እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

የፊልጶስ ፡ ፈተና ፡ እና ፡ የእንድርያስ ፡ ጭንቀት (ዮሐ 6 ፡ 1-15)

የፊልጶስ ፡ ፈተና ፡ እና ፡ የእንድርያስ ፡ ጭንቀት (ዮሐ 6 ፡ 1-15)

በዚህኛው ፡ የጥናታችን ፡ ክፍል ፡ የምናየው ፡ በወንጌሉ ፡ ሐተታ ፡ ሂደት ፡ ውስጥ ፡ ኢየሱስ ፡ ከሁለቱ ፡ ደቀ ፡ መዛሙርት ፡ ከፊልጶስና ፡ ከእንድርያስ ፡ ጋር ፡ በሚያደርገው ፡ ውይይት ፡ ዙርያ ፡ ይሆናል ፡፡ ኢየሱስ ፡ ከአምስት ፡ ሺህ ፡ ሕዝብ ፡ በላይ ፡ በአምስት ፡ ትንንሽ ፡ የገብስ ፡ እንጀራና ፡ በሁለት ፡ ዓሣ ፡ ተመግበው ፡ እንዲረኩ ፡ ካረገ ፡ በኋላ ፡ ዐሥራ ፡ ሁለት ፡ መሶብ ፡ ሙሉ ፡ ቁርስራሽ ፡ መሰብሰቡን ፡ የሚገልጸውን ፡ ታሪክ ፡ በአራቱም ፡ ወንጌላውያን ፡ ተደጋግሞ ፡ ተጽፎአል (ማቴ 14 ፡ 12 ማር 6 ፡ 32 ሉቃ 9 ፡ 10) ፡፡ ነገር ፡ ግን ፡ ወንጌላዊው ፡ ዮሐንስ ፡ በዚህ ፡ ታሪክ ፡ ውስጥ ፡ በተለየ ፡ መልኩ ፡ የተለያዩ ፡ ተጨማሪ ፡ መልእክቶች ፡ ለማስተላለፍ ፡ በማለት ፡ የሚያክላቸው ፡ ተጨማሪ ፡ ነገሮች ፡ አሉ ፡፡ ከእነዚህም ፡ ውስጥ ፡ አንዱ ፡ እዚያ ፡ ቦታ ፡ ላይ ፡ ከነበሩት ፡ ሐዋርያቶች ፡ ውስጥ ፡ የተወሰኑትን ፡ ለይቶ ፡ በሥማቸው ፡ መጥራትና ፡ ከኢየሱስ ፡ ጋር ፡ ውይይት ፡ ማድረጋቸውን ፡ አንዱ ፡ ነው ፡፡ በዚህ ፡ ታሪክ ፡ ውስጥ ፡ በመጀመርያ ፡ ሥሙ ፡ የተጠራው ፡ ሐዋርያው ፡ ፊልጶስ ፡ ሲሆን ፡ ቀጥሎም ፡ እንድርያስ ፡ ነው ፡፡ ወንጌላዊው ፡ ዮሐንስ ፡ ለምን ፡ እነሱን ፡ ብቻ ፡ ለይቶ ፡ በሥማቸው ፡ በመጥራት ፡ ከኢየሱስ ፡ ጋር ፡ እንዲወያዩ ፡ አደረጋቸው ? እነዚህ ፡ ሁለት ፡ ሐዋርያቶች ፡ ከሌሎች ፡ ሐዋርያቶች ፡ ለየት ፡ የሚያደርጋቸው ፡ ነገር ፡ ነበርን ?

እንድርያስ

እንደ ፡ ወንጌላዊው ፡ ቅ. ዮሐንስ ፡ አገላለጽ ፡ እንድርያስ ፡ ግንባር ፡ ቀደም ፡ ከሁሉም ፡ ሐዋርያቶች ፡ የመጀመርያው ፡ የጌ.ኢ.ክ ፡ ደቀ ፡ መዝሙር ፡ ነው (ዮሐ 1 ፡ 40) ፡፡ መጥምቁ ፡ ቅ.ዮሐንስ ፡ ኢየሱስ ፡ ባጠገቡ ፡ ሲያልፍ ፡ አይቶ ፡ « እነሆ ! የእግዚአብሔር ፡ በግ ›› ብሎ ፡ ሲመሰክር ፡ በመስማቱ ፡ እንድርያስ ፡ ሁሉንም ፡ ነገር ፡ በመተው ፡ ኢየሱስን ፡ መከተል ፡ ጀመረ ፡፡ ኢየሱስም ፡ ዞር ፡ ብሎ ፡ « ምን ፡ ትፈልጋላችሁ ›› ብሎ ፡ ሲጠይቃቸው ፡ « ረቢ ፡ የት ፡ ትኖራለህ ›› አሉት ፤ ኢየሱስም ፡ ኑና ፡ እዩ ፡ አላቸው (ዮሐ 1 ፡ 35 – 39) ፡፡ እንድርያስም ፡ ሁሉን ፡ ነገር ፡ እርግፍ ፡ አርጎ ፡ በመተውና ፡ የመጀመርያው ፡ ሐዋርያ ፡ በመሆን ፡ ኢየሱስን ፡ ከመከተሉም ፡ አልፎ ፡ በፍጥነት ፡ ወደ ፡ ወንድሙ ፡ ስምዖን ፡ ጴጥሮስ ፡ በመሄድ « መሲሑን ፡ አገኘነው ›› በማለት ፡ ስምዖን ፡ ጴጥሮስን ፡ ወደ ፡ ኢየሱስ ፡ ያመጣ ፡ ቀደምት ፡ ሐዋርያ ፡ ነው (ዮሐ 1 ፡ 42) ፡፡ እዚህ ፡ ላይ ፡ ማስተዋል ፡ ያለብን ፡ አንደ ፡ ዮሐንስ ፡ ወንጌል ፡ አገላለጽ ፡ እንድርያስ ፡ ከመጀመርያዎቹም ፡ የመጀመርያ ፡ ሐዋርያ ፡ ከመሆኑም ፡ በላይ ፡ ኢየሱስን « ከእግዚአብሔር ፡ የተቀባው ፡ ብቸኛ ፡ መሲሕ ›› እንደሆነ ፡ ለይቶ ፡ ያወቀና ፡ ለመጀመርያ ፡ ጊዜ ፡ ለምስክርነት ፡ ወደ ፡ ሌሎች ፡ ዘንድ ፡ በመሄድ ፡ መልካሙን ፡ ዜና ፡ በማብሰርና ፡ ወደ ፡ ኢየሱስ ፡ ዘንድ ፡ እንዲመጡ ፡ በመጋበዝ ፡ ታጥቆ ፡ የተነሳ ፡ ሐዋርያ ፡ ነበር ፡፡ ይህም ፡ ማለት ፡ ኢየሱስ ፡ ሁሉን ፡ አድራጊና ፡ በሁሉም ፡ ነገር ፡ ላይ ፡ ሀይልና ፡ ሥልጣን ፡ ያለው ፡ ሁሉንም ፡ ማከናወን ፡ የሚችል ፡ መሆኑን ፡ ከማንም ፡ በፊት ፡ በመረዳቱ ፡ አየሱስን ፡ መከተል ፡ የጀመረና ፡ ለሌሎችም ፡ መንገድ ፡ ጠራጊ ፡ ሆኖ ፡ የሚታይ ፡ ሐዋርያ ፡ ነው ፡፡ ታድያ ፡ በዚህ ፡ ታሪክ ፡ ውስጥ ፡ ከሌሎች ፡ በተለየ ፡ መልኩ ፡ ሥሙን ፡ መጠቀሱ ፡ ለምንድን ፡ ነው ? ከፊልጶስስ ፡ ጋር ፡ የሚያመሳስለው ፡ ነገር ፡ ምንድን ፡ ነው ? ቀድመን ፡ የፊልጶስን ፡ ማንነትና ፡ የጥሪው ፡ ጉዞ ፡ እንመልከትና ፡ ወደ ፡ ጥያቄው ፡ መልስ ፡ እናመራለን ፡፡

ፊልጶስ

ፊልጶስ ፣ እንድርያስና ፡ ስምዖን ፡ ጴጥሮስ ፡ የአንድ ፡ መንደር (የቤተ ፡ ሳይዳ) ፡ ሰዎች ፡ ናቸው ፡፡ ፊልጶስ ፡ ከእንድርያስና ፡ ከጴጥሮስ ፡ በኋላ ፡ ለሐዋርያነት ፡ አገልግሎት ፡ ለመጀመርያ ፡ ጊዜ ፡ በቀጥታ ፡ በኢየሱስ ፡ የተጠራ ፡ ሐዋርያ ፡ ነው (ዮሐ 1 ፡ 43) ፡፡ እንደ ፡ ወንጌላዊው ፡ ቅ.ዮሐንስ ፡ አገላለጽ ፡ ለመጀመርያ ፡ ጊዜ ፡ በኢየሱስ ፡ እይታ ፡ ውስጥ ፡ ገብቶ ፡ የተመረጠ ፣ ለአገልግሎት ፡ የታጨና ፡ እሱ ፡ ምንም ፡ አይነት ፡ ጥያቄ ፡ ሳያቀርብ ፡ ወይም ፡ አንድም ፡ ቃል ፡ ሳይናገር ፡ በኢየሱስ ፡ ተፈልጎ ፡ የተገኘና ፡ « ና ፡ ተከተለኝ ›› የተባለ ፡ የመጀመርያውና ፡ ብቸኛው ፡ ሐዋርያ ፡ ነው (ዮሐ 1 ፡ 43) ፡፡ በሌላ ፡ አገላለጽ ፡ እንደ ፡ ወንጌላዊው ፡ ቅ.ዮሐንስ ፡ አገላለጽ ፡ ትንተና ፡ ፊሊጶስ ፡ በኢየሱስ ፡ በቀጥታ « ተከተለኝ ›› ተብሎ ፡ የተጠራ ፡ ብቸኛው ፡ ሐዋርያ ፡ ነው ፡፡ በሌላ ፡ በኩል ፡ በዮሐንስ ፡ ወንጌል ፡ ውስጥ ፡ ሌሎቹ ፡ ሐዋርያቶች ፡ እንዴት ፡ እንደተጠሩና ፡ እንዴት ፡ ኢየሱስን ፡ መከተል ፡ እንደጀመሩ ፡ በግልጽ ፡ አይታወቅም ፡፡

ፊሊጶስም ፡ ልክ ፡ እንደ ፡ እንድርያስ ፡ ኢየሱስን ፡ ካገኘው ፡ በኋላ ፡ ሳይዘገይ ፡ ወድያውኑ ፡ ሲመሰከርና ፡ ናትናኤልን ፡ ወደ ፡ ኢየሱስ ፡ እንዲመጣ ፡ ሲጋብዝ ፡ ይገኛል (ዮሐ 1 ፡ 45) ፡፡ ልክ ፡ እንድርያስ « መሲሑን ፡ አገኘነው ›› ብሎ ፡ ለወንድሙ ፡ ለጴጥሮስ ፡ መስክሮለት ፡ እንደነበር ፡ ሁሉ ፡ ፊልጶስም ፡ ለናትናኤል « ሙሴ ፡ በሕግ ፡ መጻሕፍት ፣ ነቢያትም ፡ ስለ ፡ እርሱ ፡ የጻፉለትን ፡ የዮሴፍ ፡ ልጅ ፡ የናዝሬቱ ፡ ኢየሱስን ፡ አገኝተነዋል ››  በማለት ፡ ነበር ፡ የመሰከረውና ፡ ወደ ፡ ኢየሱስ ፡ እንዲመጣ « መጥተህ ፡ እይ ›› በማለት ፡ የጋበዘው ፡፡ ስለዚህ ፡ እንደ ፡ ወንጌላዊው ፡ አገላለጽ ፡ እንድርያስና ፡ ፊልጶስ ፡ ከመጥምቁ ፡ ቅ. ዮሐንስ ፡ በኋላ ፡ ከየትኞቹም ፡ ሐዋርያቶች ፡ በፊት ፡ ስለ ፡ ኢየሱስ ፡ ማንነት ፡ ጠንቅቀው ፡ የተረዱና ፡ ወድያውኑ ፡ መመስከር ፡ የጀመሩ ፡ ሐዋርያቶች ፡ በፊት ፡ ስለ ፡ ኢየሱስ ፡ ማንነት ፡ ጠንቅቀው ፡ የተረዱና ፡ ወድያውኑ ፡ መመስከር ፡ የጀመሩ ፡ ሐዋርያቶች ፡ ናቸው ፡፡ ይህም ፡ ማለት ፡ ኢየሱስ ፡ የእግዚአብሔር ፡ ልጅ ፡ መሆኑን ፣ በምድር ፡ ላይ ፡ የሥልጣን ፡ ሁሉ ፡ ባለቤት ፡ ሁሉንም ፡ ማዘዝና ፡ ማከናወን ፡ የሚችል ፡ ፍጹም ፡ አምላክ ፡ ፍጹም ፡ ሰው ፡ መሆኑን ፡ የተረዱ ፡ የመጀመርያዎቹ ፡ ሐዋርያቶች ፡ ናቸው ፡፡ ይህንን ፡ ተረድተው ፡ ጉዞ ፡ የጀመሩት ፡ ዛሬ ፡ በዮሐ 6 ፡ 1-15 ፡ ላይ ፡ ፈተና ፡ ውስጥ ፡ ሲገኙ ፡ አስተሳሰባቸውና ፡ የመፍትሄ ፡ አፈላለጋቸው ፡ ወይም ፡ ደግሞ ፡ ያንን ፡ ከማንም ፡ በፊት ፡ አምነው ፡ የተከተሉትን ፡ ኢየሱስ ፡ ላይ ፡ ያላቸው ፡ እምነት ፡ ምን ፡ ይመስላል ፡ የሚለው ፡ ሀሳብ ፡ ሳይሆን ፡ አይቀርም ፡ ወንጌላዊው ፡ ሊያተኩርበት ፡ የፈለገው ፡፡ ለዚህም ፡ ይመስላል ፡ ወንጌላዊው ፡ የእነሱን ፡ ሥም ፡ ብቻ ፡ በመጥቀስ ፡ ከኢየሱስ ፡ ጋር ፡ እንዲወያዩ ፡ የሚያደርጋቸውና ፡ ኢየሱስ ፡ ላይ ፡ ያላቸውን ፡ እምነት ፡ ምን ፡ እንደሚመስል ፡ ለማሳየት ፡ የሚሞክረው ፡፡

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት