Font Size

Cpanel

Cistercians In Ethiopia - Ethiopian Catholic Church

ፍኖተ መስቀል

ቤተ ክርስቲያናችን በምስራቃዊና በላቲን ሥርዓት የተለያዩ ብዛት ያላቸው በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማት ላይ ለማስተንተን የሚያግዙ ጸሎቶች አሏት። ከነዚህም ውስጥ በላቲን ሥርዓት ውስጥ በምእመናን ዘንድ ይበልጥ የሚዘወተረው የ"ፍኖተ መስቀል" ጸሎት ነው። በዚህ ገጽ ውስጥ የቀረበውም ይህንኑ ጸሎት መሠረት ተደርጎ "መንፈሳዊ ማሳሰቢያ" በሚል ስያሜ በማኅበረ ሲታውያን ተዘጋጅቶ ከነበረው መጽሐፍ ውስጥ ነው። ጌታ ራሱ ወደ ሕማማቱ የፍቅር መስጢር እንድንገባና እንኖረው ዘንድ ያግዘን።

በዚህ ጽሑፍ ክፍል ውስጥ የሚገኙ ሌሎች ጽሑፋት

ፍኖተ መስቀል

[fn32]
1ኛ - ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞት ተፈረደበት 1
  • 1ኛ - ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞት ተፈረደበት

    ፩ - ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞት ተፈረደበት

    stazione1

    አይሁዳውያን ጌታችንን ከያዙት በኋላ እንደ በደለኛና ወንጀለኛ አስረው ሞት እንዲፈረድበት በሊቀ ካህናት ቀያፋ  ፊት አቆሙት፡፡ እርሱም ይሙት ብሎ ከፈረደት በኋላ ወደ አገረ ገዥው ወደ ጲላጦስ ወሰዱት፡፡ ጲላጦስም ኢየሱስን ካየው በኋላ “በዚህ ሰው ላይ ያቀረባችሁት ክስ ምንድን ነው?” ዮሐ. 18፡29 ሲል ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም “ይህ ሰው ክፉ አድራጊ ባይሆን ኖሮ ወደ አንተ አሳልፈን ባልሰጠነው ነበር” ዮሐ. 18፡3ዐ ሲሉ መለሱለት፣ ቀጥለውም “ይህ ህዝባችንን ሲየጣምም፣ ለቄሳር ግብር እንዳይሰጥ ሲከለክል፣ ደግሞም እኔ ክርስቶስ ንጉስ ነኝ ሲል አገኘነው” ሉቃ. 23፡2 ብለው ይከሱት ጀመር፡፡

    ጲላጦስም “አንተ የአይሁድ ንጉስ ነህን?” ብሎ ጠየቀው ሉቃ. 23፡3 ኢየሱስም “አንተ ይህንን የምትለው ከራስህ ነውን ወይስ ሌሎች ስለ እኔ ነግረውሃል” ዮሐ. 18፡24 አለው፡፡ ጲላጦስ አይውዳውያን ደጋግመው ኢየሱስን  አጥብቀው ሲከሱት አይቶ “ምን ያህል ሰዎች እንደሚመሰክሩብህ አትሰማምን?” ማቴ. 27፡13 አለው? ጌታችን ግን ሳይመልስ ዝም አለ፡፡

    ጲላጦስ የአይሁዳውያንን ክስ ከሰማ በኋላ ኢየሱስን ደህና አድርጐ መርምሮ አጣራና በደል እንደሌለበት ስላረጋገጠ የአይሁዳውያን ክስ የጥላቻና የቅናት ፍሬ ብቻ መሆኑን ተረዳ፡፡ ስለዚህ እንደምንም ብሎ ኢየሱስን ከሞት ሊያድነው ፈልጐ “እነሆም ለሞት የሚያደርሰው ምንም አላደረገም፣ እንግዲያውስ ቀጥቸ እፈታዋለሁ” ሉቃ. 23፡16 አላቸው፡፡ እነርሱም ሁሉም “ይሰቀል!” በማለት በጩኸት መለሱለት፡፡

    ሌላ ባርባን የሚባል ከፍተኛ ወንጀል የሰራ፣ ነፍሰ ገዳይ አብሮ ተከሶ ነበርና ጲላጦስ ኢየሱስን ከሞት አድኖ በእሱ ፋንታ በርባንን ይጠሉ እንደሆነ ብሎ በርባንን እና ኢየሱስን አቅርቦ “በርባን ወይስ ክርስቶስ የተባለው ኢየሱስን ማንኛቸውን ልፈታላችሁ ትወዳላችሁ?” አላቸው… የካህናት አለቆችና ሽማግሌዎች ግን በርባንን እንዲፈታ ኢየሱስ ግን እንዲያጠፋ ህዝቡን አስተባበሩ፣ … እነርሱም በርባንን አሉ ማቴ. 27፡17-23 ፡፡

    ጲላጦስ ኢየሱስን ካስገረፈው በኋላ “እነሆ! ሰውየው እነሆ! ንጉሣችሁ በደለ እንዳላገኘሁበት እንድታውቁ እርሱ ወደ ውጭ አወጣላችኋለሁ” አላቸው፡፡ እነርሱም እንደገና “ስቀለው! ስቀለው! ብለው በመጮህ ግርግር ፈጠሩበት፡፡ ጲላጦስም “ ምን አደረገ?” ቢላቸው “ይህን ሰው ከፈታኸው የሮም ንጉሰ ነገስት የቄሳር ወዳጅ አይደለህም” ዮሐ. 19፡12 እያሉ አስፈራሩት፡፡ ጲላጦስም የሚቻውን ሁሉ ካደረገ በኋላ ኢየሱስን ለማዳን ሲል ራሱን እንዳይጐዳ ፈርቶ በደል የሌለውን ኢየሱስን የሰውን አይን በመፍራት ሞት ፈረደበት ወዲያውኑ በአይሁዳውያን እጅ አሳለፎ ሰጠው፡፡ ኢየሱስ በቀያፋና በጲላጦስ ፊት ጠላቶቹ አይሁዳውያን በሀሰት ሲከሱት አልተከላከለም፡፡ አፉን ዘግቶ ዝም አለ፤ በዚህም ጲላጦስ ሳይቀር ስለገረመው “አትመልስምን?” አለው፡፡ ኢየሱስ ዝም ማለቱ በደል ኖሮት ወይም ደግሞ መከላከል አቅቶት አልነበረም ስላልፈለገ ብቻ ነው፡፡

    አይሁዳውያን ደጋግመው በሀሰት ይከሱት ነበር፤ እርሱን ሀሰተኛ ክሳቸውንና ስድባቸውን ዝም ብሎ ተቀበለው፡፡ አይሁዳውያን ኢየሱስን ከያዙት በኋላ እንደ ትልቅ በደለኛ አስረው እያዋረዱና እየሰደቡ ወሰዱት፡፡ እርሱ ግን እንደ በግ አንድም ቃል ሳይናገር ተከተላቸው፡፡ አምላክ ሳለ ፍጥረቶቹ ሲቀልዱበትና ሲዘባበቱበት ዝም ብሎ ተመለከታቸው፣ ንፁህ ሳለ እንደ በደለኛ ተቆጠረ፡፡ እንዴት ያለ ትህትና ነው? “ኦ! አርምሞት ዘመጠነዝ አርምሞት፡- እንዴት ያለ ትህትና? ይህን ያህል ትህትና? ይህን ያህል ትዕግስት? ይህን ያህል ዝምታ?” እያለ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ይደነቃል፣ ይገረማል፡፡

    ጲላጦስ አይሁዳውያንን ፈርቶ ኢየሱስን በደል ሳይኖረው ሞት ፈረደበት፣ ኮነነው፡፡ እኛም ብዙ ጊዜ እንደዚህ እናደርጋለን፤ ከኢየሱስ ይልቅ ሰዎችን ፈርተን ኢየሱስን እንክዳለን፤ ሰዎችን ለማስደሰት ብለን ኢየሱስን እናሳዝናለን በኃጢአታችን ብዛት እንደገና በኢየሱስ ሞት እንፈርድበታለን፡፡ ኢየሱስ ስለእኛ ይህንን ሁሉ ውርደትና መከራ ተቀብሏል፡፡ ለደህንነታችን ብሎ ሲፈርዱበትና ሲያዋርዱት ዝም ብሎ ተመለከታቸው ፍቅሩንና ስቃዮን በልባችን ውስጥ እናትመው፡፡ ሁለቱንም ዘወትር እያሰብን ከሁሉ አስቀድመን ወደ ኃጢያት እየተመላለስን አናሳዝነው፤ ቀጥለን ደግሞ እርሱ እንደ ወደደን እንድንወደው ቁርጥ ውሳኔ እናድርግ፡፡

2ኛ- ኢየሱስ መስቀሉን ለመሸከም ተቀበለ 2
  • 2ኛ- ኢየሱስ መስቀሉን ለመሸከም ተቀበለ

    ፪ - ኢየሱስ መስቀሉን ለመሸከም ተቀበለ፤

    stazione2ጲላጦስ ኢየሱስን ሞት ከፈረደት በኋላ እንደ ባሕላቸው እንዲሰቅሉት ለአይሁዳውያን አሳልፎ ሰጣቸው፡፡ “ከዚህ በኋላ ጲላጦስ በርባንን አድኖ የተገረፈውን ኢየሱስን እንዲሰቀል አሳልፎ ሰጣቸው” ማቴ. 27፡26 በዚህ የአይሁዳውያን ምኞት ተፈጸመ፡፡

    ወታደሮች ኢየሱስን ተቀብለው በጲላጦስ ግቢ አቆሙት፡፡ ሁሉም በአንድ ላይ ተሰብስበው ልብሱን ገፈው ሊቀልዱበት ቀይ ልብስ አልብሰው በራሱ ላይ የእሾህ ጉንጉን አስረው በእጁ ደግሞ በንጉሥ በትር ፈንታ መቃ አስያዙት፡፡ በፊቱም እየተንበረከኩ “የአይሁድ ንጉሥ ሆይ ሰላም ላንተ ይሁን” ማቴ. 27፡27-33 እያሉ ይቀልዱበትና ይተፉበትም ራሱንም በመቃ ይመቱት ነበር፡፡

     

    እንደዚህ አድርገው ካሠቃዩት በኋላ መስቀሉን አሸክመው “ቀራኒዮ” ወደሚባል ስፍራ ወሰዱት፡፡ ኢየሱስም መስቀሉን ተሸከመ፡፡ አምላክና ፈጣሪ ሁሉን የሚችል ሆኖ ሳለ እንደ በደለኛ ተቆጥሮ ለትላልቅ በደለኞች የሚገባውን ቅጣት ተቀበለ፡፡ የባሰና የከፋ ቅጣት በራሱ ላይ ወረደበት፣ ፈጣሪ በፍጡሮቹ እጅ ተዋረደ፣ ተሰቃየም፣ ፍጡሮቹ መስቀልን አሸከሙት፡፡

3ኛ- ኢየሱስ መስቀሉን እንደተሸከመ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደቀ 3
  • 3ኛ- ኢየሱስ መስቀሉን እንደተሸከመ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደቀ

    ፫ - ኢየሱስ መስቀሉን እንደተሸከመ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደቀ

    stazione3መድኃኒታችን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስቀሉን ተሸክሞ ወደ ቀራኒዮ ሲሄድ ሳለ ለመጀመሪያ ጊዜ ከመስቀሉ ጋር እንደወደቀ ያሳስበናል፡፡ ኢየሱስ ሞት ከተፈረደበት በኋላ መስቀሉን ተሸክሞ ወደ ቀራኒዮ ፊቱን አመራ፡፡

    በመጀመሪያው ስቃይና ግርፋት ደክሞ ስለነበር ከባድ መስቀል ተሸክሞ ሲሄድ ለመጀመሪያ ጊዜ ከከባድ ሸክሙ የተነሳ በመንገድ ላይ ወደቀ፡፡ አይሁዳውያን በርኀራኄ መንፈስ ተመልክተው እንዲነሳ መርዳት ሲገባቸው በስድብ፣ በድብድብና በበትር በመምታት እንዲነሳ አስገደዱት፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን እነርሱን በመፍራት ሳይሆን በመስቀልና በደኅንነታችን ተገዶ ብድግ ብሎ ተነሳ፡፡

    ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእውነት የከበደውና ያደከመው በመንገድ የጣለው የመስቀሉ ክብደት ብቻ ሳይሆን በአንጻሩ የኃጢአታችን ክብደት ነው፡፡ ምክንያቱም ያለፈውንና የሚመጣውን ሥፍር ቁጥር የሌለውን የሁላችንም የአዳም ልጆች ኃጢአት በማስታወስ ነው፡፡ የሁላችንም የአዳም ልጆች ኃጢአት ብዛት እንደ አንድ ትልቅና በጣም ከባድ የድንጋይ ቋጥኝ ተጫነው፤ በክብደቱም ብርታት መራራ ሐዘን ተሰማው፡፡ ኃጢአታችን ለመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከባድ ሸክም ነው፡፡

     

4ኛ- ኢየሱስ ከቅድስት እናቱ ጋር ተገናኘ 4
  • 4ኛ- ኢየሱስ ከቅድስት እናቱ ጋር ተገናኘ

    ፬ - ኢየሱስ ከቅድስት እናቱ ጋር ተገናኘ

    stazione4አይሁዳውያን ኢየሱስን እያዋረዱ፣ እየመቱና እየገረፉ ይወስዱት ነበር፡፡ እርሱ ደግሞ በትሕትና ይታዘዝላቸው ነበር፡፡ “ተጨነቀ፣ ተሰቃየ አፋንም አልከፈተም ለመታረድ እንደሚዳ ጠቦት በሸላቾችም ፊት ዝም እንደሚል በግ እንዲሁ አፉን አልከፈተም” ኢሳ. 53፡ 1-6 ፡፡ ኢየሱስ ውርደትን ታግሶ ተቀበለ ከባድ መስቀልን በትከሻው ተሸክሞ ወደ ቀራኒዮ ሄደ፡፡ በመንገድ ያች የተወደደች ርኅርኅት እናት ወላዲቱ ቆየችው፤ ስቃዩን አውቃ በወላጅ እናት ፍቅር ተስባ ልታየው ወጥታ ነበር ዓይን ለዓይን የተገናኙት፡፡

    ኢየሱስ እመቤታችን ማርያምን በማየቱ ብርቱ ሐዘን ተሰማው፤ እርስዋ ደግሞ ኢየሱስን ልጅዋን  በማየትዋ ትልቅ ሐዘን ተሰማት፡፡ ኢየሱስ በድካም ተሸንፎ የመስቀሉም ሸክም ከብዶት እየተደነቃቀፈ መንገዱን ቀጠለ፡፡ ፊቱ በእድፍ፣ በቆሻሻ፣ በምራቅና በደም ተበላሽቶ ነበር፡፡ ሰውነቱ በሙሉ ቆስሎ አለመጠን ተለውጦ ተጐሳቁሎና ዝሎ ነበር፡፡

    “መልክና ግርማ አልነበረውም ከሁሉ የተዋረደና ዝቅ ያለ፣ መከራና ስቃይን የተሞላ ነው” ይላል ኢሳይያስ፡፡ ይህንን አይታ እመቤታችን ማርያም በፍጹም ደነገጠች፡፡ የእርሱ ስቃይ እንደ ሹል ጦር ልብዋን ወጋት፡፡ ያ የተወደደው ልጅዋ እንዲህ ተዋርዶና ተንገላቶ የእነዚያ ክፉ አይሁዳውያን መዘባበቻ ሆኖ በማየትዋ መራራ ሐዘን ተሰማት፣ ፊትዋ ጠቆረ፣ ከሰል ጥላሸት መሰለ፣ ከዓይኖችዋ እንባዋ እንደጐርፍ ፈሰሰ፡፡

     

    ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደግሞ በበኩሉ እናቱ በስቃይና በሐዘን ተውጣ ስለአየ በሐዘን ላይ ሐዘን ተጫነው ተጨመረበት፡፡ የሁለቱም ሐዘን ተገናኘ መከራቸውም ተለዋወጡ፣ እናት ልጅዋን አጽናናች፣ ልጅም ደግሞ እናቱን አጽናና፡፡ እያንዳንዳቸው ስቃያቸውን ለመሸከም ተጋገዙ፡፡

5ኛ- ቀሬናዊው ስምዖን የኢየሱስን ረዳ 5
  • 5ኛ- ቀሬናዊው ስምዖን የኢየሱስን ረዳ

    ፭ - ቀሬናዊው ስምዖን የኢየሱስን ረዳ

    stazione5አይሁዳውያን ኢየሱስ ከልክ በላይ ደክሞት እንደ ነበር ከተረዱ በኋላ ቀራንዮ ሳይደርስ እንዳይሞት ፈርተው በዚያ መንገድ ያልፍ የነበረ የቀሬናው ስምዖን ለሚባል ሰው የኢየሱስን መስቀል በመሸከም እንዲያግዘው አዘዙት፡፡ እርሱም ታዘዛቸው፡፡ አይሁዳውያን ኢየሱስ መስቀል ከመሸከም እንዲያርፍ የፈለጉት ራርተውለት ሳይሆን ለረጅም ጊዜ የቆየ ቂማቸው ፍጻሜ ሳያገኝ ግቡን ሳይመታ እንዳይቀር ፈርተው ነው፡፡

    እንዲሁም ቀሬናዊ ስምዖን መስቀሉን በመሸከም የረዳውና ያገዘው ራርቶለት አልነበረም፡፡ ለራሱ ተቆርቁሮ የባሰ ችግር እንዳይደርስበት ብሎ ነው፡፡ ምስኪኑ ኢየሱስ መከራውን አይቶ አንድ እንኳን ራርቶ የሚያግዘው አልተገኘም፡፡

    ኢየሱስ ዘወትር ስለ እኛ መስቀልን ይሸከማል፡፡ ለብቻው ከባድ መስቀል ተሸክሞ ሲሄድ እናየዋለን፡፡ ደክሞት ረዳት የሚያስፈልገው መሆኑን እያወቅን ዝም እንላለን፡፡ የመስቀል ውርደት በኃጢአታችን ሰበብ እንደሆነ እንረሳለን፡፡

6ኛ- ቅድስት ቨሮኒካ የኢየስን ፊት ጠረገችለት 6
  • 6ኛ- ቅድስት ቨሮኒካ የኢየስን ፊት ጠረገችለት

    ፮ - ቅድስት ቨሮኒካ የኢየስን ፊት ጠረገችለት

    stazione6ኢየሱስ መስቀል ተሸክሞ ወደ ቀራኒዮ ሲሄድ በመንገድ ላይ ቨሮኒካ የምትባል አንዲት ደግ ሴት ፊቱ በላብ፣ በምራቅ፣ በአፈር፣ በደም አድፎ ባየችው ጊዜ ሰዎቹን ሳትፈራ ወደ እርሱ ቀርባ በመሐረብ ፊቱን ጠረገችለት፡፡

     በተአምር በአንድ ጊዜ የተበላሸው የኢየሱስ ፊት ገጽታ በመሐረቧ ላይ ታትሞ ቀረ፡፡ የዚህች መንፈሳዊት ሴት ርኅራኄ የሚመሰገን ነው፡፡ አስቀድማ ኢየሱስ ማን መሆኑን ምን እንደሚያደርግ ታውቅ ስለነበር ወደ እርሱ ቀረበች፡፡

    ደግነቱን፣ ቃሉን፣ ተአምራቶቹንና ምልክቶቹን በዓይነ ሕሊናዋ አስታውሳ ፊቱ ተበላሽቶ ስታየው ያ ቀድሞ ለእርሱ የነበራት ትልቅ እምነትና ፍቅር እንደገና ሳባት፡፡ በውርደቱ በፍጹም ደንግጣ ጠጋ ብላ የፊቱን እድፍ አስወገደችለት፡፡ በዚህም በጣም ብዙ አጽናናችው፡፡

     

     

     

7ኛ- ጌ.ኢ.ክ. በቀራኒዮ መንገድ ሁለተኛ ጊዜ ወደቀ 7
  • 7ኛ- ጌ.ኢ.ክ. በቀራኒዮ መንገድ ሁለተኛ ጊዜ ወደቀ

    ፯ - ጌ. ኢ. ክ. በቀራኒዮ መንገድ ሁለተኛ ጊዜ ወደቀ

    stazione7የቀራኒዮ መንገድ ኢየሱስን ብዙ ጐዳው፣ በመጀመሪያ የወደቀውና አካላቱ የተቀጠቀጠው ሳያንሰው በተጨማሪ ከባድ መስቀል ተሸክሞ ሲጓዝ ሁለተኛ ጊዜ በምድር ላይ ወደቀ፡፡ የፊተኛው ሳይበቃው እንደገና የወደቀው ኢየሱስ ስለ እኛ ምስኪን የሆነው ከፊተኛው መውደቅ ሁለተኛው በረታበት ብዙም ጐዳው፣ አቆሰለው፡፡ እንደገና ለመሄድ ተነሣ ነገር ግን ሰውነቱ ዛለ ደከመ፡፡

    ኢየሱስ ከወደቀበት ሥፍራ ማንም ሳያግዘውና ሳይደግፈው እንደገና ራሱ ተነሣ፡፡ በሰው ተገዶ ወይም ሰውን ፈርቶ ሣይሆን በገዛ ፍቃዱ መስቀሉን ለመሸከም ወዶ ብድግ አለ፡፡ ወደሚሰዋበት ቦታ ቶሎ ለመድረስ ፈልጐ መስቀሉን ይዞ ተነሣ፡፡ ያ ሁሉ ውርደትና ስቃይ በአባቱ ፈቃድ መሆኑን አስታውሶ ተነሣና መስቀሉን ተሸክሞ መንገዱን ቀጠለ፡፡ ድካሙንና መከራውን ሳይቆጥረው በፍላጐት ብድግ ብሎ ተነሣላቸው ስቃይና መከራውን ሁሉ ረሳው፡፡

8ኛ- ኢየሱስና ርኅሩሆቹ ሴቶች 8
  • 8ኛ- ኢየሱስና ርኅሩሆቹ ሴቶች

    ፰ - ኢየሱስና ርኅሩሆቹ ሴቶች

     

    stazione8ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስበክ በጀመረ ጊዜ ሴቶች በቅድስናውና በተአምራቱ እጅግ ታንጸው ሁሉን ትተው ተከተሉት፡፡ በሞቱ ወቅት እነዚህና ሌሎች ደግ ሴቶች በወረደበት መከራ ደንግጠው ሲያስተውሉትና ሲራሩለት ታዩ፡፡
    በዚህ አጋጣሚ ከባዱን መስቀል ተሸክሞ ወደሚሰቀልበት ቦታ ወደ ቀራንዮ ሲሄድ ብዙዎቹ ሲጨክኑበት እንደዚህ ደክሞና ተዋርዶ አይተው አሳዝኖአቸው እንባ እያፈሰሱ አለቀሱለት፡፡ ኢየሱስ በፍቅራቸው ተደስቶ ወደ እነርሱ መለስ በማለት “የኢየሩሳሌም ሴቶች ሆይ ስለ ራሳችሁና ስለ ልጆቻችሁ አልቅሱ እንጅ ስለ እኔ አታልቅሱ” ሉቃ. 23፡27 እያለ አሳሰባቸው፡፡
    ስለ ራሳችሁና ስለ ልጆቻቸሁ አልቅሱ ስለ ኢየሱስ ያለቀሱ ሴቶች ደግ አደረጉ፣ የሚመሰገን ጥሩ የፍቅርና የርኅራኄ ሥራ ፈጸሙ፡፡ስቃዩንና ውርደቱን ተመልክተው በማልቀሳቸው የሚያስመሰግናቸው የማይረሳ መልካም ግብር ፈጽመዋል፡፡ ኢየሱስን በደንብ አጽናኑት፡፡

     

     

9ኛ- ጌ.ኢ.ክ. በቀራኒዮ መንገድ ሶስተኛ ጊዜ ወደቀ 9
  • 9ኛ- ጌ.ኢ.ክ. በቀራኒዮ መንገድ ሶስተኛ ጊዜ ወደቀ

    ፱ - ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቀራኒዮ መንገድ ሶስተኛ ጊዜ ወደቀ

    stazione9የኢየሱስ ሰውነት ዝሎና ደክሞ ነበር፤ የኢየሱስ መከራ ወደ ፍጻሜ ሊደርስና በቀራኒዮ ስለ አዳም ልጆች ደኅንነት ሊሰዋ ተቃርቦ ነበር፡፡ ግርፋቱ፣ ድብደባውና እንግልቱ አድክሞና አሸንፎት ሶስተኛ ጊዜ ከመስቀሉ ጋር በመንገድ ወደቀና በጣም ተጐዳ፣ ብርቱ ስቃይ ተሰማው፡፡ ግን በገዛ ፈቃዱ በፍጥነት ይነሣና በታላቅ ትሕትና ወደ ሚሰቀልበት ይሄድ ነበር፡፡

    የፊተኛው መውደቁንና ጉዳቱን ሳይቆጥር ተስፋ ባለመቁረጥ ወደ ቀራንዮ አቅጣጫ ይጓዝ ነበር፣ ሲወድቅ በጣም ይጐዳና ይሰቃይ ነበር፣ ከመስቀሉ ክብደትና ጫና ያለመጠን ይጐዳው ነበር፡፡ ነገር ግን ምኞቱ ደኅንነታችን ስለነበር ሁሉን በስቃይ ወዶ ይቀበለውና ስለ እኛ ብሎ ተደስቶ ይሰቃይ ነበር፡፡

    ደኅንነታችን ለስንት መከራና ውርደት ዳረገው፤ ስቃይ አስወደደው። ለእኛ ሲያስብ ውርደቱን ይረሳ ነበር፤ ተደራርቦ ቢመጣበትም “ይህንን አልችልም አሁንስ በቃኝ” አይልም ነበር፡፡

     

10ኛ - ኢየሱስ ልብሶቹን ተገፈፈ 10
  • 10ኛ - ኢየሱስ ልብሶቹን ተገፈፈ

    ፲ - ኢየሱስ ልብሶቹን ተገፈፈ

    stazione10ኢየሱስ ወደ ቀራኒዮ ወጣ፡፡ በአንድ በኩል የአይሁዳውናያን መጥፎ ሐሳብ እርሱን መገደል በሌላ በኩል የተቀደሰ ምኞት ዓለምን በማዳን ተፈጸመ፡፡ በቀራኒዮ የባየ መከራ ይቀብቀው ነበር፡፡ አይሁዳውያን ቀድመው ሊፈርዱበት ብለው ላይና ታች እያሉ ሲያንገላቱቱ ለፌዝና ለቀልድ ሲሉ ቀይ ካባ በልብሱ ላይ ደረቡለት፡፡ በኋላ በቀራኒዮ ልብሱን ሁሉ ገፈፉት ራቁቱን አወጡት፤ ሐሞት ኮምጣጤ አጠጡት፣ ልብሱን በመግፈፍ እንዴት ያለ ውርደት ተሰማው?

     

    እንደዚህ ያለ ውርደት ያጋጠመው ማነው? ራሱ አምላክ ነው፡፡ ይህ ራቁቱን የወጣው ሁሉን የሚችል ፈጣሪ ሁሉም ሀብት ያለው አምላክ ነው፡፡ ይህ እንደዚህ እፍረት የደረሰበት ሊደረስ የማይችል ብርሃን እና ሞገስን የሚለብስ የእግዚአብሔር ልጅ ነው፡፡

     

    መለኮታዊ ግርማ ሞገሱን መግፈፍ ሳይበቃቸው እንደገና ደግሞ ኀፍረተ ሥጋውን የሚያለብስበትን ልብሱን ገፈፉት፣ እርሱ ግን ራቁቱን መሆን በመከልከል በተአምር ሊለብስ ሲችል ግን አላደረገውም፡፡ እንደ ኃጢአተኛ ሊዋረድ ስቃያችንን ሊሸከም ወደደ፡፡ ለዚህ ያደረሰው ለእኛ ያለው ፍቅር ነው፡፡ ኃጢአት ስናደርግ ኢየሱስን እናዋርደዋለን፣ እንተወዋለን ሰማያዊ ውበቱንና አምላካዊ ግርማ ሞገሱን በኀፍረትና በሐዘን እንሸፍነዋለን፡፡

11ኛ - ኢየሱስ መስቀል ላይ ተቸነከረ 11
  • 11ኛ - ኢየሱስ መስቀል ላይ ተቸነከረ

    ፲፩ - ኢየሱስ መስቀል ላይ ተቸነከረ

    stazione11አይሁዳውያን ለኢየሱስ መራራ ሐሞት እና ሆምጣጤን ካጠጡት በኋላ ልብሱን ገፈው ሊሰቅሉት ተዘጋጁ፤ መስቀሉን በምድር አስቀመጡት ኢየሱስን በእርሱ ላይ አስተኝተው ያለ ርኅራኄ ያለ ምህረት እጆቹንና እግሮቹን ቸነከሩት፡፡ እንደገና ደሙን እያፈሰሰ እና እያጐረፈ ሲታይ ብርቱ ስቃይ ይሰማው ነበር፡፡ መከረኛው ኢየሱስ መከራው ባሰ፡፡ የመስቀል ስቃይ በጣም ከበደው፡፡

    “በደል የሌለውን እንደ በደለኛ ቆጥረው ያለ አግባብ ከበደለኞች እኩል ሰቀሉት፤ ሕይወትን የሚሰጥ በሐሰት ምስክሮች አቁመው እንደ ኃጢአተኛ ቆጠሩት፡፡ አዳምን የፈጠረ እጅ በገነት ይራመዱ የነበሩ እግሮቹ በምስማር በመስቀል ላይ ተቸነከሩ፡፡ ያ በአዳም ላይ የሕይወት እስትንፋስ እፍ ያለ አፍ ሆምጣጤ መራራ ሐሞትን መጣ፡፡ ስለ ተወደደው ሕማማት፣ ፍቅሩ የትኛው አፍ፣ የትኛው ከንፈር ሊናገር ይቻለዋል? ስለ ተወደደው ሕማማቱና ፍቅሩ ቢነገር ልብ ይሰነጥቃል፣ ሕሊናን ይመታል፣ ነፍስ ትደነግጣለች፡፡

     

    በመስቀል ላይ ቸነከሩት ከብዙና ብርቱ ውርደት ግርፋት ድካም በኋላ መቸንከሩን ይጠብቀው ነበር፡፡ ኢየሱስ መጀመሪያ መስቀሉን ይሸከም ነበር፡፡ በኋላ ግን መስቀሉ እርሱን ተሸከመው ኢየሱስ መስቀሉን ሲሸከም ብርቱ ስቃይ ተሰማው መስቀሉ እርሱን ሲሸከም ደግሞ የባሰ ስቃይ ተሰማው፡፡ ሰውነቱ ሁሉ ታመመ፤ ስቃይ በስቃይ ውርደት በውርደት ተጨመረ፡፡

    የሁሉም ጌታ ራቁቱን በመስቀል ንም ተሰቀለ፡፡ የመስቀል ስቃይና ውርደት  ይቅር ለአምላክ ለሰው እንኳ ያስረነውራል፡፡ ይህ ቢሆንም ኢየሱስ ስለ እኛ ብሎ የመስቀልን መከራ መቀበል አላፈረም፡፡ ስለ ደኅንነታችን ብሎ መስቀል ፊት መቆምን አልጠላም፡፡ የመስቀልን መከራና ኀፍረት ሊያስወግድ በቻለ ነበር፡፡ ግን አላደረገውም የደኅንነት መስዋዕት ሊሆንልን ወደደ፡፡

12ኛ - ኢየሱስ በመስቀል ላይ ተቸንክሮ ሞተ 12
  • 12ኛ - ኢየሱስ በመስቀል ላይ ተቸንክሮ ሞተ

    ፲፪ - ኢየሱስ በመስቀል ላይ ተቸንክሮ ሞተ

    stazione12ወታደሮች ኢየሱስ በመስቀል ላይ ከቸነከሩት በኋላ መስቀሉን ጉድጓድ ውስጥ አቆሙት፡፡ መስቀሉ እንደቆመ ኢየሱሰ ከባድ ስቃይ ተሰማው፣ ቁስሎች ጠዘጠዙት፡፡

    “ከእግር እስከ ራሱ ድረስ ቆስሏል” ኢሳ. 1፡7 ጅማቶቹ ተገታተሩ፣ የሥጋው ክብደት ወደ ታች ሳበው፣ ሥጋው ተቆራርጦ አጥንቶቹም ከውጭ ታዩ፡፡ “እጆቼንና እግሮቼን ቸነከሩኝ፣ አጥንቶቼ ሁሉ ተቆጠሩ እነርሱም አዩኝ ተመለከቱኝም” መዝ፡21  የሚል የዳዊት ቃል ተፈጸመ፡፡

    ከእርሱ ጋር በቀኙ እና በግራው ሁለት ሌቦች ተሰቀሉ ማቴ. 27፡38 “ከአመጸኞች ጋር ቆጠሩት” ኢሳ. 53፡12 እያለ ኢሳይያስ ይናገራል፡፡ አይሁዶች በኢየሱስ ለማፌዝ ብለው በላዩ “ኢየሱስ ናዝራዊ የአይሁድ ንጉሥ” ዮሐ. 19፡19 የሚል ጽሑፍ ለጠፉበት፡፡

13ኛ - ኢየሱስን ከመስቀል አውርደው ለእናቱ አስታቀፏት 13
  • 13ኛ - ኢየሱስን ከመስቀል አውርደው ለእናቱ አስታቀፏት

    ፲፫ - ኢየሱስን ከመስቀል አውርደው ለእናቱ አስታቀፏት

    stazione13ኢየሱስ “ሁሉም ተፈጸመ” በማለት ሞተ፡፡ የቀራኒዮን መስዋዕት አቀረበ ከረጅም ዘመናት ጀምሮ ይመኘው የነበረውን የአዳምን ዘር የማዳን ሥራ ፈጸመ፡፡ በሞቱ ሞታችንን አሸንፎ ሕይወትን ሰጠን፡፡ እኛ ታስረንበት የነበረውን ሰንሰለት ከእኛ አስወግዶ በእኛ ምትክ አስሮን የነበረውን ዲያብሎስን አሰረው፡፡ “አስሮ ለሰይጣን ወአግዓዞ ለአዳም”

    ዓርብ ምሽት ስለነበር ሬሳው ለቅዳሜ እንዲያድር አልፈለጉም፡፡ በኦሪት ዘዳግም “ማንም ሰው ለሞት የሚያበቃውን ኃጢአት ቢሠራ እንዲሞት ቢፈረድበት፤ በእንጨትም ላይ ብትሰቅለው በእንጨት ላይ የተሰቀለ በእግዚብሔር ዘንድ የተረገመ ነውና ሬሳው በእንጨት ላይ አይደር፡፡ ስለዚህ በዚያው ቀን ቅበረው” ዘዳ 21፡22 የሚል ትዕዛዝ ስለነበረ በሌላ በኩል ደግሞ ቅዳማ ቅልቅ በዓል ስለነበረና በዚህ ዕለት ምንም ነገር ማድረግ ስለማይቻል ነበር፡፡

    ዘጸ፡ 12፡17 በዚህ ምክንያት ጲላጦስ ሬሳውን ከመስቀል እንዲወርዱ ትዕዛዛ ሰጠ፡፡ ወታደሮቹም ተልከው ወደ ቀራኒዮ ሄዱ፤ የሁለቱን ወንበዴዎች ጭን ሰበሩ፤ ወደ ኢየሱስ ሲያዩ ሞቶ ስለነበር ጭኑን በመስበር ፈንታ ጐኑን በጦር ወጉት ከጐኑም ደምና ውኃ ፈሰሰ፡፡ ዮሐ. 19፡34

     

     

     

     

14ኛ - ኢየሱስ ተቀበረ 14
  • 14ኛ - ኢየሱስ ተቀበረ

    ኢየሱስ ተቀበረ

    stazione14እነዚህ ሶስት ጻድቃን ኢየሱስን ከመስቀል ካወረዱት በኋላ ሳይመሽ ሊቀብሩት ተቻኰሉ፡፡ እዚያ የነበሩት የዋህ ሴቶች በመታገዝ እንደ አይሁዳውያን ልማድ የኢየሱስን አስከሬን ሽቶ ቀብተው ከፈን ከፍነው በአጠገባቸው በነበረው መቃብር ቀብረው መቃብሩ ላይ ትልቅ ድንጋይ ጫኑበት፡፡ ማቴ. 27፡59-61 የህንንም አድርገው ወደ ቤታቸው ተመለሱ፡፡

ተወራራሽ ርእሶች