ለእውነት ክፍት መሆን ይገባል
ራድዮ ቫቲካን - ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቤኔዲክቶስ በቼክ ሪፐብሊክ አገር አቀፍ አሥራ ሦስተኛ ሐዋርያዊ ጉብኝት ፈጽመው ከትናንትና በስቲያ ወደ ካስተል ጋንደልፎ ሐዋርያዊ መንበራቸው መመለስቻው ታውቋል።
ቅዱስ አባታችን ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቤኔዲክቶስ ከቼክ ሪፐብሊክ ርእሰ ከተማ ፕራግ አውሮፕላን ማረፍያ ሲነሡ አሸናኘት ላደረጉላቸው የቼክ ሪፐብሊክ የሃይማኖት እና የመንግሥት ከፍተኛ ባለስልጣናት ንግግር ያደረጉ ሲሆን፤ ከአውሮፕላን ማረፍያ ሲነሡ መለኮታዊ ቁንጅና ለዓለም እንዲያንጸባርቅ ለእውነት ክፍት ትሆኑ ዘንድ እመኛለሁ ብለዋል ።
ቼክ ሪፐብሊክ የተባረከች ሃገር ናት ምክንያቱም አንጋፋዎች ሚስዮናውያን እና ሰማዕታትን ያበቀለች ቅድስት የክርስትያን እሴቶች አቀፍ ሀገር ናት ሲሉ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቤኔዲክቶስ ቼክ ሪፐብሊክን አወድሰዋል።
ቼክ ሪፐብሊክ በኮሚኒስት አገዛዝ ሥር በነበረችበት ወቅት የተገደለችው ቅድስት አኘሰ ዘቦኤሚያ እና በስታራ ቦስላቭ ሰማዕት የሆነውን ቅዱስ ቬንሰስላው አስታውሰዋል።
ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቤኔዲክቶስ ከሀገሪቱ ሦስት የክርስትያን ማኅበረሰቦች ተውካዮች ጋር ያደረጉትን ውይይት ዘክረው በክርስትያኖች መካከል ዘወትር ውይይት ማካሄድ ተኪ የሌለው አስፈላጊ ነገር መሆኑን ገልጸዋል።
እንዲሁም ከቼክ ሪፐብሊክ ወጣቶች ጋር ያካሄዱት ግንኙነትን አስታውሰው፡ ወጣቶቹ በሀገሪቱ የክርስትና እሴቶች ላይ ተመርኩዘው ሀገሪቱን ለማነጽ ዓቢይ ተስፋ እንዳላቸው በመጠቆም ፈላስፋ ፍርንስ ካፍካንም በማጣቀስ የፍጥረት መልካምነትን የያዘ ሰው ከቶ አያረጅም ብለዋል።
ዓይናችን የእግዚአብሔርን ፍጥረት፡ አእምሮአችን ደግሞ እውነትነቱን ለማየት ክፍት የሆኑ ወጣቶች ሆነን ለመቅረት እና መኮታዊ ቆንጆነት በማነጽ ለመጪው ትውልድ መልካም እና የተባረከ ባህል ለመተው ተስፋ አለን ማለት ነው ሲሉ ቅዱስ አባታችን ቤኔዲክቶስ አመልክተዋል ።
በመጨረሻም በቼክ ቋንቃ “አት ፕራዘስክ ጀዙላትኮ፡ እግዚአብሔር ቼክ ሪፐብሊክን ይባርክ” ብለዋል ።
የቼክ ሪፐብሊክ መንግስት ፕሬዝዳንት ክላውስ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቤኔዲክቶስ በቼክ ሪፐብሊክ ያካሄዱት ሐዋርያዊ ጉብኝትን አመስግነው ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ለሀገሪቱ ሕዝብ አዲስ ተስፋ መስጠታቸውን ገልጸው የቸሩትን አባታዊ ምክር ተግባራዊ ለማድረግ እንጥራለን ብለዋል።
ፕሬዝዳንት ክላውስ አያይዘውም የርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት አቋም በፖለቲካ ረገድ ሲታይ በሁሉም ወይም በአብዛኞዎቹ ትክክለኛ እና ተቀባይነት ያለው ነው ካሉ በኋላ የቼክ ሪፐብሊክ ሕዝብ መሠረታዊ የስልጣኔ እና ክርስትና መርሆችን እንዲከተል ያሰሙት ንግግር ተቀባይነት ያለው ስለሆነ ይህንኑ ተግባራዊ እንዲሆን እኔ ራሴ አርአያ ለመሆን እጥራለሁ ብለዋል።
ቅዱስ አባታችን ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ቤኔዲክቶስ በቼክ ሪፐብሊክ ያካሄዱት ሐዋርያዊ ጉብኝት ስኬታማ መሆኑን እና የሀገሪቱ ሕዝብም በዚሁ ጉብኝት በእጅጉ መደሰቱን የቼክ ሪፐብሊክና የውጭ መገናኛ ብዙኀን ዘግበዋል ።
Last Updated (Thursday, 01 October 2009 22:54)












Comments
RSS feed for comments to this post.