የካቶሊካዊት ቤ/ያን ትምህርትና የጽንስ መከላከያ ዘዴዎች
- Category: እምነታችን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ
- Published: Sunday, 25 August 2013 08:37
- Written by Super User
- Hits: 2115
- 25 Aug
የወሊድ መቆጣጠሪያ ዘዴዎች
ባለትዳር ጥንዶች፣ ኤች.አይ.ቪ እና ኮንዶም
የቁምስናዬ አባላት የሆኑ ባለትዳር ጥንዶች ምክር ፍለጋ ወደ እኔ መጡ፡፡ ባል ኤች.አይ.ቪ ሲኖርበት ሚስት ደግሞ ከቫይረሱ ነጻ ናት፡፡ እንዲህ ባለው አስቸጋሪ አጋጣሚ ወቅት ኮንዶም እንዲጠቀሙ እመክራቸው ይሆን?
ጥርት ካለ ሳይንሳዊ አስተሳሰብ አንጻር ስንመለከተው ኮንዶም ከፍተኛ ውድቀት ያስከተለው እርግዝናን ለመከላከል ባለመቻሉ ብቻ ሳይሆን የኤች.አይ.ቪ ስርጭትን ለመቀነስ እዚህ ግባ የሚባል አስተዋጽኦ ባለማድረጉም ጭምር ነው፡፡ ከዚህም በላይ ኮንዶም በከፍተኛ መጠን ጥቅም ላይ በዋለባቸው ሀገሮች የኤች.አይ.ቪ ኤድስ ሥርጭት እጅግ ከፍተኛ ነው፡፡ በጥናት እንደተመለከተው በትዳር ጥንዶች መካከል ባሎች የኤች.አይ.ቪ ቫይረስ ተጠቂ በሆኑበት እና ሚስቶች ከቫይረሱ ነጻ በሚሆኑበት አጋጣሚ ምንም እንኳን ዘወትር ኮንዶም በአግባቡ ቢጠቀሙም ከአሥራ ስምንት ወራት በኋላ በተደረገ ምርመራ ቀድሞ ከቫይረሱ ነጻ ከሆኑት ሚስቶች መካከል 30% ያህሉ ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ እንደተገኘ ተረጋግጧል፡፡{jathumbnail off}
እንዲህ ያሉት የትዳር ጥንዶች ኮንዶምን በመጠቀም የጋብቻቸውን ግብር በሚፈጽሙበት ጊዜ የሚኖረው ሁኔታ ልክ በሚወዳት ባለቤቱ ግንባር ላይ ሽጉጥ የደቀነ ባል ሁኔታን ይመስላል፡፡ ፈጠነም ዘገየም ሽጉጡ መተኮሱ የማይቀር ሁኔታ ነው፡፡ ባል ኤች.አይ.ቪ ፖዘቲቭ ሆኖ ሚስት ከቫይረሱ ነጻ በምትሆንበት ጊዜ ሁለት ምርጫዎች ይኖራሉ፡- አንደኛው መታቀብ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በሚስት ላይ የሞት ፍርድ መፍረድ ነው፡፡ ይህ በእርግጥ ሊሻር የማይችል መራራ እውነታ ነው ነገር ግን በዚህ ዓይነት ሁኔታ ውስጥ የሚገኝ ባል ለሚስቱ ያለው ፍቅር እውነተኛ ከሆነ ለእርሷ መልካም የሆነውን ስለሚመርጥ አሳልፎ ለጉዳት አይዳርጋትም፡፡
ዓለም ከሚያስተምረው በተቃራኒው የግብረ-ሥጋ ግንኙነት ባለማድረጉ የሞተ ማምን ሰው የለም፤ ይልቁንም ‹‹ከልክ በላይ›› የግብረ ሥጋ ግንኙነት በመፈጸማቸው ብዙኀን ሞተዋል፡፡ በእርግጥ በጋብቻ አንድነት ውስጥ የሚፈጸም የግብረ-ሥጋ ግንኙነት የጸጋ ምንጭ በመሆኑ በባል እና በሚስት መካከል ልዩ ትሥሥርን ይፈጥራል፡፡ ምንም እንኳን ለዛሬው ዓለም ሰው እንግዳ ቢሆንም እውነቱን መለወጥ አንችልም ይህም የግብረ-ሥጋ ግንኙነት መፈጸም የሰው ልጅ በሕይወት ይኖር ዘንድ መሠረታዊ እና የግድ አስፈላጊ ተግባር አይደለም፡፡ በጋብቻ አንድነት ውስጥም ቢሆን እንኳን በተለይ ከባል ወይም ከሚስት አንደኛቸውን ለአደጋ አሳልፎ በሚሰጥበት ወቅት የግብረ-ሥጋ ግንኙነት የግድ አይደለም፡፡
የቆዳ በሽታን ለመከላከል
የወሊድ መቆጣጠሪያ እንክብል መጠቀም?
በአካባቢያችን በሚገኝ የጤና ተቋም ውስጥ የሚሠራ አንድ የጤና ባለሙያ አንዲት የቁምስናዬ ባልደረባ የሆነችን ሴት ለሚያሰቃያት ከባድ የቆዳ በሽታ መፍትሔ ይሆናት ዘንድ የወሊድ መቆጣጠሪያ እንክብል እንድትጠቀም አደረገ፡፡ በእርግጥ ይህ መልካም የሕክምና ተግባር ይሆን?
የወሊድ መቆጣጠሪያ እንክብሎችን ከእርግዝና እና ከወሊድ ጋር ግንኙነት ለሌላቸው ነገሮች ቢሆንም መድኃኒቱን ማዘዝ ወይም የታዘዘውን መድኃኒት መጠቀም ትክክለኛ የሕክምና ተግባራት አይደሉም፡፡ ምናልባትም አንዳንድ የጤና ባለሙያዎች ይህንን ካዘዙ በኋላ ተጠቃሚዋ እርጉዝ ከሆነች በጽንሱ ላይ ጉዳት እንዳያስከትል በሚል እንደ Accutane (አኩቴን) ያሉ መድኃኒቶችን አብረው ያዝዛሉ፤ ነገር ግን አኩቴን (Accutane) ራሱ ሕጻኑ ጤናማ ሆኖ እንዳይወለድ እክል ይፈጥራል፡፡
አንዳንድ የወሊድ መቆጣጠሪያ እንክብሎች አምራች የሆኑ ድርጅቶች ወጣት ሴቶች እነዚህን መድኃኒቶች ተጠቅመው የቆዳቸውን ጤና እና ውበት እንዲጠብቁ ይቀሰቅሳሉ፤ ነገር ግን ከትክክለኛው የሕክምና ሳይንስ አንጻር ነገሩ ሲጠና እነዚህ መድኃኒቶች መጠቀም በቆዳችን ላይ ከፍተኛ ተያያዥ ችግሮችን ያስከትላል፡፡ ከዚህ ጐን ለጐን የእነዚህ እንክብሎች ዋነኛ ተቀዳሚ ዓላማቸው የሴቷን የዘር ፍሬ ማቋረጥ ነው፡፡ እነዚህ ክኒኖች አያሌ ተያያዥ ችግሮችን ያስከትላሉ፡፡ ለምሳሌ፡- የደም መርጋት፣ የልብ በሽታ፣ የደም ሥር መጥበብ፣ የቆዳ ካንሰር ወዘተ… ተያያዥ ከሆኑት የጤና እክሎች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡
ማንኛውም የሕክምና ባለሙያ ዓላማው የቆዳ በሽታን ማስወገድ ወይም ቆዳን ማጥራት ከሆነ በቀላሉ ለዚህ ተግባር የተዘጋጁ ጥሩ መድኃኒቶችን ሊያዝዝ ይችላል፤ በቆዳ ጥናት ዘርፍ የተሰማሩት ባለሙያዎች በተደጋጋሚ በጥናታቸው እንዳመለከቱት የወሊድ መከላከያ እንክብሎችን ለቆዳ ችግሮች እንደ መፍትሔ መውሰድ ጊዜው ያለፈበት መሆኑ በመግለጽ ለዚህ ተግባር ብሎ እነዚህን እንክብሎች ማዘዝ መጥፎ የሕክምና አቋራጭ መሆኑን መስክረዋል፡፡
ባጠቃላይ የሴት ልጅን የቆዳ ውበት እና ጤንነት ለመጠበቅ የወሊድ መከላከያ እንክብል የሚሰጥ የሕክምና ባለሙያ የሴቷን የመራቢያ ዘዴ ኬሚካላዊ በሆነ መንገድ ለማበላሸት ቆርጦ የተነሣ ነው፡፡ አንዳንድ የሕክምና ባለሙያዎች ወጣት ሴቶች ይህንን መንገድ ሲከተሉ እውነቱን ለመናገር ያለባቸውን ኃላፊነት ከኅሊናቸው አውጥተው ጥለዋል፡፡
ሌላኛው ቀውስ ደግሞ ምንም እንኳን ወጣቷ ለቆዳዋ ጥራት መድኃኒቱን ለመጠቀም ብትጀምርም ውሎ አድሮ ግን ውበቷን ከመጠበቅ ባሻገር ወሲባዊ ግንኙነት ለመጀመር ትነሳሳለች፤ ምክንያቱም መድኃኒቱ ከእርግዝና ስጋት እንደሚያድናት ስለምታምን ነው፡፡ በተመሳሳይም ፍቅረኛዋ መድኃኒቱን እንደምትጠቀም ማወቁ ወደ ወሲባዊ ተግባር ለመግባትና ምኞታቸውን ለመፈጸም ብሎ በእርሷ ላይ ግፊት ማሳደር ይጀምራል፡፡ ይህንን የወሊድ መከላከያ የሚያዝዙ ሐኪሞች ልጅቷን ወደ ኃጢአት ገደል እየገፈተሯት ነው፡፡
ቤተ-ክርስቲያን በወሊድ መከላከያ መድኃኒቶች ላይ ያላት
አስተምሕሮ የማትቀይረው ለምንድነው?
ከዘመናዊው ዓለም ተግባራዊ እንቅስቃሴ ጋር አብራ ለመራመድ እንዲሁም ከማኅበረሰቡ የአመለካከት ገጽታ ጋር ለመዛመድ ስትል አብዛኞቹ ካቶሊክ ራሳቸው በአሳዛኝ ሁኔታ ተጠቃሚ መሆናቸው እየታወቀ ቤተ-ክርስቲያን በወሊድ መከላከያ መድኃኒቶች ላይ ያላትን አስተምሕሮ የማትቀይረው ለምንድነው?
ቤተ-ክርስቲያን በሌሎች ጉዳዮች ላይ ለምሳሌ፡- በሊጡርጊያ፣ ሴቶች በመንበረ ቦታት ዙሪያ ስላላቸው የአገልግሎት ድርሻ፣ በሥርዓተ ቅዳሴ ወቅት ሴቶች ፀጉራቸውን ይሸፍኑ አይሸፍኑ በሚሉት ርዕሶች ዙሪያ መሠረታዊ ለውጦች እያደረገች እስከሆነ ድረስ በወሊድ መከላከያ መድኃኒቶች ላይ አቋሟን ለመቀየር እጇን ምን ያዘው?
እዚህ ላይ መሠረታዊው ጥያቄ የቤተ-ክርስቲያን የሥልጣን ገደብ እስከምን ድረስ ነው? የሚለው ነው፡፡ በርግጥም ቤተ-ክርስቲያን በተወሰነ መልኩ ሥርዓተ አምልኳዊ መሻሻሎችን ልታደርግ ትችላለች፤ ምክንያቱም ይህንን ለማድረግ ሥልጣን ተሰጥቷታል፣ ሕጉም ቢሆን ሰብዓዊ ባህሪ ያዘለ አካል አለው፡፡ በርግጥ እዚህ ላይም ቢሆን ቤተ-ክርስቲያን ልታሻሽላቸው የማትችላቸው ነገሮች እንዳለ ሊታወቅ ይገባል፡፡
ነገር ግን የወሊድ መከላከያ እንክብሎች፣ መርፌዎችን ወዘተ… ስናነሣ መርሳት የሌለብን ቁምነገር፣ ቤተ-ክርስቲያን የተፈጥሮ ሕግ ጠባቂ እና የሕይወት አገልጋይ መሆኗን ነው፡፡ ቤተ-ክርስቲያን የሕይወት ጠባቂ እና ተንከባካቢ፣ የሰው ልጅ የሕይወት ክቡርነት ሞግዚት እና መጋቢ ናት፡፡ የተፈጥሮ ሕግ የተሰጠን ከእግዚአብሔር በመሆኑ ሊለወጥ የሚችል አይደለም፡፡ ስለዚህ ቤተ-ክርስቲያን የሕይወትን መሠረታዊ ግብረገባዊ ይዘት ለመለወጥ ሥልጣኑ የላትም፡፡
የወሊድ መከላከያ ዘዴዎችን የሚያበረታቱ ሰዎች ስልት የተለያዩ የሕዝብ አስተያየቶችን በማሰባሰብ ከ80-90% የሚሆኑት ምዕራባውያን ካቶሊኮች የዚህ ተጠቃሚ መሆናቸውን የሚያስረዱ የጥናት ውጤቶችን ይፋ ማድረግ ወይም ደግሞ አንዳንድ ካህናት እና የሥነ-መለኮት ሊቃውንት ጉዳዩን ችላ ብለው የማለፋቸውን ሁኔታ በመዘርዘር ቤተ-ክርስቲያን ላይ ተፅዕኖ መፍጠር ይፈልጋሉ፡፡ ባለትዳር ጥንዶች ሰው ሠራሽ የወሊድ መከላከያ ሲጠቀሙ እግዚአብሔር በእነርሱ በኩል ለሚያከናውነው ፍጥረትን የመቀጠልን ሥራ ያቋርጡታል፤ ይህም የእግዚአብሔርን ፈጣሪ እጅ ወደ ኋላ ማሠር ነው፡፡ ከዚህ ክፉ ልማድ በመነሣት ጉዳዩን እንደ ጤናማ ምርጫ ማዘውተር የተለመደ ሆኗል፡፡
በሚያሳዝን ሁኔታ አብዛኞቹ ምዕራባውያን ጥንዶች በእውነትም በዚህ ድንቁርና ተከበዋል፡፡ ነገር ግን የእምነት ነገሮች እና ግብረ-ገባዊና መለኮታዊ እውነታዎች በድምፅ ብልጫ አይወሰኑም፡፡ ግብረ-ገባዊና መለኮታዊ ነገሮችን በሚመለከት የጋራ ስምምነት ብሎ ነገር የለም፡፡ ስለዚህ የትዳር ጥንዶች ሰው ሠራሹን የወሊድ መከላከያ ሲጠቀሙ በቀጥታ እግዚአብሔር በጀመረው የፍጥረት ሥራ ጣልቃ ይገባሉ፡፡
ከዚህ ሁሉ በላይ ካቶሊካውያን ሌላ ጠለቅ ያለ መመሪያ አላቸው፡፡ ይህም የርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ትምህርት ነው፡፡ አንዳንድ ካህናት እና ምዕመናን በግብታዊነት የሚሰጡት አስተያየት እዚህ ግባ የማይባል ነው፡፡ ቁጥሩ ምንም ያህል አነስተኛ ቢሆንም እንኳን የመልካም ካቶሊካውያን ኅሊና የግድ እግዚአብሔርን እና ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳትን ይከተላል፡፡
ከወጣት መ/ር ሳምሶን ደቦጭ - ቅ. ዮሴፍ ቁምስና አ.አ.