እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

ዘገብር ኄር

ዘገብር ኄር                         የጸጋ "አትራፊ ነጋዴዎች"

ምስባክ - ከመ እግበር ፈቃድከ መከርኩ አምላኪየ፤ ወሕግከኒ በማእከለ ከርስየ፤ ዜኖኩ ጽድቅከ በማኅበር ዐቢይ።

አምላኬ ሆይ ፈቅድህን ለማድረግ ወደድኩ፤ ሕግህም በልቤ ውስጥ ነው፤ በታልቁ ጉባኤም ጽድቅህን ተናገርኩ። መዝ. 40:8

ንባባት፦- 2ጢሞ.2:1-15 - 1ጴጥ.5:1-11- ሐዋ.1:6-8 - ማቴ.25:14-30

three servants

የዚህ ሰንበት ሥያሜ በግእዝ ገብር ኄር ሲሆን ትርጉሙም ታማኝ፣ ቸር አገልጋይ ማለት ነው። በዛሬው ወንጌል ውስጥ በአገልጋይ መልክ የተንጸባረቁት ሦስት ግለሰቦች በተለያየ ዓይነት ደረጃ ክርስቲያኖችን ይወክላሉ። በጥምቀት ጸጋ ክርስቲያን ከሆንን በኋላ እንደ የአናኗራችንና ለተቀበልነው ወይም ለተሰጠን ጸጋ እንደምንሰጠው ምላሽ ሁኔታችን ይለያያል።

እምነታችን ማለትም ክርስትናችን አንዴ ተቀብለነው ምንም መሥራት ወይም መተባበር የማያስፈልገው ነገር ቢሆን ኖሮ ቀላል ነበር። እውነቱ ግን ይህ አይደለም፤ እምነት ጸጋ ነው ስለዚህም በነጻ የተሰጠን ማለት ሲሆን እንደየትብብራችንና ጥረታችን ደግሞ የተቀበልነው ወይም እንዳልተቀበለ ልንሆንበት የምንችለው ነገር ማለት ነው። ስለዚህም የእምነት ጸጋን ከተቀበልን በኋላ ትብብራችንና ጥረታችን እጅጉን እንደሚያስፈልግ ክርስቶስ በዛሬው ወንጌሉ በተናገረው የአገልጋዮች ምሳሌ በግልጽ ይታያል።

አንዴ ክርስቲያን ሆኛለሁና ድኛለሁ ስለዚህም ከአሁን በኋላ እጆቼ ለጭብጨባና ለአምልኮ ብቻ እንጂ ለበጎ ሥራ አይንቀሳቀስም፣ ጌታ እምነትን ሲሰጠኝ ከሥራ ገላገለኝ እንዳንል እምነትን መቀበል ሌላ፤ አማኝ መሆን ደግሞ ሌላ ጉዳይ መሆኑን ያሳየናል። በጾማችን ወቅት የምናደርጋቸው የተለያዩ የ"እምነት ሥራዎች" ዋጋ እንዳላቸው አንጠራጠርም። ይብዛ ይነሥ ግን በአቅማችን መጠን ያተረፍነውን ክርስቶስ ይጠይቀናል። የግድ እንደ እገሌ ባይሆንም እንደ ራሳችን በእምነታችን እንድናተርፍ ጥሪው ይስተጋባል። ወንጌሉ "ወደ ሌላ አገር የሚሄድ አንድ ሰው አገልጋዮቹን ጠርቶ ንብረቱን አስረከባቸው፤ ለእያንዳንዱ እንደ ችሎታው በማካፈል...ሄደ።" ስለዚህ ከችሎታችን በላይ አልተቀበልንምና ከዚያ በላይ አንጠየቅም። ይህ የሕይወት እንጂ የሙያ ጥያቄ አይደለም፤ እያንዳንዳችን ክርስትናችንን የምንተገብርበትን አቅም እግዚአብሔር አልነሳንም።

ታማኝ፣ ሰላማዊ፣ የፍቅር ሰው፣ ታጋሽ፣ ትሑት...መሆን ማለት የክርስትናችን ጸጋ ወይም ስጦታዎች ቢሆኑም ተባብረን ካላሳደግናቸው ግን ምንም ትርጉም የላቸውም። አንድ ሰው ታማኝነቱ፣ አፍቃሪነቱ ወይም ታጋሽነቱ እስኪነካ ድረስ ከሆነ ያው የተሰጠውን ሀብት ቀብሮ ጌታውን የጠበቀው አገልጋይ ቢጤ መሆኑ ነው። ስለዚህ በተሰጠን ጸጋ መኖር ካለብን በዚያ ላይ ሠርተን ማትረፍ ስንችል ነው። አንድ ነጋዴ እውነተኛ ነጋዴ ከሆነ የሚያተርፍበትን ሁኔታዎች ከማውጣትና ማውረድ አእምሮው አያርፍም። ለማትረፍም በእጁ ያለውን ሀብት መጀመሪያ ማውጣት ይኖርበታል፤ ከዚያ ነው ትርፍ የሚከተለው። ይህ ካልሆነ ግን ማለትም ምንም ሳያወጣ ገንዘቡን እንደያዘ ማትረፍ ቢያስብ ነጋዴነቱ ትርጉም የለውም። እኛም ክርስትናችን የሰጠንን ጸጋ አስቀድመን በማድረግ ካልሆነ በሌላ መንገድ ወይም ስለእምነታችን በማውራትና በመመስከር ብቻ ማትረፍ አንችልም። ስለፍቅር፣ ትሕትና፣ ትእግሥት እያወራን በጥላቻና ነቀፌታ የተሞላን፣ ትእቢተኞች፣ አትንኩኝ ባይ... ከሆንን ጸጋችንን በመቅበር የጌታችንን መመለስ እየጠበቅን ሊሆን ይችላልና እግዚአብሔር የሰጠንን ይህንን የጾም ጊዜ ከቃሉና ከቅዱስ ማዕዱ ራሳችንን በመመገብ በሕይወታችን አድራጊዎችና አትራፊዎች መሆንን እንጀምርበት፤ እናሳድግበት።

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት