2:1 - በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ለምን ሁለት ኪዳናት ኖሩ?
- Category: መጽሐፍ ቅዱስን ለመረዳት - ባጭሩ
- Published: Tuesday, 01 December 2009 08:48
- Written by Super User
- Hits: 8606
- 01 Dec
2:1 - በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ለምን ሁለት ኪዳናት ኖሩ?
በመጀመሪያ ደረጃ ለምን ብሉይና አዲስ ኪዳን? አዲስ ኪዳን ካለን ብሉይ ኪዳን ለምን አስፈለገ? የሚል ሀሳብ ሊነሣ ይችል ይሆናል።
መልሱ አንዱ ኪዳን ያለ ሌላው ሙሉ መሆን አይችልም፤ ጎዶሎ ነው። ሁለቱ ኪዳናት የአንዱ እግዚአብሔር ብቸኛ እቅድ ማስፈጸሚያ ናቸው። ቅዱስ አውጎስጢኖስ አዲስ ኪዳን በብሉይ ኪዳን ውስጥ ተደብቆ አለ፤ ብሉይ ኪዳን ደግሞ በአዲስ ኪዳን ውስጥ ተገልጧል ይላል።
ኢየሱስ በትንሣኤው ዕለት የብሉይ ኪዳን ትንቢቶች መፈጸም እንደነበረባቸው አስረዳ፦ “እናንተ የማታስተውሉና ነቢያት የተናገሩትንም ሁሉ ከማመን የዘገያችሁ! መሲሕ ይህንን ሁሉ መከራ መቀበልና ወደ ክብሩ ምግባት ይገባው የለምን? ከዚህ በኋላ ከሙሴና ከነቢያት መጻሕፍት ጀምሮ በቅዱሳት መጻሕፍት ሁሉ ስለ እርሱ የተነገረውን እየጠቀሰ አስረዳቸው።” (ሉቃስ 24:25-27)። እንዲሁም የመጀመሪያዎች ክርስቲያኖች ብሉይ ኪዳንን በስብከታቸው እንዴት እያያዙ ይጠቀሙበት እንደነበረ ጥሩ ምሳሌ የሚሆነን በሐዋ. ሥራ 2:14-36 የምናገኘው የቅዱስ ጴጥሮስ ስብከት ነው።
ይህ ማለት መሠረታዊና ዋነኛ የሆነውን የክርስቲያን መልእክት ከብሉይ ኪዳን ውጭ መረዳት አንችልም ማለት ነው፣ አዲስ ኪዳን ብሉዩን ያድሰዋል፣ ፍጹም ያደርገዋልም እንጂ ሊያጠፋውና ሊደመስሰው አልመጣም።
በርግጥም መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ስንጀምር በሁለቱ ኪዳናት መካከትል ያለው ቅርብ ግንኙነትን ማስተዋል እንጀምራለን። ከጊዜ ወደ ጊዜ በአንደኛው ኪዳን ውስጥ የሚከናወኑት ሁኔታዎች በሌላኛው ኪዳን ውስጥ የሚገኙ ተመሳሳይ ሁኔታዎችን እያስታወሰን ይመጣል። ክርስቲያን ነገረ መለኮታውያን (Theologians) ይህን ትስስር Typology ይሉታል። ይህም መጀመሪያ የሚመጡ ነገሮች ኋላ ሊመጣ ያለውን ነገር ማንጸባረቅ ሲችሉ ማለት ነው። ለምሳሌ ፦ በዘፍጥረት 22:1-19 የምናገኘው የይስሐቅ መሥዋዕትነትን ከዘመናት በኋላ የሆነውን የክርስቶስ የመስቀል መሥዋዕት አስቀድሞ እንዳንጸባረቀ ወይም ዓይነቱን እንደገለጸ ክርስቲያኖች ያያሉ። ይህ ዝም ብሎ መመሳሰል ብቻ ሳይሆን በርግጥ ለአብርሃምና ለይስሐቅ የተከናወነ እውነተኛ ታሪክ ነው። ልክ እንደ ጥሩ ችሎታ እንዳለው ደራሲ ሴራው የኋላ እቅዱን የበለጠ እንዲያስረዳ እንደሚጠቀምበት ሁሉ እግዚአብሔርም እውነተኛ ታሪክን እንዲሁ ይጠቀምበታል።
አዲሱ የካቶሊክ ቤተ ከርስቲያን ትምህርተ ክርስቶስ በቁ.130 ላይ እንደዚህ ዓይነት የመጽሐፍ ቅዱስ ተመሳሳይነት ያላቸው ታሪኮች ወደ መጨረሻው ፍጽምና የመጓዝ እንቅስቃሴ መሆኑን ይገልጻል። ይህ ምስስል ጠቅላላና ብቸኛ የሆነው የእግዚአብሔር የማዳን እቅድን ወጥ አሠራርን ያሳያል። የአብርሃም መሥዋዕት እስራኤላውያን ከግብጽ ሲወጡ የሰዉትን የፋሲካ ጠቦት አስቀድሞ ያሳያል፤ እንዲሁም ደግሞ የኋላ ኋላ ልክ አብርሃም ይስሐቅን ለመሠዋት በተዘጋጀበት ቦታ በታነጸው በኢየሩሳሌሙ ቤተ መቅደስ የተደረጉትን የእንስሳት መሥዋዕት አስቀደሞ ያመላከተም ነበር። በመጨረሻም ታላቁ የዚህ መሥዋዕት ፍጽምና የሆነውን የክርስቶስን መሥዋዕትነት ያሳያል፤ ወደዚሁም ይመራል። ዛሬም ቢሆን ቤተ ክርስቲያን በመሥዋዕተ ቅዳሴ ጊዜ በሚሠዋው “የእግዚአብሔር በግ” በቅዱስ ቁርባን ይህን መሥዋዕትነት በመቀጠል ላይ ትገኛለች። ስለዚህ ከይስሐቅ መሥዋዕትነት እስከ ዛሬው የቅዱስ ቁርባን ክርስቶሳዊ መሥዋዕትነት ድረስ ተመሳሳይነትና ቀጣይነት አንዱ ሌላውን ፍጹም እያደረገ የእግዚአብሔር የማዳን እቅድ በዘመናት ለትውልድ ሁሉ ይከናወናል ማለት ነው።