱን የማሳደግና የማስተማር ጉዳይ በሚመለከት ክርስቲያናዊ ቤተሰብ የእግዚአብሔርን የመፍጠር ስራ ያንጸባርቃል፡፡ ክርስቲያናዊ ቤተሰብ በክርስቶስ ጸሎት መስዋዕት ለመሳተፍ ተጠርቷል በክርስቶስ ጸሎትና መሥዋዕትም እንዲካፈል ተጠርቷል፡፡ ክርስቲያናዊው ቤተሰብ በየዕለቱ የሚደግመው ጸሎትና የሚያነበው ቃለ እግዚአብሔር የፍቅር ሥራዎችን ይሠራ ዘንድ ያበረታቱታል፡፡ ክርስቲያን ቤተሰብ የስብከት ወንጌልና የተልእኮ ስራ አለበት፡፡

በቤተሰብ ውስጥ ያሉ ግንኙነቶች የመቀራረብ ስሜቶችን፣ የመፈቃቀርንና የመፈላለግን መንፈስን ይፈጥራሉ፡፡ ይህም የቤተሰቡ አባላት እርስ በእርስ የሚኖሩአቸው መከባበር ውጤት ነው፡፡ ቤተሰብ “ተጋቢዎች ሀሳባቸውን የሚካፈሉበት፣ በጋራ የሚወያዩበት እንዲሁም የልጆችን አስተዳደግ በተመለከተ በውዴታ የሚደረግን ትብብር ከግብ የማድረስ ጥሪ ያለበት ከፍ ያለ ክብር የተሰጠው ማኅበር ነው፡፡”