የቅዱስ አባታችን የመካከለኛ ምሥራቅ አገራት ጉብኝት
- Category: ዜናዎች
- Published: Monday, 26 May 2014 06:18
- Written by Super User
- Hits: 2023
- 26 May
ቅ.አባታችን ር.ሊ.ጳ ፍራንቼስኮስ በመካከለኛ ምሥራቅ አገሮች በዮርዳኖስ በፍልስጥኤም እና በቅድስት መሬት በቤተ ልሔም እስራኤል ውስጥ ሐዋርያዊ ዑደት ለማድረግ ግንቦት 16 ቀን 2006 ዓ.ም. ጠዋት ከሮም ተጉዘዋል።
ቅዱስነታቸው ዘወትር እንደሚያደርጉት ከጉዛቸው በፊት ማምሻውን በሳንታ ማሪያ ማጆሬ ዐቢይ ደብር በመሄድ ይህንን ጉዞ ለእመቤታችን ድንግል ማርያም በማማጠን ጉዞው የተሳካና ፍሬ ያለበት እንዲሆን በእመቤታችን መንበረ ታቦት ተንበርክከው ለረጅም ጊዜ ጸሎት እንዳሳረጉ ከቅድስት መንበር የወጣ ዜና አመልክቷል።
ቅዱስነታቸው የመንበረ ጴጥሮስ ሥልጣን ከተረከቡ ወዲህ ይህ ዓለም አቀፍ ሐዋርያዊ ጉዞ ለሁለተኛ ጊዜ ሲሆን፤ አንደኛውና የመጀመርያው ባለፈው ዓመት ለዓለም አቀፍ ወጣቶች ቀን ለማክበር ወደ ብራዚል ሪዮ ዲ ጃኔሮ ያደረጉት ጉዞ መሆኑ የሚታወስ ነው።
የአሁኑ ሐዋርያዊ ጉዞ ዋና ዓላማ የእምነት ጉዞ ሆኖ የዛሬ አምሳ ዓመት በቅርብ ጊዜ ብፅዕነታቸው እንዲታወጅ የምንጠባበቀው ነፍሰኄር ር.ሊ.ጳ ጳውሎስ ስድስተኛና የቍስጥንጥንያ ፓትሪያርክ የነበሩ ብፁዕና ቅዱስ አተናጎራ በኢየሩሳሌም የተደረገው የመጀመርያው የተዋህዶና የካቶሊካ ግኑኝነት ለአብያተ ክርስትያን አንድነት መሠረት የሆነውን ግኑኝነት ለማስታወስ እና ስለአከባቢው ሰላም ለመጸለይ መሆኑም ተመልክቷል፣ ያ ከአምሳ ዓመት በፊት የተደረገው ግኑኝነት በኦርቶዶክስና በካቶሊክ መካከል የነበረውን ልዩነት ለማጥበብና ይቅርታ ለመለዋወጥ እንዲሁም በሁሉቱም አብያተ ክርስትያን መካከል የነበረውን ውግዘትን ለማንሳት ነበር።
ቅዱስነታቸው ቅዳሜ ጥዋት ከሊዮናርዶ ዳ ቪንቺ ዓለም አቀፍ የአየር ማረፍያ ሲነሱ የቤተ ክርስትያንና የኢጣልያ መንግሥት ባለሥልጣናት ሸኝዋቸዋል፣ ከሶስት ሰዓት ከአርባ አምስት ደቂቃ የበረራ ጊዜ በኋላ አማን ሲደርሱ ታላቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋል ከቤተ መንግሥት ባለስልጣናትና ከንጉሣዊ ቤተሰብ ከተገናኙና የተለያዩ ንግግሮች ከቀረቡ በኋላ በዮርዳኖስ ወንዝ አከባቢ በሚገኘው ሜዳ መሥዋዕተ ቅዳሴ አሳርገዋል፣ ማምሻውን በ2001 ዓ.ም. ልሂቅ ር.ሊ.ጳ ቤኔዲክቶስ 16ኛ መሠረት ያኖሩበት ቤተ ክርስትያንን ተሳልመው በአከባቢው የሚገኙ ከ600 በላይ የሚሆኑ ስደተኞችና በሽተኞች ጋር ተገናኝተው ወደ ሚያድሩበት ቦታ ተጉዘዋል።
ከቫቲካን ሬድዮ ድረ ገጽ የተወሰደ