“የሁላችን አጥናኝ መንፈስ ጰራቅሊጦስ የተመሰገነ ይሁን!”

M Qidusስለመንፈስ ቅዱስ ስናስብ ዘወትር በቅዳሴ ወቅት የምንለውን በማስታወስ እንጀምር፡- “በሕይወት ሰጪ ጌታ በመንፈስ ቅዱስም እናምናለን” እንላለን። ዛሬ የምናከብረው ይህንን ነው፤ ሞትን ክፋትን ሽንፈትን ፍርሃትን ጭንቀተን ሳይሆን ሕይወት ሰጪውን እናከብራለን። ሕይወት ሰጪን ማክበር ማለት ሕይወትን ማክበር ማለት ነው፤ ያም የያንዳንዳችንንና የሌሎችን ሕይወት ነው። በዚህም ምክንያት በአገራችን ሥርዓት በዓለ ጰራቅሊጦስ የትንሣኤ አቻ ነው። 

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የመጀመሪያ መጽሐፍ መጀመሪያ ምእራፍ ቁ. 2 ላይ የተገለጸውም እውነት መንፈስ ቅዱስ በፍጥረታት መጀመሪያ ላይ አድራጊ ነበር “የእግዚአብሔርም መንፈስ በውኃ ላይ ሰፍፎ ነበር። እንዲሁም በዚያው መጽሐፍ 2፡7 ላይ “እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር አፈር አበጀው፤ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት፤ ሰውም ሕያው ነፍስ ያለው ሆነ።” ይላል። እንግዲህ ሰማይና ምድርም ሲፈጠም ሆነ የሰው ልጅ ሲፈጠር አምላክም እስትንፋስም ሆኖ  ፈጣሪ እንዲሁም ሕይወት ሰጪ ነበር። በአዲስ ኪዳንም እመቤታችንን በጸጋ ሞልቶ የእግዚአብሔር ቃል የሆነው ክርስቶስን ትቀበል ዘንድ ብቁ ያደረጋት መንፈስ ቅዱስ ነው። መልአኩ ቅ. ገብርኤል “መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፥ የልዑልም ኃይል ይጸልልሻል ስለዚህ ደግሞ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል።” /ሉቃስ 1፡35/ በማለት መንፈስ ቅዱስ ዓለምን በማዳን በኩል ያለውን ሚና አጉልቶ ያሳያል።  

የመንፈስ ቅዱስ ሕይወት ሰጪነትና አዳኝነት በክርስቶስና በሐዋርያቱ ተልእኮ ውስጥ ትልቅ ሚና ነበረው፤ ስለዚህም ክርስቶስ መራራውን የሞት ጽዋ ተቀብሎ ያድነን ዘንድና ሐዋርያትም ስደትና ሞትን በድፍረት ተጋፍጠው ክርስትናን ኖረውና አስተላልፈው እንዲያልፉ ያስቻላቸው ይኸው መንፈስ ቅዱስ ነው። ከዚህም የተነሣ ክርስቶስ ሐዋርያቱን የእኔ መሄድ ለናንተ ይበጃችኋል ይላል “እኔ ግን እውነት እነግራችኋለሁ፤ እኔ እንድሄድ ይሻላችኋል። እኔ ባልሄድ አጽናኙ ወደ እናንተ አይመጣምና፤ እኔ ብሄድ ግን እርሱን እልክላችኋለሁ። /ዮሐ. 16፡7/። ይህ እውነታ ከእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ አንጻር አልተለወጠም፤ ይህ መንፈስ ቅዱስ ለዘመናት ክርስቲያኖችን ሲያጸናና ወደ እውነት ሲመራ፤ በመከራና ስቃይ መካከልም የአማኞችን ልብ ደስታና ተስፋ በመሙላት ላይ ይገኛል።

እግዚአብሔር አብ ሰውን ከአፈር ከአበጃጀው በኋላ በአፍንጫው የሕይወትን እስትንፋስ እፍ እንዳለበት ሁሉ፤ ክርስቶስም በሐዋርያት ላይ እስትንፋሱን ሰጣቸው፤ “ኢየሱስም ዳግመኛ። ሰላም ለእናንተ ይሁን፤ አብ እንደ ላከኝ እኔ ደግሞ እልካችኋለሁ አላቸው።  ይህንም ብሎ እፍ አለባቸውና። መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ። ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል፤ የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል አላቸው።” /ዮሐ. 20፡21-23/። መንፈስ፣ እስትንፋስ በሚል ባህሪይ የሚገለጸው መንፈስ ቅዱስ ድፍን የሆነና በሌላ ነገር የተሞላ ልብን ወደ ውስጥ ይገባ ዘንድ እንዲከፈትለት ይጠይቃል። ነፋስ ክፍት ነገርን ሲያገኝ ይሞላዋልና በእያንዳንዱ መስዋእተ ቅዳሴ እያንዳንዳችን ደንዳና ልብ ይዘን እንዳንመላለስ እንጋበዛለን፤ ስለዚህም ቅደሴያችንን ስንጀምር “መንፈስ ቅዱስ ከሰማይ ወርዶ ይህን መስዋእት የሚያጠላባት የሚቀድስባት ይህች ቀን ምን ያህል የምታስገርም ናት-ይህች ሰዓት ምን ያህል የምታስደንቅ ናት! የእግዚአብሔር ሰላም ከኔና ከሁላችሁም ጋር ይሆን ዘንድ በጽሞናና በፍርሃት ቆማችሁ ጸልዩ” እንላለን። በዚህ መልኩ መንፈስ ቅዱስን የምናከብረው በየቀኑ መሆኑንና የእግዚአብሔር ሰላምም የሚኖረን ለዚሁ ለከበበንና በውስጣችን ላለው መንፈስ ቅዱስ መገኘት ስንችል መሆኑን ያሳየናል። ልባችንን ከሞሉት ኮተቶች ያጸዳንና እስትንፋሱ በውስጣችን ይገባ ዘንድ እንለምነው።

አጽናኝ የሚለው የመንፈስ ቅዱስ ባህርይ ለክርስቲያኖች በሙሉ የተሰጠ ወደር የለሽ ሀብት ነው፤ ሰው ሁሌም ጎዶሎ ነውና መጽናኛ ይፈልጋል፤ አንዳንዱ በእውቀቱ፣ በውበቱ፣ በዘሩ፣ በንብረቱ…በምግብ፣ በመጠጥ…ወዘተ። ነገር ግን አሁንም “እኔባልሄድአጽናኙወደእናንተአይመጣምና፤እኔብሄድግንእርሱንእልክላችኋለሁ።” የሚለውን የወንጌሉን ቃል ወስዶ የቅዳሴ ጸሎታችን “የሁላችን አጥናኝ መንፈስ ጰራቅሊጦስ የተመሰገነ ይሁን!” ይለናል። የአንዳንዶቹ ሳይሆን የሁላችን!

ሌላው የመንፈስ ቅዱስ ተግባር አማኞችን አንድ ማድረግ ነው፤ ለዚህም ነው በቅዳሴያችን “በመንፈስ ቅዱስህ አንድ እንድንሆን አድርገን” በማለት የምንለምነው። ጠለቅ ብለን እስክናስበው ድረስ አንድ መሆን ማለት እንዲሁ ቀላል ነገር ሊመስል ይችላል፤ ሆኖም ግን እያንዳንዳችን ውስጣዊ ማንነታችን አንድ መሆኑን ስናስብ ከሌሎች ጋር በስምምነት በአንድነት መሆን ከባድ ነገር መሆኑን እንረዳለን። እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ አእምሯችንንና ልባችንን ወደ እውነትና ፍቅር የመምራት ብቃት እንዳለው አምነን ለእርሱ ካልታዘዝን በስተቀር ሃሳባችንና ስሜቶቻችንን መከተሉ አይደለም ከሌላ ጋር ከራሳችን ጋር ኅብረት እንዳይኖረን ያደርገናል። ከራሱ ጋር ኅብረት ያለው ሰው ቅ. ጳውሎስ በገላትያ 5፡22-23 የዘረዘራቸው የመንፈስ ፍሬዎች በሕይወቱ ይንጸባረቃሉ፡- ደስታ፣ ሰላም፣ ትእግሥት፣ ቸርነት፣ በጎነት፣ እምነት፣ የውሃትና ራስን መግዛት ናቸው። እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በምናሳርገው መስዋእተ ቅዳሴ በእግዚአብሔር ቃልና በምንቀበለው የክርስቶስ ሥጋና ደም ከራሳችንም ሆነ ከሌሎች ጋር ኅብረት ያለን የሰላምና የፍቅር ክርስቲያኖች ያድርገን።