Map St Joseph Cistercians

Top Panel

“ሞትን ሳንፈራ ልንጋፈጠው የምንችለው በትንሣኤ በማመን ብቻ ነው!”

ሞትን ሳንፈራ ልንጋፈጠው የምንችለው በትንሣኤ በማመን ብቻ ነው!”

wwwርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ የካቲት 2/2014 ዓ. ም በጳውሎስ 6ኛ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ውስጥ ለተገኙት ምእመናን እና ነጋዲያን የተለመደውን ሳምንታዊ የረቡዕ ዕለት የጠቅላላ ትምሕርተ ክርስቶስ አስተምህሮአቸውን አቅርበዋል። ቅዱስነታቸው በአስተምህሮአቸው፣ በፍርሃት ሳንሸነፍ የሞትን ገደል መጋፈጥ የምንችለው በትንሣኤ በማመን ብቻ እንደሆነ አስገንዝበዋል።

ክቡራት እና ክቡራን፣ የቅዱስነታቸውን አስተምህሮ ትርጉም ሙሉ ይዘቱ እንደሚከተለው እናቀርብላችኋለን፥  

ውድ ወንድሞቼ እና እህቶቼ፣ እንደምን አረፈዳችሁ!

ባለፈው ሳምንት በቀረበው የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ፣ በቅዱስ ዮሴፍ ላይ በድጋሚ በመመሰጥ፣ በቅዱሳን አንድነት ትርጉም ላይ ማሰላሰላችን ይታወሳል። ከዚህ በመነሳት በዛሬው አስተምሮዬ ክርስቲያኖች ለቅዱስ ዮሴፍ ዘወትር ያላቸውን ልዩ ክብር እና የመልካም ሞት ባልደረባነቱን ማየት እፈልጋለሁ። ክርስቲያኖች ለቅዱስ ዮሴፍ የሚሰጡት ክብር የሚጀምረው ከናዝሬት ቤቱ ከመሰናበቱ በፊት በቅድስት ድንግል ማርያም እና በኢየሱስ ክርስቶስ እንክብካቤ ሲደረግለት ቆይቶ እንደሞተ በማሰብ ነው።

የቀድሞ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት በነዲክቶስ 15 ከዛሬ አንድ መቶ ዓመት በፊት ባቀረቡት አስተምህሮ፣በቅዱስ ዮሴፍ በኩል ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንቀርባለን፣ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በኩል ደግሞ ወደ ቅድስና ምንጭ ወደ ሆነው ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ እንሄዳለንበማለት ማስተማራው ይታወሳል። ለቅዱስ ዮሴፍ የምንሰጠውን ክብር ለማበረታታት በመፈለግም እንዲህ በማለት መክረውናል፥ ቅዱስ ዮሴፍ ለሞት በተቃረበበት ወቅት በኢየሱስ ክርስቶስ እና በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በኩል ዕርዳታ የተደረገለት በመሆኑ፣ በሞት ለሚለዩት በሙሉ የመልካም ሞት ባልደረባ እንደሆነ ተደርጎ ሊቆጠር የሚገባው በመሆኑ፣ ሐዋርያዊ አስተማሪዎች በአስተምህሮአቸው በኩል ምዕመናንን ለማበረታታት ካላቸው ከፍተኛ ፍላጎት የተነሳ፣ ምእመናንን የሚያበረታቱ ማኅበራትመልካም ሞትየቅዱስ ዮሴፍ ሕልፈትእናበሞት ለሚለዩን ሰዎች እንዲሆንበሚሉ ስያሜዎች ተቋቁመዋል። (የር. . በነዲክቶስ 15 ሐዋርያዊ የግል ውሳኔ፣ ሐምሌ 18/1912 . )

ውድ ወንድሞቼ እና እህቶቼ! ምናልባት አንዳንድ ሰዎች ይህ አስተምህሮ እና ርዕሥ ያለፈ ታሪክ ብቻ እንደሆነ ያስቡ ይሆናል። ነገር ግን ከሞት ጋር ያለን ግንኙነት የሚያልፍ ሳይሆን ዘወትር ከእኛ ጋር የሚቆይ እና የሚዘልቅ ነው። ምናልባትየምቾት ሕይወትባሕል ይህን ሐቅ ሊሰውርብን ይችላል። ነገር ግን በዓለማችን ውስጥ የገባው የኮሮርና ቫይሬስ ወረርሽኝ በሚያስደንቅ መልኩ እውነቱን ገሃድ አድርጎታል። በርካታ ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን ከጎናቸው መሆን ባልቻሉበት ሁኔታ የሚወዷቸውን በሞት አጥተዋል። ይህም ሞትን በወጉ ተቀብለን እንዳናስተናግድ አድጎናል።

የሞትን እና ፍርሃቱን ማስወገድ እንደምንችል በማመን እራሳችንን እናታልላለን። በዚህ ምድር የምንኖረው ለተወሰነ ጊዜ ብቻ መሆኑን ለመርሳት ሁሉ ጥረት እናደርጋለን። ነገር ግን የክርስትና እምነት የሞት ፍርሃትን የሚያስወግድ ሳይሆን ፊት ለፊት እንድንጋፈጠው የሚረዳን ነው። የሞትን ምስጢር በጉልህ እንዳናይ የሚያሳየን እውነተኛው ብርሃን የመጣው ከኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ነው። ይህን በማስመልከተ ሐዋርያው ጳውሎስ እንዲህ ብሎ የጻፈውን እናገኛለን፥ነገር ግን ክርስቶስ ከሞት እንደተነሳ የምናስተምር ከሆነ ከእናንተ አንዳንዶቹከሞት መነሳት የለምእንዴት ይላሉ? ከሞት መነሳት ከሌለማ ክርስቶስ ከሞት አልተነሳም ማለት ነው! ክርስቶስ ከሞት ካልተነሳ የእኛም ትምህርት ሆነ የእናንተም እምነት ከንቱ መሆኑ ነው!’ (2ቆሮ. 15:12-14)

ውድ ወንድሞቼ እና እህቶቼ! በፍርሃት ሳንሸነፍ የሞትን ገደል መጋፈጥ የምንችለው በትንሣኤ በማመን ብቻ ነው። ይህ ብቻ አይደለም! የሞትን አዎንታዊ ሚናንም መመልከት እንችላለን። በኢየሱስ ክርስቶስ ምሥጢር የተገለጠውን ሞት ማሰብ ሕይወትን በአዲስ ዓይን እንድንመለከተው ያግዘናል። ስለዚህ አንድ ቀን እንደምንሞት የምናውቅ ከሆነ ለራስ ብቻ በማሰብ ብዙ ሃብት ማካበት ዋጋ የለውም። ማካበት ያለብን ቸርነትን፣ ያለንን ከሌሎች ጋር መጋራትን እና ምን እንደሚያስፈልጋቸው አለመርሳት ነው። ከወንድም ወይም ከእኅት፣ ከጓደኛ ወይም ከዘመድ ጋር በእምነት ጉዳይ ላይ መጨቃጨቅ ዋጋ የለውም፤ ምክንያቱም አንድ ቀን በሞት ስለምንለያቸው ነው። ከሞት በፊት መስተካከል ያለባቸው ብዙ ጉዳዮች አሉ። ያለ ቂም እና ያለ ጸጸት ታርቀው መሞት መልካም ነው! ቅዱስ ወንጌል፣ ሞት እንደ ሌባ እንደሚመጣ ይነግረናል። ሞትን በቁጥጥር ስር ለማዋል ብንሞክር እና ስለ ራሳችን ሞት እንኳን ማቀድ ብንጀምር ስህተት እንጂ ምንም ዋጋ አይኖረውም።

እኛ ክርስቲያኖች ሞትን በሁለት መንገድ እንገነዘበዋለን። የመጀመሪያው ከሁሉ በፊት ሞት ማምለጥ የምንችለው ጉዳይ አይደለም። ስለዚህ የታመሙትን ለመፈወስ በሰው የሚቻለውን ሁሉ ካደረግን በኋላ ሞት የማይቀር በመሆኑ፣ በሕጋዊ መንገድ የሕመምተኛውን ፍላጎት በሚያከብሩ ሰዎች ውሳኔዎች መደረግ አለባቸው። (የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ . 2278) ሁለተኛው የክርስቲያን ግንዛቤ የሞት ዓይነትን፣ ሕመምን እና ስቃይን ይመለከታል። በእርግጥ በመድሐኒት አማካይነት ሊሰጥ ለሚሞከር እርዳታ ምስጋናን ልናቀርብ ይገባል።የማስታገሻ እንክብካቤበሚባለው ዘዴ በኩል በሕይወቱ የመጨረሻ ሰዓት ላይ ለሚገኝ እያንዳንዱ ሰው በተቻለ መጠን ሰብዓዊ በሆነ መንገድ ድጋፍ ማድረግ ይችላል። ነገር ግን ይህን ድጋፍ፣ ተቀባይነት ከሌለው በሕክምና ዕርዳታ አማካይነት ነፍስን ለማሳረፍ ከሚደረግ ጥረት ጋር እንዳናደናግር መጠንቀቅ ያስፈልጋል። በሞት አፋፍ ላይ የሚገኙትን ሰዎች ወደ ሞት መሸኘት ይኖርብናል እንጂ ለሞት እንዲበቃ ማመቻቸት የለብንም። አቅመ ደካማ ለሆኑት በተለይም አረጋውያን እና ሕመም ላይ የሚገኙ ሰዎች የመንከባከብ እና የመታከም መብታቸው ሁል ጊዜ ቅድሚያ ሊሰጠው እንደሚገባ መጠቆም እፈልጋለሁ፣ በእርግጥም በሕይወት መቆየት እንጂ መሞት መብት አይደለም። ሞት ደግሞ በጸጋ መቀበል ያለብን እንጂ በግድ መቀበል ያለብን ክስተት አይደለም። ይህ ስነ-ምግባራዊ መርህ ክርስቲያኖችን ወይም አማኞችን ብቻ ሳይሆን ሁሉንም ሰው ይመለከታል።

የሞትን ምስጢር በመልካም መንገድ እንድንኖርበት ቅዱስ ዮሴፍ ይርዳን! ለክርስቲያን መልካም ሞት መሞት በዚያች የመጨረሻዋ የሕይወታችን ሰዓት ወደ እኛ የሚቀርበውን የእግዚአብሔር ምሕረት የምናገኝበት ልምድ ነው። ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በምናቀርበው ጸሎታችን፣ "በሞታችን ዕለት" ወደ እኛ እንድትቀርብ እንለምናታለን። በዚህም ምክንያት፣ ለሟች እና የሐዘን ሰለባ ለሆኑት በሙሉ በኅብረት ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በመጸለይ የዛሬውን የትምህርተ ክርስቶስ አስተምሮዬን እደመድማለሁ።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን  

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።