እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

3.1 - በእግዚአብሔር መንፈስ አነሣሽነትና መሪነት

4 - በእግዚአብሔር መንፈስ አነሣሽነትና መሪነት

 

“ቅዱሳት መጻሕፍት በሙሉ በእግዚአብሔር መንፈስ መሪነት የተጻፈ ነው፤ እርሱ እውነትን ለማስተማር፣ የተሳሳቱትን ለመገሠጽ፣ ስሕተትን ለማረም ለትክክለኛ ኑሮ የሚበጀውን መመሪያ ለመስጠት ይጠቅማል።” (2ጢሞ. 3:16)በዚህ ጥቅስ መጀመሪያ ላይ “በእግዚአብሔር መንፈስ መሪነት” ስንል ምን ማለታችን ነው?

 

በግሪክ ቋንቋ የዚህ 2ጢሞ. “በእግዚአብሔር መንፈስ መሪነት” የሚለው አባባል “በእግዚአብሔር ተንፋሽነት” ይላል።   ስለዚህ በእግዚአብሔር መንፈስ መሪነት የሚለው አባባል በእግዚአብሔር ርዳታ፣ ተቆጣጣሪነት ወይም በእርሱ ስምምነት ከማለት በላይ በጽሑፎቹ ላይ የእሱን ሥልጣንና ድራሲነት ያመለክታል።

 

እግዚአብሔርን “ዋነኛ ደራሲ” ሰውን ደግሞ “መሣሪያዊ ደራሲ” በማድረግ ካቶሊካዊ ትውፊት የመጽሐፍ ቅዱስን “ሁለትዮሽ ደራሲነት” ይናገራል። የእግዚአብሔር የደራሲነት ሥልጣን የጸሐፊው (የሰው) ቃላት የመምረጥ ችሎታ ድረስ ይዘረጋል። ጸሐፊዎቹ እግዚአብሔር የፈለገውን ነገር ሁሉና ብቻ በነጻነት ጽፈዋል።

 

ይህ ጥምር ደራሲነት ታላቅ ምስጢር ነው፤  ይህን ያህልም ታላቅ ምስጢር ከመሆኑ የተነሣ ቤተ ክርስቲያናችን ይህን የእግዚአብሔር ቃል በሰው ቃላት የመገለጥ ሁኔታ ከክርስቶስ ሥጋ የመልበስ (ትሥግውት) እውነታ ጋር ታነጻጽረዋለች። በሁለቱም ሁኔታዎች እግዚአብሔር አብ እንደ እውነተኛ አባት ከልጆቹ ጋር ለመገናኘት ራሱን ዝቅ ማድረጉ ይታያል።

 

ሥጋ የለበሰው “ቃል” (ክርስቶስ) እና በእግዚአብሔር ዋነኛ ደራሲነት የተጻፈው “ቃል” ሁለቱም ፍጹም አምላክና ፍጹም ሰብአዊ ባሕርይ አላቸው። በሁለቱም ውስጥ ሰብአዊውና መለኮታዊው አይለያዩም፤ በሁለቱም ውስጥ ሰዋዊው ባሕርይ መለኮታዊውን ለማስተላለፍ ይጠቅማል።

 

የመጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ደራሲነትም ሆነ የወልደ እግዚአብሔር ሥጋ መልበስ መለኮታዊ ግልጸት እንደመሆናቸው መጠን ሊታወቁ የሚችሉት በእምነት ብቻ ነው፤ ከእምነት ውጭ በሆነ ሰዋዊ ነገር ሊታወቁ አይችሉም። ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፒዮስ 12ኛው “ከኃጢአት በቀር የእግዚአብሔር ቃል (ክርስቶስ) በሁለ ነገሩ ሰው እንደሆነ ሁሉ በሰው ቋንቋ የተገለጸው የእግዚአብሔርም ቃል (በመጽሐፍ ቅዱስ) ከስህተት በስተቀር በሁለንተናው የሰው ልጅ ንግግርን ሆነ” ይላሉ።

 

በርግጥ መጽሐፍ ቅዱስ ስህተት የለሽ ነው፤ ር.ሊ.ጳ. ሌዮ 13ኛውም የመጽሐፍ ቅዱስ ውስጣዊ ይዘት ስህተት የለሽ መሆኑ ከእግዚአብሔር ደራሲነት የተነሣ ነው በማለት ይገልጻሉ (እግዚአብሔር የመጽሐፍ ቅዱስ ዋነኛ ደራሲ ከሆነ ስህተት መጠበቁ መሳሳት ነው)። እንዲሁም “በእግዚአብሔር መንፈስ መሪነት ተጻፈ የሚለው ሀሳብና ስህተት አብረው ሊሄዱ የማይችሉ ነገር ናቸው” ይላሉ።

 

ሆኖም ግን ይህ “ስህተት የለሽ” የሚለው አባባል ገና ሙሉ ለሙሉ በበቂ ሁኔታ የመጽሐፍ ቅዱስን ባሕርይ አይገልጸውም። ምክንያቱም ሌሎች መጻሕፍትም ስህተት ላይኖራቸው ይችላል፤ ለምሳሌ በጥንቃቄ እርማትና አርትዖ የተደረገለት የሂሳብ መማሪያ መጽሐፍ በይዘቱ ስህተት ላናገኝለት እንችላለን። ትልቁ የመጽሐፍ ቅዱስ መለያ እግዚአብሔር ዋነኛ ደራሲው መሆኑ ነው፤ ሌላ ማንኛውም መጽሐፍ እግዚአብሔር ደራሲው የሆነለትና የእሱን የማዳን ኃይል በምልአት የሚያስተላልፍ የለም። ኢየሱስ ራሱ ሲመሰክር “ሕይወትን የሚሰጥ የእግዚአብሔር መንፈስ ነው፤ የሰው ኀይል ግን ለምንም አይጠቅምም። እኔ ለእናንተ የተናገርሁት ቃል ሕይወትን የሚሰጥ መንፈስ ነው” (ዮሐ.6:63) ይላል። መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔርን ቃል ለሰው ልጆች ደኅንነት በማስተላለፉ ረገድ ልክ እንደ ቤተ ክርስቲያናችን ምስጢራት ልንመስለው እንችላለን።

የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት - ብሉይና አዲስ ኪዳናት 

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት