“ካህን ለቤተ ክርስትያን እና ለዓለም ጸጋ ነው”
- Category: ዜናዎች
- Published: Tuesday, 15 June 2010 12:05
- Written by Super User
- Hits: 2851
- 15 Jun
ራድዮ ቫቲካን - እሑድ እኩለ ቀን ላይ ቅዱስ አባታችን ር.ሊ.ጳ. ቤኔዲክቶስ 16ኛ የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎትን ሲያሳርጉ ባሰሙት ስብከት፣ የእንተ ላእለ ኵሉ (ካቶሊካዊት) ቤተ ክርስያን ካህናት በሰው ልጅ ታሪክ ለመንፈሳዊ እና ማኅበራዊ ኅዳሴ መረጋገጥ የደረሷቸው መጻሕፍት፣ የሰጡት አብነት እና አስተዋጽኦ የማይካድ ብቻ ሳይሆን የሚደነቅ መሆኑን አመልክተዋል።
በመቀጠልም ለአንድ ዓመት በኵላዊት ቤተ ክርስትያን የተከበረውንና ባለፈው ሳምንት የተጠናቀቀውን የክህነት ዓመት መዝጊያ ምክንያት በማድረግ ከመላ ዓለም የተወጣጡ ከ15 ሺሕ በላይ የሚገመቱ ካህናት የተሳተፉበት በሮማ የተካሄደው ዓቢይ በዓል ፈጽሞ የማይረሳ የዘወትር ትውስታ እንደሚሆን ገልጠው፣ በዚህ የክህነት ዓመት ምክንያት እግዚአብሔር ለኵላዊት ቤተ ክርስትያን ለሰጠው ጸጋዎች ምስጋናን በማቅረብ፣ የታደሉት ጸጋዎች ማንም ሊለካው የማይቻል ቢሆንም ፍሬው በግልጽ የታየና ገና ተትረፍርፎ የሚታይ ነው ብለዋል።
ካህን የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልብ ለቤተ ክርስትያን እና ለዓለም የሰጠው እና የሚሰጠው ጸጋ መሆኑም አስረድተው፣ ካህናትን የፍቅር ሥልጣኔ የመጀመሪያ አገልጋዮች በማለትም ገልጠዋቸዋል። ቅዱስ ዮሓንስ ማሪያ ቪያነይ እና ባለፈው ሳምንት ቅድስት ቤተ ክርስትያን በቫርሳቪያ ብፅእና ያወጀችለት የደም ሰማዕት የፖላንድ ተወላጅ ካህን ኣባ ጀርዝይ ፖፒየሉስዝኮን በመጥቀስ ለክህነት ሕይወት አብነት ናቸው ካሉ በኋላ፣ ቅዱስ አባታችን መላው ውሉደ ክህነትን ለቅድስት ድንግል ማርያም ጥበቃ በማማጸን፣ ባለፉት ጥቂት ቀናት ቅድስት ቤተ ክርስትያን ብፅእና ያወጀችላቸውን በማሰብ፣ በተለይም ደግሞ ዓለማዊ ምእመን ጋዜጠኛ ማኑኤል ሎዛኖ ጋሪዶ፣ ሕመም እና ስቃይ ሳይበግረው፣ ሥራውን እና ክርስትያናዊ ኃላፊነቱን በመወጣት የመሰከረው እምነት በቅድሱ ቁርባን ላይ የነበረው ፍቅር የሕይወቱ ማእከል በማድረግ የኖረው ለሁሉም ጋዜጠኞች አብነት ነው ብለው፣ በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰው በብዙ ሺሕ ለሚገመተው ምእመን ቡራኬ በመስጠት መልካም እሁድን ተመኝተው የዕለቱን አስተምህሮ አጠቃለዋል።