ሰሙነ ሕማማት
- Category: የ ፵ ጾም አሰተንትኖ
- Published: Monday, 14 April 2025 07:01
- Written by Samson
- Hits: 52
- 14 Apr
ሰሙነ ሕማማት
ሆሳዕና ጌታ በምድር ላይ የቀሩት ስድስት ቀናት መጀመርያ ነው። ጊዜው ለቤተ መቅደስ መሥዋዕት የሚቀርብበት በዓል ሰሞን ነው። ሰዎች በታላቅ ደስታ ወደ ኢየሩሳሌም የሚገቡበት እና የመኸር ምሥጋና የሚያቀርቡበት የምሥጋና በዓል ሳምንት ነው። ከዚህ ጎን ለጎን ኢየሱስ አልዓዛርን ከሞት የማስነሳቱ ተዓምር ዜና በኢየሩሳሌም ሁሉ ተስፋፍቶ ነበር። ወንጌል እንደሚመሰክረው ብዙዎች ከሞት የተነሳውን አልዓዛርን ለማየት ወደ ቢታኒያ ይሄዱ ነበር። በመሆኑም ኢየሱስን ለመቀበል እና እርሱን ለማየት እጅግ ብዙ ሕዝብ ይመኝ ነበር። ስለዚህ ኢየሱስ በአህያ ውርንጫ ላይ ተቀምጦ እንደ ሰላም ንጉሥ በምሥራቁ በር በኩል በመምጣቱ ሕዝቡ በታላቅ ደስታ ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ! በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው! ሆሣዕና በአርያም!” እያለ ሲቀበለው እንመለከታለን።
የሕዝቡ ሁኔታ፣ እልታው፣ ዝማሬው፣ ደስታው ሁሉ መጨረሻው እንደቀረበ የሚያሳይ የምጥ ጣር መጀመርያ ነው። የማይቀረው መስቀል አሁን በጌታ ፊት ተስሏል። ጌታ በዚህ መልኩ ወደ ኢየሩሳሌም እስኪገባ ድረስ መሲህ እና ንጉሥ ተብሎ እንዳይጠራ ሲከላከል የቆየ ቢሆንም አሁን ግን ይመጣል የተባለው መሲህ እና እውነተኛው የእሥራኤል ንጉሥ እርሱ መሆኑን በግልጽ ያሳያል። የሕዝቡ ሁካታ ከቁጥጥር ውጪ በመሆኑ ከተማው በሙሉ እንደተናወጠ እና የከተማው አስተዳደር በፍርሃት ውስጥ እንደወደቀ ወንጌል ይናገራል። ጌታ በበኩሉ ቤተ መቅደሱን ያነጻል፣ ጠረጴዛውን ይገለብጣል፣ የታመሙት ይድናሉ፣ መዝሙሩን ማስቆም የሚሹት በመሲሁ መልስ ኃይል የመናገር አቅማቸው ይነጠቃል። ይህ ትንብታዊ መገለጥ ነው፤ ሚልክያስ የመጨረሻውን ትንቢት ከተናገረ በኋላ ከእግዚአብሔር ዘንድ ምንም ትንቢት ያልመጣለት የእሥራኤል ሕዝብ አሁን የነብያት ሁሉ አክሊል፣ ነብያት ሁሉ የተነበዩለት መሲህ ራሱ የትንቢት ፍጻሜ ሆኖ ተገልጧል።
በዚህ ሰሙነ ሕማማት የጌታ ማንነት የበለጠ እየተገለጠ፣ መስቀሉ የበለጠ እየቀረበ ይመጣል። ኢየሱስ የመጨረሻውን ውሳኔ የሚያደርግበት፣ ከዚህ በኋላ ከኢየሩሳሌም ወጥቶ የማይሄድበት እና ወደ ኋላ የማይመለስበት ጉዞ ላይ ነው። ሕማሙን ለመታመም፣ መስቀሉን ለመቀበል እና መዳናችንን ለመፈጽም ከኢየሩሳሌም ጋር ፊት ለፊት ተገናኝቷል፤ እኛም በዚህ ሰሙነ ሕማማት ቆርጠን እንድንለይ፣ ውሳኔ እንድንወስን፣ ወደ ኋላ እናዳንመለስ እና ከጌታ ጋር የትንሳኤ ተስፋ ወዳለው ወደ ሕማሙ እና ወደ ሞቱ እንድንገባ እንጋበዛለን!
ሴሞ