ቅዱስ ቆጵርያኖስ (Saint Cyprian) - መስከረም 1

ቅዱስ ቆጵርያኖስ (Saint Cyprian) 

Saint of the dayመስከረም 1 - ቅዱስ ቆጵርያኖስ (St. Cyprian) ካርቴጅ በሰሜን አፍሪካ (የዛሬዋ ቱኒዚያ) ተወልደ፣ የኖረበት ዘመን 3ኛ ክፍለ ዘመን ነበር ። አወላለዱም ከሀብታም አረመኔያዊ ቤተሰብ ነበር ። ክርስትናን እንደተቀበለም ያለውን ንብረቶች ሁሉ ለድሆች በመስጠት ከዚያም አልፎ እስክሚጠመቅ ድረስ ንጽሕናውን/ድንግልናውን ለመጠበቅ ቃለ መሐላ በማድረግ የሚያውቁትን ሰዎች አስገርሟል ። በሁለት ዓመት ውስጥ ቅስናን ተቀብሎ ግን ያለፍላጎቱ የካርቴጅ (Carthage) ጳጳስ ተደርጎ ተሾመ ።

           ቅ. ቆጵርያኖስ በቤተ ክርስትያኗ የነበረው ሰላም በመዳከሙና በመደፍረሱ የተቃውሞ ድምጹን ያሰማ ነበር ። ምክንያቱም ቤተ ክርስትያኗ ለብዙ አዲስ አማኞች የእውነት መንፈስ ሳይኖራቸው በሯን በመክፍቷ ነበር ። የሮማው ንጉስ ዲሲየስ ክርስትያኖችን ማሳደድ ሲጀምር፣ ብዙ ክርስቲያኖች እምነታቸውን በመተው ከቤ/ክ ሽሹ ። በዚህ በ3ኛ ክፍለ ዘመን ነበር አከራካሪው ጥያቄ የተነሳው። ይኸዉም እነዚህ እምነታቸውን ክደው የነበሩት ወደ ቤ/ክ ሲመለሱ ቤተክርስቲያኗ እንዴት ነው የምትቀበላቸው የሚል ነበር። በዚህ ምክንያት ነበር የምስጢረ ንስሐ አስተሳሰብ በወቅቱ በውስጡ እያደገበት የመጣው ።

           ኖቫቱስ የተባለ ካህን የቆጵርያኖስ ጵጵስናን ከመጀመሪያው ሲቃወም የነበረ ነው። ቆጵርያኖስ በስደት ላይ ሆኖ ከተደበቀበት ቦታ ከርቀት ቤተክርስቲያኗን ይመራ ነበር ። ሁኔታው እንዲህ እያለ ኖቫቱስ ቆጵርያኖስ በሌለበት እነዚያ እምነታቸውን ክደው የነበሩትን ሰዎች ምንም ቀኖናዊ ንስሐ ሳያደርጉ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲመለሱ አደረገ ። በመጨረሻ ግን ተወግዟል። ቆጵርያኖስ ግን ጣዖትን ሲያመልኩና ለጣዖት ሲገብሩ የነበሩትን እነዚህን ሰዎች፣ ቅዱስ ቁርባን በሞታቸው ጊዜ ብቻ እንዲቆርቡ፣ ሌሎች ደግሞ ጣዖት ሳያመልኩ ግን አምልከናል ብለው የምስክር ወረቀት ያላቸው ከረጅም የንስሐ ጊዜ በኋላ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲመለሱ የሚል አቋም ነበረው ። ይህ የምስክር ወረቀት የነበራቸው ሰዎች፣ ንጉሥ ዲሲየስ በሚያሳድዳቸው ጊዜ የገዙት ነበር ።

           ቆጵርያኖስ የር.ሊ.ጳ. ኮርኒለስ ጓደኛ ነበር፤ ይሁንና ር.ሊ.ጳ. ኮርኒለስን የተካው ር.ሊ.ጳ. እስጢፋኖስ ጥምቀትን በሚመለከት ከቆጵርያኖስ ጋር ይቃረኑ ነበር ። ቆጵርያኖስና ሌሎች የአፍሪካ ጳጳሳት በመናፍቃንና ከቤተ ክርስቲያን በተገነጠሉት አማኞች የተደረገ የጥመቀት ሥርዓትን ስለማይቀበሉ ነው። በዚህ ጊዜ ር.ሊ.ጳ. እስጢፋኖስ ቆጵርያኖስን ከቤ/ክ አስወጥሃለሁ እያለ ያስፈራራው ነበር ። ግን ቆጵርያኖስ አልተበገረም ።

           ለሁለተኛ ጊዜ ክርስትያኖችን የማሳደድ እርምጃ በጊዜው በነበረው ንጉሥ ተጀመረ። ቆጵርያኖስም ጣዖትን አላመልክም በማለት ራሱን ተቆርጦ እራሱን መስዋዕት አድርጎ ለሌሎች ምሳሌ ሆኗል። ቆጵርያኖስ ትሁት ሆኖም ግን ቆራጥ፣ ኃይለኛና አቋም ያለው፣ እንዲሁም ደስተኛና ቆፍጣናም ነበር ። በዚህ በተለያዩ ፀባዮች ምክንያት ሰዎች ለሱ ያላቸው ስሜት በፍቅር ይሁን በአክብሮት በምን መልኩ መቅረብ ግራ ይገባቸው ነበር ።

ትርጉም፦ ዮሴፍ ወልደዮሐንስ