ዜና እረፍት ክቡር አባ ኃይለማርያም ተኽለማርያም
- Category: ዜናዎች
- Published: Tuesday, 10 November 2020 09:33
- Written by Super User
- Hits: 1043
- 10 Nov
ክቡር አባ ኃይለማርያም ተኽለማርያም ዘማኅበረ ሲታውያን በተወለዱ በ101 ዓመት እድሜያቸው ጥቅምት 29 ቀን 2013 ዓ.ም. በሰላም አርፈዋል።
ነፍሰኄር አባ ኃይለማርያም ሰኔ 30 ቀን 1911 ዓ.ም. በዓደንገፎም - ሠገነይቲ ከአቶ ተኽለማርያም ተስፋማርያም እና ከወ/ሮ ለተኺዳን ተኽለማርያም ተወለዱ። በሠገነይቲ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርታቸውን ከጨረሱ በኋላ በ18 ዓመት እድሜያቸው የከረን ዘርአክህነት በመግባት በቀጣይነትም የፍልስፍናና የነገረ መለኮት ትምህርታችውንና ሕንጸት ተከታትለው በ29 ዓመት እድሜያቸው በደብረ ቅዱስ ሚካኤል ከረን የካቲት 7 ቀን 1940 ዓ.ም. በአቡነ ኪዳነማርያም ካሣ ሢመተ ክህነት ተቀበሉ። ከዚህም በኋላ ለስምንት ዓመታት በተለያዩ ቁምስናዎች ቆሞስ ሆነው ካገለገሉ በኋላ በአቡናቸው ፈቃድና ምርቃት ሚያዝያ 6 ቀን 1948 ዓ.ም. ወደ ሲታውያን ማኅበር ገቡ።
በመቀጠልም በማኅበሩ ሂደት ወደ ጣልያን ሄደው በመስከረም ወር 1949 ዓ.ም. “አባ ኃይለማርያም” በሚል ስመ ምንኩስና የተመክሮ ዓመት ጀመሩ፤ በዓመቱ የመጀመሪያ የምንኩስና መሐላ አድርገው ወደ አገራቸው አሥመራ ተመልሰው መስከረም 21 ቀን 1954 ዓ.ም. በደብረ ፍልሰታ ገዳመ ሲታውያን የመጨረሻ መሐላቸውን በማድረግ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በተመደቡበት ሁሉ እያገለገሉ ቆይተዋል። በነዚህ መጀመሪያ ዓመታት “ሕጊ ኣቡነ ቡሩኽ” ወደ ትግርኛ ተርጉመው ለማሳተም የበቁ ሲሆን ካላቸው ጥዑመ ዜማና የግእዝ ቋንቋ ስጦታና ችሎታ ብዙዎችን አስተምረዋል።
በመጨረሻው የእድሜያቸው ሂደት ውስጥ አሥመራና ከረን ተመድበው በማገልገል የመጨረሻዎቹን ስድስት ዓመታት በአሥመራ ገዳም አሳልፈዋል። ስለዚህ በክህነት 72 ዓመታት፣ በምንኩስና ደግሞ 63 ዓመታት፣ ባጠቃላይ እድሜያቸውም 101 ዓመታት ሆኗቸው ከአረጋዊነትና ከድካም ካልሆነ በስተቀር ፍጹም የጎላ ሥቃይ ሳይሠቃዩ የሆነውን ሁሉ በትዕግሥትና በምስጋና ሆነው በመነኮስት ወንድሞቻቸው ተከበው በሰላም አረፉ።