ስምንተኛይቱ ትእዛዝ - በባልንጀራህ ላይ በሐሰት አትመስክር

ስምንተኛይቱ ትእዛዝ

በባልንጀራህ ላይ በሐሰት አትመስክር

ደግሞ ለቀደሙት “በውሸት አትማል፤ ነገር ግን መሐላዎችህን ለጌታ ሥጥ” ማቴ. 2፡33 ተብሎአል፡፡

ስምንተኛው ትእዛዝ ከሌሎች ጋር በሚኖረን ግንኙነት እውነትን እንዳናዛባ ይከለክለናል፡፡ ይህ ሥነ ምግባራዊ መመሪያ የሚፈሰው እውነት ለሆነና እውነትንም ለሚሻ አምላኩ ይመሰክር ዘንድ ለተቀደሰው የቀረበለት ጥሪ ነው፡፡ በቃል ወይም በተግባር በእውነት ላይ የሚፈጸሙ በደሎች ለትክክለኛ ሥነ ምግባር በጽናት አለመቆምን ይገልጻል፡፡ እነዚህ በደሎች በእግዚአብሔር ላይ የተቃጡ መሠረታዊ አለመታመኖች ናቸው፤ ስለዚህም ከዚህ አንጻር የቃል ኪዳኑን መሠረቶች ያዳክማሉ፡፡

በእውነት ውስጥ መኖር

እግዚአብሔር የእውነት ሁሉ ምንጭ መሆኑን ብሉይ ኪዳን ያረጋግጣል፡፡ ቃሉ እውነት ነው፡፡ ሕጉ እውነት ነው፡፡ የእርሱ “እውነተኛነት በዘመናት ሁሉ ይኖራል፡፡” መዝ. 119፡9ዐ እግዚአብሔር “እውነት” በመሆኑ የሕዝቡ አባላት በእውነት እንዲኖሩ ጠርቶአቸዋል፡፡

በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት መላው የእግዚአብሔር እውነት ተገለጠ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ “በጸጋና በእውነት ተሞልቶ፣” “የአለም ብርሃን” ሆኖ በመምጣቱ እርሱ እውነት ነው፡፡ “በእኔ የሚያምን በጨለማ አይኖርም” ይላል፡፡ የኢየሱስ ደቀ መዝሙር ሰውን “ነፃ የማያወጣና” የሚቀድስ እውነትን ለማወቅ ሲል ለቃሉ ይታመናል፡፡ ኢየሱስን መከተል ማለት አብ በራሱ ስም በላከውና ወደ “እውነት ሁሉ” በሚመራ “የእውነት መንፈስ” መኖር ማለት ነው፡፡ ኢየሱስ “ቃላችን አዎን አዎን ወይም አይደለም አይደለም ይሁን” ሲል ለእውነት ስለሚገባው የማይለወጥ ፍቅር ለደቀ መዛሙርቱ ትምህርትን ሰጥቷል፡፡

ሰው በባሕሪው ወደ እውነት ያዘነብላል፡፡ ስለዚህም እውነትን ለማክበርና ለእውነት ለመመስከር ይገደዳል፡፡ ይህ ማለት “ሰዎች ሁሉ በሰብአዊ ክብራቸው ምክንያት… በባህሪያቸውና በሕሊናቸው ግፊት እውነትን አንዴ ካወቁ በኋላ እሱን አጥብቆ በመከተል መላ ሕይወታቸውን እርሱ በሚጠይቀው መሠረት መምራት አለባቸው፡፡

እውነት በሰው ድርጊትና ንግግር እንደሚገለጽ ትክክለኝነት እውነተኝነት ከግብዝነት በማራቅ ፣ ቅንነት ወይም ሃቀኝነት ይባላል፡፡ እውነት ወይም እውነተኛነት እራስን በድርጊት ትክክል፣ በቃልም እውነተኛ በማድረግ ከሐሰት፣ ከማስመሰልና ከግብዝነት በማሳየት ምግባር ነው፡፡

“አንዱ ለሌላው እውነተኛ ስለመሆናቸው የጋራ መተማመን ባይኖራቸው ኖሮ ሰዎች በጋራ መኖር አይችሉም ነበር” እውነት ለሌላው የሚገባውን ዋጋ ይሰጠዋል፡፡ እውነተኛነት መገለጥ በሚገባውና ምስጢር ሆኖ መጠበቅ ባለበት ጉዳይ መካከል ያለ ትክክለኛ አማካይን ያከብራል፡፡ እውነተኛነት ቅንነትንና አስተዋይ ውሳኔ ይጠይቃል፡፡ ፍትሕን በተመለከተ “የክብር ጉዳይ እንደመሆኑ መጠን እውነቱን መግለጥ አንዱ ለሌላው ሊያደርገው የተገባ ነው፡፡”

የክርስቶስ ደቀ መዝሙር “በእውነት ለመኖር፣” ማለትም ከጌታ አርአያነት ጋር በሚስማማ ሕይወት በእርሱ በእውነት በመጽናት ለመኖር እሽታውን ይገልጻል፡፡ “ከእርሱ ጋር ኅብረት አለን ብንል፤ በጨለማም ብንመላለስ እንዋሻለን፤ እውነትንም አናደርግም፡፡”

ስለ እውነት መመስከር

ክስርስቶስ በጲላጦስ ፊት በቀረበ ጊዜ “… እርሱ ወደዓለም የመጣው ስለ እውነት ለመመስከር እንደሆነ” ያረጋግጣል፡፡ ስለዚህ ክርስቲያን ሰው “ስለ ጌታ ለመመስከር ማፈር የለበትም፡፡” ስለ እምነት መመስከር የሚያስፈልግበት ሁኔታ ሲያጋጥም ክርስቲያን ሰው “ቅዱስ ጳውሎስ በፈራጆቹ ፊት በተግባር ያሳየውን አብነት በመከተል” እምነቱን ያለማወላወል መግለጽ አለበት፡፡ ምእመን “በእግዚአብሔርና በሰው ፊት ነውር የሌለበት ሕሊና እንዲኖረው” ይገባል፡፡

ክርስቲያኖች በቤተ ክርስቲያን ሕይወት ውስጥ የማኖራቸው የተሳትፎ ሃላፊነት ወንጌልንና ከእርሱም የሚመነጩ ግዴታዎችን እንዲመሰክሩ ያስገድዳቸዋል፡፡ ይህ ምስክርነት በሥራዎችና በቃላት አማካይነት እምነትን ማስተላለፍ ነው፡፡ ምስክርነት እውነትን የሚያረጋግጥ ወይም እውነትን የሚያሳውቅ የጽድቅ ሥራ ነው፡፡

ክርስቲያኖች በሚኖሩበት ሥፍራ ሁሉ በሕይወታቸው አርአያነትና በቃላቸው ምስክርነት አማካይነት በጥምቀት የለበሱትን የአዲሱን ሰው የማሳየትና በሜሮን ያበረታቸዋን የመንፈስ ቅዱስን ኃይል የመግለጽ ግዴታ አለባቸው፡፡

ሰማዕታት ለእምነት እውነተኛነት የሚሰጥ የላቀ ምስክርነት ነው፡፡ ይህ ምስክርነት እስከሞት ድረስ ይዘልበቃል፡፡ ሰማዕት በፍቅር አማካይነት ከእርሱ ጋር ለተዋሐደውና ሞቶ ለተነሳው ክርስ”ተስ ይመሰክራል፡፡ ሰማዕት በእምነት እውነተኛነት እ ለክርስቲያናዊ አስተምህሮ ምስክርነቱን ይሰጣል፡፡ ሰማዕት ሞትን በልበ ጠንካራነት ይቋቋመዋል፤ “ወደ እግዚአብሔር መድረሻዬ ለሆኑት ለአውሬዎቹ ምግብ ልሁናቸው፡፡”

ቤተ ክርስቲያን ለእምነታቸው እየመሰከሩ እስከ ሕይታቸው ፍፃሜ የጸኑ ሰዎችን ታሪክ ከፍ ባለ ጥንቃቄ ሰብስባለች፡፡ እኒህ ናቸው እንግዲህ የሰማዕታታ ሥራዎች የሚባሉት፡፡ ፊደላት የተጻፉ የእውት መዝገቦች፡፡

የዚህ ዓለም ደስታ ወይም የዚህ ዘመን ግዛቶች ምንም አይጠቅሙኝም፤ ለእኔ ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር /እራሴን አዋሕድ ዘንድ/ ብሞት የምድር ዳርቻ ድረስ ከግዛት ይሻለኛል፡፡ ለእኛ ሲል የሞተውን ጌታ ላገኝ እፈልጋለሁ፡፡ ለእኛም ሲል ከሙታን የተነሳውን ጌታ ማግኘት እሻለሁ፡፡ የልደቴ ቀን ተቃርቧል… ጌታ ሆይ በዚች ዕለትና ሰዓት ጀምሮ ከሰማዕታትህ ጋር ስለቆጠርኸኝ እወድስሃለሁ፡፡ የታማኝነትና የእውነት አምላክ ሆይ የተስፋ ቃልህን ጠበቀሃል፡፡ በዚህ ምክንያትና ስለሁሉም ነገር አመሰግንሃለሁ፤ አከብርሃለሁ፡፡ ዘላለማዊ፣ ሰማያዊ፣ ሊቀ ካህናት በሆነው በውድ ልጅህ አማካይነትም ከፍ ከፍ አደርግሃለሁ፡፡ ከአንተና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በሆነው በእርሱ አማካይነት አሁንና ለመጪዎችም ዘመናት ክብር ለአንተ ይሁን፡፡ አሜን፡፡