ሦስት ሺህ ሰዎችን በማዳናቸው ሚሲዮናዊው ተመሰገኑ
- Category: ዜናዎች
- Published: Monday, 27 July 2009 06:57
- Written by Super User
- Hits: 2018
- 27 Jul
(Independent Catholic News) - እ.ኤ.አ. በ1994 ዓ.ም. በሩዋንዳ 800,000 ሰዎችን ሰለባ ባደረገው የጅምላ ጭፍጨፋ ወቅት ሌሎችን ከሞት ለመታደግ ላደረጉት ትልቅ አስተዋፅኦ ባለፈው ሳምንት ታላቅ አክብሮት ከተቸራቸው አሥር ሰዎች መካከል አንድ ጣልያናዊ ሚሲዮናዊ አንዱ መሆናቸው ታውቋል።
በአሁኑም ሰዓት እዚያው ሩዋንዳ ውስጥ በማገልገል ላይ የሚገኙት አባ ማሪዮ ፋልኮኒ የቱትሲ ጎሣ አባላትን በምሥራቅ ሩዋንዳ ሙሁራ ውስጥ በሚገኘው የቁምስና ቤተ ክርስቲያናቸው ውስጥ በማስጠጋትና በመደበቅ በወቅቱ ከ3,000 በላይ የሆኑ ሰዎች ሕይወት መታደጋቸውን የሩዋንዳ ሬድዮ ዘግቧል።
ኢቡካ በሚባለው ከዘር ማጥፋቱ የተረፉ ሰዎች ባቋቋሙት ድርጅት አዘጋጅነት በተካሄደው የሽልማት ሥነ ሥርዓት ላይ አባ ማሪዮ የተሸለሙ ሲሆን በጅምላ ጭፍጨፋው ወቅት ወደ ጣልያን መመለስን ያልፈለጉበት ምክንያት የሚያገለግሏቸውን ሕዝቦች ጥለው መሄል ባለመፈለጋቸው መሆኑን ገልጸዋል።
በሽልማቱ ሥነ ሥርዓት ላይ አባ ማሪዮ ሲናገሩ "ዛሬ እኔን እንደ አንድ ጀግና አከበራችሁኝ ነገር ግን እኔ የማውቀው አንድ ማንኛውም ክርስቲያን ሊያደርግ ይገባ የነበረውን ነገር ማድረጌን ነው። ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያኑን እንደሚታደግ ሁሉ እኔም እነርሱን ከገዳዮች አዳንኩ፤ በመጨረሻም ገዳዮቹ ወደኛ በተቃረቡ ወቅት እኛን ሊከላከሉን ስለደረሱልን የሩዋንዳ አርበኞች ግንባርን አመሰግናለሁ" ብለዋል።