እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

ዐቢይ ጾም 1ኛ ቀን

ዐቢይ ጾም

ዐቢይ ጾም(1 ቀን)Lent-main-image

በመጀመርያዎቹ ሦስት መቶ ዓመታት በጥንታዊቷ ቤተ ክርስትያን ክርስትያኖች ለፋሲካ በዓል የሚያደርጉት ዝግጅት ከሁለት እስከ ሦስት ቀን ቢበዛ ደግሞ ለአንድ ሳምንት የሚዘልቅ መንፈሳዊ ዝግጅት ነበር። የሊዮኑ ቅዱስ ኤሬኒዮስ (140-202 ዓ.ም.) በጽሑፎቹ  የጥንት ክርስትያኖችን ልምምድ በሚመለከት የ40 ሰዓት የጾም-ጸሎት ዝግጅት ያደርጉ እንደነበረ ያወሳል። ዐቢይ ጾም ለዐርባ ቀናት የሚዘልቅ የጾም-ጸሎት ጊዜ ሆኖ በቀኖና ቤተ ክርስትያን የተወሰነው በ325 ዓ.ም. በኒቂያ ጉባዔ ነው። ከዚህም በመነሳት ከ፬ተኛው ክፍለ ዘመን ማብቂያ አንስቶ ዐቢይ ጾም አሁን ባለው ይዘት ለዐርባ ቀናት ያህል የሚዘልቅ የቤተ ክርስትያን የጾም-ጸሎት ጊዜ ሆኖ በቤተ ክርስትያን ሕይወት ውስጥ ተገልጦ ይገኛል።

ይህ የጾም-ጸሎት ወቅት በተለይ አዲስ ወደ ቤተ ክርስትያን ሕብረት የሚጨመሩ ንዑስ ክርስትያኖች ምሥጢረ ጥምቀት ከሚቀበሉባት ከትንሳኤ ሌሊት ሥርዐተ አምልኮ ጋር ተያይዞ ቤተ ክርስትያን በልዩ መንፈሳዊ ተጋድሎ የምትጓዝበት የጸጋ ወቅት ሆኗል። በዚህ አይነት የተጠመቁ እና የቤተ ክርስትያን ሕብረት ውስጥ የሚገኙት በምሥጢረ ጥምቀት ለሚሆነው የአዲስ ልደት ሕይወት ከሚዘጋጁት ወንድሞች ጋር የጾም-ጸሎት  ሕብረት የሚያደርጉበት፣ የቤተ ክርስትያን አይነተኛ መልክ የሚገለጥበት መንፈሳዊ ሱታፌ ሆኗል። ከዚህ ጊዜ ጅምሮ ዐቢይ ጾም አሁን ያለውን ገጽታ እንደያዘ ቀስ በቀስ በቤተ ክርስትያን እና በአማኞች ሕይወት ውስጥ ይበልጥ ሕያው እየሆነ መጥቷል።

ጾም ከመደበኛው የጊዜ ቀመር ዑደት በጸጋ ወደሆነው የጊዜ ዑደት የሚደረግ ጉዞ ነው። ጾም ከሕይወት አንድ ምዕራፍ ወደ ሌላኛው የጸጋ ሕይወት ምዕራፍ የምንጓዝበት የእምነት፣ የተስፋ እና የፍቅር ልምምድ ወቅት ነው። የዚህ ጉዞ አይነተኛ ገጽታ በጽሞና፣ በጾም፣ በጸሎት፣ በቅዱሳት ንባባት፣ በሥርዐተ አምልኮ ንቁ ተሳትፎ የተሞላ ሆኖ የሚገለጥ፤ ሕይወት ፊቷን ወደ እግዚአብሔር ፊት የምታስተካክልበት፣ የቀደመውን ፍቅሯን የምታድስበት፣ ከጸጋ ሙላት የምትካፈልበት፣ በንስሐዋ መንበርከክ የምትታደስበት፣ የምትጎበኝበት ዘመኗ፣ የተወደደችው የእግዚአብሔር ዓመት ናት።

ጾም፣ ጸሎት፣ ንስሐ እና ምጽዋት ከፍ ብለን የምንበርባቸው መንፈሳዊ ክንፎች ናቸው። በእነዚህ መንፈሳዊ ክንፎች ታግዘን፣ በአእምሮአችን መታደስ እየተለወጥን እና በላይ በሰማያት ያሉትን፣ ከፍ ያሉትን ሐሳቦች በልባችን ጠብቀን እያሰላሰልን ወደ እግዚአብሔር ልብ እንጠጋለን። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በገሊላ ክፍለ ሀገር ያደረገው ጥሪ በዚህ በዐቢይ ጾም ወቅት ለእያንዳንዳችን በተለየ መልኩ ይቀርብልናል። ይኸውም “ዘመኑ ተፈጸም፤ የእግዚአብሔር መንግሥት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ፤ በወንጌልም እመኑ” (ማር 1፡ 14-15) የሚለው የንስሐ እና ራስን በእግዚአብሔር ቃል ብርኀን የማስተዋል ጥሪ ነው። ይህ ጥሪ የዐቢይ ጾም መክፈቻ አዋጅ እና የጾም-ጸሎታችን መሰረታዊ ቁም ነገር ነው።

ዐቢይ ጾም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በገዳመ ቆሮንጦስ ያደረገውን ጾም-ጸሎት በገዛ ሥጋችን የምንለማመድበት እና ጌታን በሕማሙ፣ በሞቱ እና በትንሳኤው የምንመስልበት የመንፈሳዊ ሕይወት ሁሉ አብነት ትምህርት ቤት ነው። ዐቢይ ጾም የጸጋ ወቅት እንደመሆኑ መጠን ነፍስ ለእግዚአብሔር ጸጋ የተዘጋጀች፣ በንስሐ የተሞሸረች፣ ለአዲስ የትንሳኤ ሕይወት ዐይኖቿ በእግዚአብሔር ቃል የተኳሉ፣ እግርቿ በእግዚአብሔር መንግሥት ውስጥ የተተከሉ፣ ኅያው እና ዘላለማዊ የሚያደርጋትን በዔደን ገነት መካከል የተተከለውን የሕይወት ዛፍ እርሱም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በመሥዋዕተ ቅዳሴ ገበታ ያለማቋረጥ የምትመገብበት፣ የእግዚአብሔርን መንግሥት እስከ ዓለም ዳርቻ የምትሰብክበት፣ የሕማሙ፣ የሞቱ እና የትንሳኤው ምሥክር እና ሐዋርያ ሆና የምትሰራበት የጸጋ ሙላት ዘመን ሥጦታ ነው። በዚህም ለኢየሱስ ክርስቶስ ቃል እና ምሥጢር ራሳችንን ዕለት ዕለት በእምነት መታዘዝ እያስገዛን፣ እርሱ በእኛ ውስጥ እኛም ደግሞ በእርሱ ውስጥ ኅያዋን እንሆን ዘንድ ይህንን ዐቢይ ጾም በሰላም። በእምነት፣ በተስፋ እና በፍቅር እንጓዝ።

መልካም የተባረከ የዐቢይ ጾም ጉዞ

ሴሞ

ተመሳሳይ ርእሶች

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት