-
Last Updated on 09 August 2011
-
Hits: 935
ቫቲካን ራድዮ - ቅ.አ.ር.ሊ.ጳ ቤኔዲክቶስ 16ኛ ለበጋ ዕረፍት ከሚገኙበት ከካስተል ጋንደልፎ ሐዋርያዊ አደራሽ ትናንትና ረፋዱ ላይ ከተለያዩ ክፍለ ዓለማት የመጡ ነጋድያንና የአካባቢው ምእመናን በተገኙበት የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎት ከማሳረጋቸው በፊት ዘወትር እንደሚያደርጉት የዕለቱን ቃለ ወንጌል በመመርኮዝ አስተምህሮ አቅርበዋል። በዓለማችን በተለይ ደግሞ በመካከለኛው ምሥራቅ የተከሰተውን ሰብአዊ ቀውስ አመልክተውም በሶርያ ሰላም እንዲነግሥ ተባብሮ የመሥራትና የመቻቻል መንፈስ እንዲዘወተር፤ በሊቢያ ላይ የሚፈጸመው ዓመጽም በቶሎ እንዲቆም ጥሪ አቅርበዋል፣
ቅዱስነታቸው ያቀረቡት አስተምህሮ የሚከተለው ነው፡- ውድ ወንድሞቼና እህቶቼ በዛሬው እሁድ ወንጌል ኢየሱስ ሕዝቡን አሰናብቶ ሊጸልይ ብቻውን ወደ ተራራ እንደወጣና መላውን ሌሊት ሲጸልይ ማደሩን እናነባለን፣ ጌታ እንዲህ በማድረጉ የሚያስተምረን ነገር አ፤ በመጀመርያ እርሱ ከአባቱ ጋር የነበረውን አንድነት ሲያሳይ በሌላ በኩል ደግሞ ከዚህ ዓለም ረብሻና ጩኸት ወጣ ብሎ እንዲሁም ከሕዝብም ይሁን ከሐዋርያት ተለይቶ ብቻውን ሆኖ መጸለይ እንደሚያስፈግ ያስተምረናል፣ ይህ መለየት ሐዋርያትን ወይንም ሕዝቡን እንደመተው ስለእነርሱ ግድ እንደሌለው ሆኖ መታየት የለበትም፣ ቅ.ማቴዎስ በወንጌሉ (14፡22) እንደሚነግረን
“ወዲያውም ሕዝቡን ሲያሰናብት ሳለ፥ ደቀ መዛሙርቱ በታንኳይቱ ገብተው ወደ ማዶ እንዲቀድሙት ግድ አላቸው። ሕዝቡንም አሰናብቶ ይጸልይ ዘንድ ብቻውን ወደ ተራራ ወጣ። በመሸም ጊዜ ብቻውን በዚያ ነበረ”። ይላል፣ አያይዞም ከሌሊቱም በአራተኛው ክፍል “ኢየሱስ በባሕር ላይ እየሄደ ወደ እነርሱ መጣ ይላል። ሐዋርያት ተቸግረው ነበር ፍርሃትም ስለነበራቸው ምትሐት ነው ብለው ታወኩ በፍርሃትም ጮኹ። ወዲያውም ኢየሱስ ተናገራቸውና። አይዞአችሁ፥ እኔ ነኝ፤ አትፍሩ አላቸው”። ይህ የወንጌል ክፍል ብዙ ትርጉም ስላለው የቤተ ክርስትያን አባቶች ብዙ ትጠቀሙበት፣ ባህሩ የሰው ልጅ ሕይወትንና የዓለማችን ቋሚ አለመሆንን ሲያመለክት ማዕበሉ በኑሮ የሚይጋጥሙትን ፈተናዎች ሁሉ ያመለክታል፣ ጀልባይቱ በክርስቶስ ላይ የታነፀችውንና በሐዋርያት የምትመራውን ቤተ ክርስትያንን ያመልክታል፣ በዚህም ኢየሱስ ለሐዋርያት የሕይወት ትግልን በብርታት እንዲጋፈጡ በሆሬብ ተራራ ላይ ለኤልያስ ነቢይ ከምድር መናወጥና ከእሳት በኋል ለስለስ ባለ ድምጽ በተገለጠው (1ኛው መጽሐፈ ነገስት 19።12) እግዚአብሔር እንዲተማመኑ ሊያስተምራቸው በመፈለጉ ይህን አድርገዋል፣ የወንጌሉ ክፍል ከዚህ በመቀጠል ጴጥሮስ ያደረገውን እንዲህ ሲል ይተርካል። “ጴጥሮስም መልሶ ጌታ ሆይ፥ አንተስ ከሆንህ በውኃው ላይ ወደ አንተ እንድመጣ እዘዘኝ አለው። እርሱም ና አለው። ጴጥሮስም ከታንኳይቱ ወርዶ ወደ ኢየሱስ ሊደርስ በውኃው ላይ ሄደ። ነገር ግን የነፋሱን ኃይል አይቶ ፈራ፥ ሊሰጥምም በጀመረ ጊዜ ጌታ ሆይ፥ አድነኝ ብሎ ጮኸ። ወዲያውም ኢየሱስ እጁን ዘርግቶ ያዘውና። አንተ እምነት የጎደለህ፥ ስለምን ተጠራጠርህ? አለው።” ቅዱስ አጎስጢኖስ ስለዚህ ፍጻሜ ሲያስተምር “ጌታ ዝቅ ብሎ በእጅህ ያዘህ፣ ያችን የረዳችህ እጅ አንተን ለማዳን ከሰማይ የወረደ የጌታ እጅ ቀጥ አድርገህ ያዘው” ይላል፣ ይህንን ያለው ለቅዱስ ጴጥሮስ ብቻ አይደለም፣ እኛንንም እንዲሁ ይለናል፣ ቅዱስ ጴጥሮስ በወኃ ላይ ለመጓዝ የቻለው በገዛ ኃይሉ ሳይሆን በሚያምነው በእግዚአብሔር ጸጋ ነው፣ ሆኖም ግን እምነቱን በጌታ ከማኖር ይልቅ መጠራጠር በጀመረበት ግዜ ፍርሐት ይወረዋል ማዕበሉ አስፈራው። ይህም የሆነበት ምክንያት በመምህሩ ቃል አልተማመነም በሌላ አነጋገር በኅሊናው ከመምህሩ መራቅ ጀመረ ያኔም ሊሰጥም ተቃረበ እኛም በሕይወታችን ራሳችንን ብቻ የተመለከትን እንደሆነ እንዲሁ እንሆናለን፣ በነፋስ እንገፋለን ወደ ሕይወት ውኃ ለመሻገርም ያቅተናል፣ ትልቁ ጸሐፊ ሮማኖ ጓርዲኒ ይህንን አስመልክቶ “ገዛ ራስን መቀበል” በሚለው መጽሐፉ “ጌታ የህልውናችን መሠረት በመሆኑ ሁል ግዜ አጠገባችን ነው፣ ጌታ ከእኛ ጋር መኖሩን ለማጣጣም ከፈለግን ጌታ ምኑን ያህል ቅርባችን መሆኑንና ከእኛ ምን ያህል ሩቅ መሆኑ በማስተንተን ነው፣ በቅርበቱ ከለላ እናገኛለን በመራቁ ደግሞ ወደ ፈተና እንገባለን” ብለዋል።።
ውዶቼ! የእግዚእብሔርን ህላዌ በለስላሳ ድምጽ ያዳመጠው ኤልያስና በመጠራጠር ጌታ የረዳው ጴጥሮስ ተመክሮ የሚያስተምረን ነገር ጌታ ገና እኛ ሳንሻውና ሳንማጠነው ሊያገኘንና ሊረዳን የሚመጣ እርሱ መሆኑን ነው፣ ከሰማየ ሰማያት ዝቅ ብሎ በእጃችን ይዞ ከፍ ወዳለ ቦታ እንዲወስደን እኛ በእርሱ እስከምንተማመንና እጁን ለመያዝ እጃችን እስክንዘረጋ ይጠባበቀናል፣
በዚሁ የችግሮችና የፈተናዎች ማዕበላት የሕይወት ባህራችንን በሚያናውጡት አሳሳቢ ዘመናችን አይዞህ አትፍራ እኔ ነኝ የሚለው አስተማማኝ የጌታ ድምጽ በልባችን እንዲያስተጋባና በእርሱ ላይ ያለን እምነት እንዲያድግ በሙላት በእግዚአብሔር የመተማመን አብነት የሆነች ድንግል ማርያም እንትድረዳን ዘንድ እንማጠናት፣ ብለው ካስተማሩ በኋላ የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎት አሳርገዋል፣
ከመልአከ እግዚአብሔር ጸሎት በኋላ ቅዱስነታቸው በሶርያና በሊብያ ስላለው ዓመጽ ይህንን ብለዋል።። በሶርያ ብዙ የሰው ሕይወት እየቀሰፈና ብርቱ ሥቃይ እያስከተሉ ያሉ ከዕለት ወደ ዕለት እየባሱ የሚሄዱት ዓመጾች እያሳሰቡኝ ናችው፣ ካቶሊካውያን ምእመናን ይህ ሥቃይ እንዲያበቃ መከፋፈልና ቂም በቀል ተወግዶ ዕርቀ ሰላም እንዲወርድ እንዲጸልዩ አሳስባለሁ፣ በተጨማሪም የሶርያ ሕዝብና ባለሥልጣናት በተቻለ መጠን አሁኑኑ በሰላም ተባብሮ የመኖር ሁኔታ እንዲፈጠር ዘንድ የሕዝቡ ጥያቄ ሰብአዊ መብታቸውን በሚጠብቅና መረጋጋት በሚፈጥር መንገድ ሁነኛ መፍትሔ እንዲገኝ ጥሪ አቀርባለሁ፣ በሌላ በኩል የጦር መሣርያ ኃይል ምንም መፍትሔ ያላስገኘላት የሊብያ ሁኔታም ያሳስበኛል፣ ዓለም ዓቀፍ ተቋሞች ፖለቲካዊና ወታደራዊ ኃላፊነት ያላቸው ሁሉ በውይይትና ገንቢ በሆነ ድርድር ለሀገሪቱ ሰላም የሚሆን ዕቅድ እንዲፈልጉ እማጠናለሁ፣ ብለዋል።