Map St Joseph Cistercians

Top Panel

ለእግዚአብሔር ድምፅ ባእድ ያለመሆን

የቅዱስ ዮሴፍ ቦታና ክብር - የ 2005 ዓ.ም. የዓመታዊው ቅዱስ ዮሴፍ መስዋእተ ቅዳሴ ስብከት፡-

174ስለ ቅዱስ ዮሴፍ ታላቅነትና ለእኛ ስለሚሰጠን አብነታዊ ሕይወትና የአማላጅነቱ ጸጋ ለማየት ያግዘን ዘንድ በእግዚአብሔር ዘንድ ስላለን ቦታ ለማየት የሚያግዙን ነጥቦችን በማየት እንጀምር።

በእግዚአብሔር መንግስት ትልቅነታችን የሚለካው በምንድነው?

1. የመመረጥ ደረጃ (በምድር ላይ የሚሰጠን የሕይወት ዓይነት ነው)

2. የሚሰጥ የጸጋ ብዛት (ለተጠራንበት ሕይወት የሚያስፈልገን ጸጋ ነው)

3. የተሰጠንን ሕወትና ጸጋ ለመኖር የሚኖረን ትጋትና ታማኝነት ነው

ኢየሱስ 12 ሐዋርያት ከርሱ ጋር እንዲሆኑ ከሰው ዘር ሁሉ እነርሱን ከመምረጡ በፊት ሌሊቱን ሙሉ ሲጸልይ አደረ፤ይህንንም ዓለም ትቶ ወደ መጣበት ከመመለሱ በፊት እንዲህ አላቸው፡አባቴ እንደላከኝ እኔም ደግሞ እልካችኋለሁ፤እናንተን የሚሰማ እኔን ይሰማኛል፤እናንተን የሚያከብር እኔን ያከብራል፤ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱና ወንጌልን ለዓለም ሁሉ አብሥሩ፤እናንተ በምድር ላይ የምታስሩት በሰማይ የታሰረ ይሆናል፤በምድርም የምትፈቱት ሁሉ በሰማይም የተፈታ ይሆናል፤እኔ መርጫችኋለሁና፡፡ በዚህ አባባል ኢየሱስ በእግዚአብሔር መንግስት ከሌሎች ሰዎች በተለየ መልኩ በሐዋርያቱ ላይ ያሳረፈውን ክቡርና መለኮታዊ የሆነውን ኀላፊነት ያመለክታል፡፡ ይህም ኀላፊነት ለሐዋርያት በእግዚአብሔር መንግስት ዘላለማዊ መገለጫቸው ሆኖ ይኖራል፡፡ ከሱ ጋር ለመፍረድ በ12 ዙፋን ላይ እንደሚቀመጡም ይናገራል፡፡

icona-santa-famigliaይህንን ከቅዱስ ዮሴፍ ጥሪ ጋር ስናነጻጽረው የሱ ጥሪ ይበልጥ የላቀ ኀላፊነት  ሆኖ እናገኘዋለን፤ዮሴፍ በዚህ ምድር ከኢየሱስ አጠገብ ሆኖ ሰማያዊ አባቱን እንዲወክል እግዚአብሔር ጠራው፤ድንግልና እናት ለሆነችም እጮኛ፣ለኢየሱስም አባት እንዲሆን አ/ር መረጠው፤ኢየሱስ በግርግም ከተወለደበት ጊዜ አንሥቶ ዮሴፍ ከኢየሱስ ጋር ይሆናል፤እንደ ሐዋርያት 3 ዓመታት ብቻ ሳይሆን ሳይለየው በሕይወቱ ዘመን ሁሉ ከርሱ ጋር ይሆናል፡፡ሐዋርያት ከብዙ ሕዝብ ጋር ሆነው ኢየሱስን ይከተሉ ነበር፤ቅዱስ ዮሴፍ ግን ከኢየሱስ ጋር አብሮት   ይኖር ነበር፤ኢየሱስና ዮሴፍም (እንደ አባቱ) ፊት ለፊት ለብቻቸው በማንኛውም ጊዜ ይነጋገሩ  ነበር፤ከነርሱ በላይ ዮሴፍ ኢየሱስን ያውቅ ነበር፤እምነትህ ጎደሎ ነው ተብሎ አያውቅምና፡፡

ኢየሱስ ቤተክርስቲያንን ለሐዋርያት አደራ ሰጣት፤የቤተክርስቲያን መስራች የሆነው እሱ ግን ለዮሴፍ በአደራ ተሰጠው፤ለዚህ ማዕረግ ብቁዕ ለመሆን ዮሴፍ እጅግ ቅዱስ የሆነ ሕይወት የነበረው ሰው መሆን አለበት፤ምክንያቱም ማንኛውም ዕብራዊ አባት የቤተሰብ መሪ ስለሆነ ለቤተሰቡ አባላት ሁሉ በቅድስናው አርአያ መሆን አለበት፡፡ ስለዚህም የሱ ሕይወቱ ለኢየሱስና ለማርያምም አርአያ መሆን የሚችል ነበር፤ኢየሱስም ይህንን ጻድቅ ሰው እንደ ልጁ ያከብረው እንደነበረ መገመት አያስቸግርም፡፡ የሐዋርያት ሕይወት ለኢየሱስና ማርያም አርአያ መሆን የሚችል አልነበረም በአንጻሩ ከኢየሱስና ከማርያም ሕይወት መማር ነበረባቸው፡፡

ሐዋርያትን በተመለከተ ግን ደካሞች እንደሆኑና አንዳንድ ጊዜ መገሰጽም የሚየስፈልጋቸው እንደነበሩ በወንጌል እናገኛለን፤ዮሴፍን በተመለከተ ግን እንዲህ ዓይነት አናገኝም፤ስለዚህ የሴፍ እንከን የሌለው ኑሮ እንደኖረና ኢየሱስም ይህ ወይም ያ ሰው ካንተ በተሻለ መልኩ ለኔ አባት ሊሆን ይችላል ብሎ ከቶ ሊናገር አልቻለም፡፡ወንጌል ስለሱ የሚሰጠው ምስክርነት ‹‹እርሱ ጻድቅ ሰው ነበር›› የሚለውን ነው፡፡ እሱ ከማርያም ቀጥሎ ከሌሎች ቅዱሳን ሁሉ በላይ ከፍ በለ ደረጃ ላይ የሚገኝ ቅዱስ ነው፡፡

2 በሰማይ የሚኖረን ክብር የሚወሰነው እንደ ክርስቲያኖች በዚህ ምድር ላይ እንደጥሪያችን በሚሰጠን ጸጋና አጠቃቀሙ ላይ ነው፤ሐዋርያት ከሌሎች የላቀ የጸጋ ስጦታ ሲሰጣቸው እነርሱም ይህንኑ ጸጋ በአግባቡ ተጠቅመው በእግዚአብሔር መንግስት የክብር ቦታቸውን እንደያዙ መጽ.ቅ ይናገራል፡፡ በዘህም አንጻር ለቅዱስ ዮሴፍ የተሰጠው ጸጋና እሱም ከሐዋርያት በላይ የተሰጠውን ጸጋ በምልአት እንደኖረ መጽ.ቅ ይመሰክራል፡፡ ጸጋም በሕይወታችን እንዲበዛ የሚያደርገው ጸሎት ነው፡፡

3 በሰማይ የሚኖረን ክብር የሚወሰነው አንድ ክርስቲያን የተሰጠውን ጸጋ በተግባር ለተሰጠው ዓላማ ለመኖር በሚያሳየው ታማኝነት ነው፡፡ሐዋርያት በድፍረት እኛ ክርስቶስን እንደመሰልን እናንተም እኛን ምስሉ በማለት የተሰጣቸው ጸጋ በከንቱ እንዳልጠፋ ይመሰክራሉ፡፡

ቅዱስ ዮሴፍ ደግሞ ከሐዋርያት በላቀ መልኩ የሕወቱን ዘመን ሁሉ ከኢየሱስና ማርያም ጋር ስለኖረ ቀንና ሌሊትም ከኢየሱስ ጋር አብሮ በመኖሩም ሰማያዊውን ሕይወት ከኢየሱስ እያየ እሱን ከማንም በላይ እየተከተለ በመኖሩ ከሐዋርያትም በላይ እኔ እግዚአብሔርን ስለመሰልኩ እናንተም እኔን ምሰሉ ብሎ በሙሉ ድፍረት ይናገረናል፡፡

ሐዋርያት በኃጢአት ባርነት ለሚገኙ ነፍሳት ነፃነትን አበሠሩ፤ቅዱስ ዮሴፍ ግን ለቅድስት ድንግል ማርያና ለኢየሱስ የሚያስፈልጋቸውን እንክብካቤ አደረገ፡፡የቅዱስ ዮሴፍ ሕይወትና ሥራ ሙሉ በሙሉ ከኢየሱስና ከማርያም ጋር ግንኙነት ስላለው በእግዚአብሔር ፊት እጅግ ክቡር ነው፡፡በነርሱም አማካይነት የሰው ልጅ ሁሉ አገልጋይ ሆኖ ይቀርባል፡፡

በቅዱስ ዮሴፍ ሕይወት መከራና ችግሮቹ አንዱ ከሌላ በኋላ ተሰልፈውበታል

ቅ.ዱሴፍ ከአንድ መከራ ወደ ሌላ መከራ የሚያልፍ ሕይወት ቢያጋጥመውም በመከራዎቹ ውስጥ አይጨፈለቅም፤ ሁሉ ጊዜ መመሪያዎችን ከእግዚአብሔር በመቀበል አሸናፊ ሆኖ የሕይወቱን ጉዞ ይቀጥላል፡፡ይህ ከእግዚአብሔር የሚሰጠው መመሪያ አምኖ በእሺታ ተቀበሎ የሕይወቱ ክፍል የሚያደርገው አካል ከሌለ ጥቅመቢስ ይሆናል፡፡ ዮሴፍም ከእግዚአብሔር የተሰጠውን መመሪያ ተቀብሎ በሱ ሕይወቱን ለመምራት ፈቃደኛ ባይሆን ኖሮ የሱም የቤተሰቡም ሕይወት በተበላሸ ነበር፡፡በርግጥ ዮሴፍ እግዚአብሔርን ለማዳመጥም በሰማውም ቃል መሠረት ሥራውን ሁሉ ለማከነውን ፈቃደኛ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ስለዚህም ሁላችን በየኀላፊነታችን እግዚአብሔር መመሪያ ስለሚሰጠን ራሳችንና ከኀላፊነታችን ስር የሚገኙ ወገኖች ችግር ውስጥ እንዳይገቡ የእግዚአብሔርን ቋንቋ ለይተን ማወቅ ያስፈልገናል፡፡

 ይህ ለቅዱስ ዮሴፍ የተሰጠው መመሪያ የመጨራሻ ሳይሆን የመጀመሪያው ነው፤እንደየአስፈላጊነቱ በየምዕራፉ የሚመሩት መረጃዎች ሊሰጡት ነው፤በየምዕራፉም የሚሰጠው መመሪያ ዮሴፍን ራሱንና ቤተሰቡን ከአደጋ በራቀና በቀና መንገድ እንዲመራ የታቀደ ነው፡፡ ስለዚህ የመጀመሪያው መመሪያ እጮኛውን ማሪያምን ምንም ሳይፈራ ወደ ቤቱ እንዲወስዳት ይመራዋል፤ በሁለተኛው መመሪያ ቤተሰቡን ወደ ግብፅ እንዲያሽ ያሳየዋል (ሄሮድስ ተንኮል ስላሰበ)፤ ከግብፅ እንዲመለስ በይሁዳ እንዳይኖርና በናዝረት እንዲኖር ይመራዋል፤እያንዳንዳችን ሕይወታችን በዮሴፍ ሕይወት አድርገን እንመልከት፡፡ ጋብቻለሚፈልግ መመሪያ ይሰጠዋል፣በጋብቻ ለሚኖር መመሪያ ይሰጠዋል፣ለአሠሪና ሠራተኛም መመሪያ ይሰጠዋል፣ አመፀኛና ለእግዚአብሔር በእድ ካልሆን መመሪያውን አንስተውም

ዮሴፍ እንግዲያውስ ከአንድ ችግር በኋላ ሌላ ችግር ይመጣበታል፡ቢሆንም ከእነዚህ ችግሮች የሚወጣበትን መንገድ እግዚአብሔር ሲነግረው1ቆሮ 10፡13 ሁሊ ጊዜ ይሰማል፤በሰማውም ይመራል፡፡ ታዲያ ይህ ሰው ሳይሳሳት እግዚአብሔርን ሊያዳምጥና ሊረዳው የቻለበት ምክንያት ምንድነው? የዚህን ጥያቄ መልስ በወንጌል እናገኛለን፤ዮሴፍ ጸድቅ ሰው መሆኑን ይነግረናል፤ዮሴፍ እግዚአብሔርን ያውቀዋል ለሚያውቀውም እግዚአብሔር ይታዘዛል፣ዮሴፍ ለእግዚአብሔር በእድ አይደለም፤ ከእግዚአብሔር ጋር ቤተሰብ የሆነ ሰው ነው፤መከራ ሲመጣ በዚው በመከራ ውስጥ እግዚአብሔር ሲናገር ዮሴፍ የእግዚአብሔርን ድምፅ ለይቶ ማዳመጥ የሚችልና የሰማውንም በተግባር የሚፈጽም ነው፡፡ ዮሴፍ ከመከራው ፊት የእምነት ሰው ነው፤መከራዎቹም ሲያጋጥሙት በእምነት መልስ ይሰጣል፤በእምነት መልስ መስጠቱ እግዚአብሔር በሱ ሕይወት ገብቶ ወደ ቀና መንገድ እንዲመራው ያደርገዋል፡፡

ይህም ማለት ዮሴፍ የጸሎት ሰው ነው ማለት ነው፤ከእግዚአብሔር ጋር ሊኖረን የሚገባንን ዝምድና በጸሎት አማካይነት የምንቀጥል ከሆነና በተራው ዕለታዊ ሕይወታችን እግዚአብሔር እንዲመራን የምንፈቅድ ከሆነ ከለመድነው ወጣ ያለ ነገር ቢመጣና ዓለምም ሁሉ በላያችን የሚወድቅብን ብመስለንም እንኳን የሚናገረንን የእግዚአብሔርን ቃል ለይተን ልንሰማና በእምነት የሆነ መልስ ሰጥተን እግዚአብሔር በሚፈልገውና በትክክለኛው የሕይወት ጎዳና ልንጓዝ እንችላለን፡፡

ሁላችን የእምነት ሰዎች ብንሆንም የየዕለቱ ሕይወት በማስተዋል ካየን በድንገትና በትግል የታጀበ ነው፤እምነት ያለቸውና የእግዚአብሔር መንፈስ የሚመራቸው ሰዎች ይህን ያህል ጥንቃቄና እግዚአብሔርን ማዳመጥ የሚያስፈልቸው ከሆነ እምነት የሌላቸውና የማይጸልዩ ማለፍ የሚገባቸው ችግር ሲያጋጥማቸው ምን ሊሆኑ ነው? እግዚአብሔር ትቶኛል፣እግዚአብሔር አይሰማኝም ማለት ይጀምራሉ፤እውነቱ ግን እግዚአብሔርን የማይሰሙትና የተውት እንደዚያ የሚሉ ሰዎች ናቸው፡፡ አመጽን በተውነው መጠን መንፈሳዊ ጆሮአችን ለእግዚአብሔር ድምፅ ስለሚከፈት በዕለታዊ ኀላፊነታችን አመጽን እያስወገድን እንደ ቅዱስ ዮሴፍ በጽድቅ መንገድ እንመራ፡፡

ይትባረክ እግዚአብሔር በኩሉ ግብሩ፡፡    

አባ ወልደትንሣኤ (ሲታዊ)    

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።