ዓመታዊ የቅዱስ ዮሴፍ ክብረ በዓል ተከበረ
በየዓመቱ በወርኃ ግንቦት የሚከበረው አ.አ. የሚገኘው የሲታውያን ገዳም የጻድቁ ቅዱስ ዮሴፍ ክብረ በዓል ብፁዕ ሊቀ ጳጳሳት አቡነ ብርሃነ ኢየሱስ፣ ካህናት፣ ደናግላን እንዲሁም ቁጥራቸው እጅግ የበዛ ካቶሊካዊያን ምእመናንና ሌሎችም በተገኙበት ግንቦት 26/2004 ዓ.ም. በዕለተ ጰራቅሊጦስ በድምቀት ተከብሮ ዋለ፡፡ ከዋና ክብረ በዓሉ በፊት ማለትም ዋዜማው ብዙ ያሬዳውያን መዘምራን፣ ካህናት፣ የቅዱስ ሚካኤል ዘርአ ክህነት፣ የኮምቦኒ፣ የቅዱስ ኤፍሬም አቢይ ዘርአ ክህነት፣ የመንዲዳ ገዳመ ሲታውያን ተመካሪያንና ዘርአ ምንኩስና ተማሪዎች እንዲሁም የቀድሞ የገዳመ ሲታውያን ተማሪዎችና ሌሎች እንግዶችም በተገኙበት እጅግ ያማረ የዋዜማ ሥነ ስርአት ከቀኑ 9 ስዓት እሰከ 11፡30 ተከናውኖአል፡፡
ዕለቱ ድርብ በዓል (ጰራቅሊጦስ ና ቅዱስ ዮሴፍ) እንደመሆኑ መጠን ብፁዕ አባታችን አቡነ ብርሃነ ኢየሱስ ሊቀ ጳጳሳት ዘካቶሊካዊያን በስብከታቸው ስለ መንፈስ ቅዱስና ስለ ቤተሰብ በሰፊው ሰብከዋል፡፡ በተለይም ‹‹ወመንፈሰከ ቅዱሰ ኢታውፅእ እም ላዕሌየ...›› የሚለውን የዕለቱን ምስባክ ጠቅስው ህይወታችን በመንፈስ ቅዱስ ካልተመራ ትርጉም አልባ ነው፡፡ ስለዚህም ‹‹እባክህን መንፈስህን ከእኔ አትውሰድ ከወሰድክ ግን እሞታለሁ...›› ብለን እንማፀነው በማለት ገልጸዋል፡፡ በሌላ በኩል ቤተሰብን አስመልክተው ሲሰብኩ ከሕዝበ ክርስቲያኑ መካከል የተወሰኑትን ቤተሰቦች (አባት፣ እናት፣ ልጅ) ወደፊት እንዲቀርቡ በጋበዙት መሰረት የተለያዩ ቤተሰቦች ወደ እርሳቸው ሲቀርቡ እርሳቸውም በበኩላቸው ከመካከላቸው አንዱን ሕፃን አንስተው በመታቀፍ ‹‹ቤተሰብ የቤተክርስቲያን እስትንፋስ ነው የሀገርም መሰረት ነው፡፡ ቤተሰብ ከሌለ ማህበረሰብ የለም፡፡ ስለዚህ በዛሬ ቀን በመላ ዓለም ቤተክርስቲያን ዘንድ ስለቤተሰብ የሚጸለይበት ቀን ስለሆነ ሁላችንም በመቆም ስለቤተሰብ እንጸልይ ፡፡ ›› በማለት የዕለቱን ቃለ እግዚአብሔር አጠቃለሉ፡፡
መሰዋዕተ ቅዳሴ ከተፈጸመ በኃላ ቅዱስ ቁርባንና የተለያዩ ቅዱሳን ስዕላት በመያዝ በወጣት መዘምራን፣ በያሬዳዊያን እንዲሁም በአባቶችና በእናቶች የተለያዩ ዝማሬዎችና ጸሎት የታጀበ የዑደት ስርዐት በማድረግ በብፁዕ አባታችን በተሰጠ የመጨረሻ የቅዱስ ቁርባን ቡራኬ የዕለቱ የቤተ ክርስቲያን መርኃ ግብር ተጠናቀቀ፡፡ በመጨረሻም ገዳሙንና የቁምስናው ምዕመናን ምክር ቤት በመተባበር ያዘጋጁትን የምሳ ግብዣ (ፀበል ፃዲቅ) ለሁሉም ምዕመናን በማዳረስ በጥሩ ሥነ-ሥርዓት የዕለቱ መርኃ ግብር ተፈጸመ፡፡
የመንዲዳ መድኃኔዓለም ቁምስና ምዕመናንና የደብረብርሃን ቁስቃም ማርያም ምዕመናን በሁለት ትላልቅ አውቶቡሶች በመሆን ያደረጉት የቅዱስ ዮሴፍ ንግሥ መንፈሳዊ ጉዞ ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡ በሌሎችም ዘንድ ቢለመድ ጥሩ ነው የሚል የግል አስተያየት አለኝ፡፡
ከመ በኩሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!!
አባ ተሻለ ንማኒ /ሲታውያን/




