እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

የመጽሐፍ ፡ ቅዱስ ፡ የንባብ ፡ ቁልፎች

የመጽሐፍ ፡ ቅዱስ ፡ የንባብ ፡ ቁልፎች

ከዚህም ፡ በፊት ፡ በዚሁ ፡ ጋዜጣ ፡ ላይ ፡ ለመግለጽ ፡ እንደሞከርነው ፡ አንድን ፡ የወንጌል ፡ ክፍል ፡ በምናነብበት ፡ ጊዜ ፡ በመጀመርያ ፡ እይታ ፡ ወይም ፡ በምናደርገው ፡ የአንድ ፡ ዙር ፡ ተራ ፡ ንባብ ፡ ምሥጢሩን ፡ ወይም ፡ ማስተላለፍ ፡ የፈለገውን ፡ ትክክለኛውን ፡ መልእክቱን ፡ በሚገባ ፡ ለመረዳት ፡ ሊያዳግተን ፡ ስለሚችል ፡ የወንጌሉን ፡ መልእክት ፡ በሚገባ ፡ ለመረዳት ፡ ማስተዋልና ፡ ማድረግ ፡ ከሚያስፈልጉን ፡ ነገሮች ፡ ውስጥ ፡ ጥቂቶቹን ፡ በድጋሚ ፡ እናስታውስ ፡፡

  1. የወንጌሉን ፡ ክፍል (ዮሐ 6 ፡ 1-15) በማስተዋል ፡ ደጋግሞ ፡ በሚገባ ፡ ማንበብ ፡፡ ወንጌሉን ፡ በምናነብበት ፡ ጊዜ ፡ ስለምን ፡ እንደሚያወራና ፡ ትኩረቱ ፡ ምን ፡ ላይ ፡ እንደሆነ ፡ በጥንቃቄ ፡ መከታተል ፡፡ በተጨማሪም ፡ ወንጌሉን ፡ የሚያወራው ፡ ስለ ፡ አንድ ፡ አርእስት ፡ ብቻ ፡ ነው ፡ ወይስ ፡ ሌሎችም ፡ አሉ ፤ ካሉስ ፡ ከአንዱ ፡ አርእስት ፡ ወደ ፡ ሌላው ፡ እንዴት ፡ ነው ፡ የሚሸጋገረው ፤ እንዲሸጋገርስ ፡ ምክንያት ፡ የሆነው ፡ ምንድን ፡ ነው ፤ ለምሳሌ ፡ ስለ ፡ ፍቅር ፡ እያስተማረ ፡ እያለ ፡ እዛው ፡ ላይ ፡ ስለ ፡ እንጀራና ፡ ዓሣ ፡ ማውራት ፡ ይጀምራል ፡፡ በዚህ ፡ ጊዜ ፡ ታድያ ፡ የንግግሩን ፡ አርእስት ፡ እንዲቀይር ፡ ምክንያት ፡ የሆነው ፡ የሕዝቡ ፡ ረሃብ ፡ ወይም ፡ ጥማት ፡ ሊሆን ፡ ይችላል ፡፡ ስለዚህ ፡ ይህንን ፡ በማስተዋል ፡ ማየት ፡፡
  2. ወንጌሉን ፡ በምናነብበት ፡ ጊዜ ፡ ታሪኩ ፡ ውስጥ ፡ የሚንጸባረቁት ፡ ዋና ፡ ዋና ፡ ገጸ ፡ ባሕርያት ፡ በማስተዋል ፡ መመልከት ፡ ወይም ፡ በደንብ ፡ ለይቶ ፡ ማወቅ ፡፡ ይህም ፡ ታሪኩ ፡ በማን ፡ ዙርያና ፡ ትኩረቱ ፡ ማንን ፡ ወይም ፡ ምን ፡ ላይ ፡ እንዳደረገ ፡ የበለጠ ፡ ለመረዳት ፡ ይጠቅማል ፡፡ ለምሳሌ ፡ በዮሐ 6 ፡ 1-15 ጌ. ኢ. ክ ፣ ሕዝቡና ፡ ሐዋርያቶች የድርጊቱ ፡ ዋና ፡ ዋና ፡ ገጸ ፡ ባሕርያቶች ፡ ሆነው ፡ ይገኛሉ ፡፡
  3. ታሪኩ ፡ ምን ፡ ጊዜና ፡ የት ፡ ቦታ ፡ ላይ ፡ እየተከናወነ ፡ መሆኑን ፡ በደንብ ፡ በማስተዋል ፡ መመልከት ፡፡ ድርጊቱ ፡ እየተከናወነ ፡ ያለው ፡ ጸሎት ፡ ቤት ፡ ውስጥ ፡ ነው ፣ ባሕር ፡ አጠገብ ፡ ነው ፣ ገለልተኛ ፡ ቦታ ፡ ላይ ፡ ነው ፣ ተራራ ፡ ላይ ፡ ነው ፣ ኢየሩሳሌም ፡ ውስጥ ፡ ነው ፡ ወይስ ፡ ገሊላ ፡ አውራጃ ፣ ወይስ ፡ ጌ.ኢ.ክ ፡ ከገሊላ ፡ ወደ ፡ ኢየሩሳሌም ፡ ያደርገው ፡ በነበረው ፡ ጉዞ ፡ ላይ ፡ ነው ፡፡ ያንን ፡ ቦታ ፡ ላይ ፡ ከዚህ ፡ በፊት ፡ ለምሳሌ ፡ በብሉይ ፡ ኪዳን ፡ ውስጥ ፡ አንድ ፡ ድርጊት ፡ የተከናወነበት ፡ ወይም ፡ ትንቢት ፡ የተነገረለት ፡ ወይም ፡ ከሕዝቡ ፡ ማህበራዊና ፡ ታሪካዊ ፡ አኗኗር ፡ ጋር ፡ በተያያዘ ፡ መልኩ ፡ የራሱ ፡ የሆነ ፡ ሌላ ፡ መልእክት ፡ ሊያስተላልፍ ፡ ስለሚችል ፡ በደንብ ፡ መታየት ፡ አለበት ፡፡ ጊዜውስ ፡ ጠዋት ፣ ቀትር ፣ ማታ ፣ ክረምት ፣ በጋ ወይስ ፡ በፋሲካ ፡ ወቅት ፡፡
  4. እነዚህን ፡ ነገሮች ፡ ግንዛቤ ፡ ውስጥ ፡ በማስገባት ፡ ካነበብነው ፡ ወይም ፡ ካጠናነው ፡ በኃላ ፡ ከታሪኩ ፡ በፊትና ፡ በሁዋላ ፡ ያለውን ፡ የንባብ ፡ ክፍል ፡ በማንበብ ፡ ከታሪኩ ፡ ጋር ፡ የተያያዙ ፡ ወይም ፡ ምንም ፡ ግኑኝነት ፡ የሌላቸው ፡ መሆኑን ፡ በደንብ ፡ መረዳት ፡፡ ለምሳሌ ፡ በምናጠናው ፡ የወንጌል ፡ ክፍል (ዮሐ 6 ፡ 1-15) ከሆነ ፡ ዮሐ 5 የመጨረሻው ፡ ከፍል ፡ ምን ፡ ላይ ፡ እንደሚያተኩርና ፡ ከዮሐ 6 ፡ 15 ጀምሮ ፡ ያለው ፡ ስለምን ፡ እንደሚያወራ ፡ በማስተዋል ፡ መመርመርና ፡ የሚገናኙበት ፡ ነጥብ ፡ ካለ ፡ አስተውሎ ፡ በማየት ፡ የበለጠ ፡ ለመረዳት ፡ መሞከር ፡ የራሱ ፡ የሆነ ፡ ጠቀሜታ ፡ አለው ፡፡
  5. የምናነበው ፡ የወንጌል ፡ ክፍል ፡ በሌሎች ፡ ወንጌላውያን ፡ በድጋሚ ፡ ተጽፎ ፡ ከሆነ ፡ እነሱ ፡ ከጻፉት ፡ ታሪክ ፡ ጋር ፡ በምን ፡ እንደሚመሳሰልና ፡ ልዩነቱስ ፡ ምኑ ፡ ላይ ፡ እንደሆነ ፡ ለይቶ ፡ መረዳት ፡ ያስፈልጋል ፡፡ ለምሳሌ ፡ ዮሐ 6 ፡ 1-15 በማትዮስ ፣ በማርቆስና ፡ በሉቃስ ወንጌሎች ፡ ውስጥ ፡ ተጽፎ ፡ ስለሚገኝ ፡ አራቱም ፡ እያመሳከርን ፡ የእያንዳንዳቸው ፡ ትኩረት ፡ ምን ፡ ላይ ፡ እንደሆነና ፡ ለምንስ ፡ ትኩረታቸው ፡ እዚያ ፡ ነገር ፡ ላይ ፡ ማረግ ፡ እንደፈለጉ ፡ ለመረዳት ፡ መሞከር ፡፡ በዚህ ፡ ታሪክ ፡ ውስጥ ፡ ቅዱስ ፡ ዮሐንስ ፡ የሐዋርያቶች ፡ ሥም ፡ እየጠቀሰ ፡ ከኢየሱስ ፡ ሲወያዩ ፣ ወቅቱም ፡ የፋሲካ ፡ ጊዜ ፡ እንደነበር ፣ አምስት ፡ እንጀራና ፡ ሁለት ፡ ዓሣ ፡ የያዘ ፡ ልጅ ፡ እንደተገኘ ፣ ኢየሱስ ፡ እራሱ ፡ እንጀራውና ፡ ዓሣዎቹ ፡ እንዳከፋፈለና ፡ በመጨረሻም ፡ ሕዝቡ ፡ ኢየሱስን ፡ ሊያነግሡት ፡ እንደፈለጉ ፡ ትኩረት ፡ ሰጥቶ ፡ ይተነትነዋል ፡፡ ሌሎቹ ፡ ወንጌላውያን ፡ ግን ፡ ይህንን ፡ ዝርዝር ፡ ሁሉ ፡ አይጠቅሱትም ፡፡ ታድያ ፡ ቅ. ዮሐንስ ፡ ይህንን ፡ ሁሉ ፡ መዘርዘሩ ፡ ለምን ፡ አስፈለገው ፡፡
  6. በተጨማሪም ፡ ይህንን ፡ የወንጌል ፡ ክፍል ፡ ቀድሞውኑ ፡ በብሉይ ፡ ኪዳን ፡ ውስጥ ፡ በተለያየ ፡ መልኩ ፡ ተገልጾ ፡ ከሆነ ፡ ከዚህ ፡ በፊት ፡ የሰማናቸውን ፡ የብሉይ ፡ ኪዳን ፡ ታሪኮች ፡ በድጋሚ ፡ ማሰብና ፡ ማገናዘብ ፡ ያስፈልጋል ፡፡ ይህም ፡ ማለት ፡ ቀድሞ ፡ በብሉይ ፡ ኪዳን ፡ ውስጥ ፡ ስለዚያ ፡ ታሪክ ፡ ተነግሮ ፡ ወይም ፡ ተተንብዮ ፡ ከሆነ ፡ ከዚህኛው ፡ ታሪክ ፡ ጋር ፡ ምን ፡ ግኑኝነት ፡ ሊኖረው ፡ እንደሚችል ፡  ማስተዋል ፡፡ ለምሳሌ ፡ ዮሐ 6 ፡ 1-15 በምናይበት ፡ ጊዜ ፡ የፋሲካ ፡ በዓል ፡ በደረሰ ፡ ጊዜ ፡ ኢየሱስ ፡ ወደ ፡ ተራራ ፡ ወጣ ፤ ከዚያም ፡ ሕዝቡ ፡ ያልነበራቸውን ፡ እንጀራና ፡ ዓሣ ፡ እንዲመገቡ ፡ አደረጋቸው ፡ ሲል ፡ በብሉይ ፡ ኪዳን ፡ ውስጥ ፡ ሙሴ ፡ ከፋሲካ ፡ በዓል ፡ በፊት ፡ ወደ ፡ ተራራ ፡ መውጣቱንና ፡ በምድረ ፡ በዳ ፡ ከእግዚአብሔር ፡ ዘንድ ፡ መና ፡ እንዲወርድላቸው ፡ ማድረጉን ፡ የሚገልጸውን ፡ ታሪክ ፡ ለማገናዘብ ፡ መሞከር (ዘጸ 16 ፡ 4) ፡፡ ወይም ፡ ነብዩ ፡ ኤልሳ ፡ በሃያ ፡ የገብስ ፡ ሙልሙልና ፡ በጥቂት ፡ የእ ሸት ፡ ዛላዎች ፡ ብዙዎችን ፡ ከመገበ ፡ በሁዋላ ፡ ብዙ ፡ የተረፈ ፡ ምግብ ፡ መሰብሰቡን ፡ የሚተርከው ፡ የመጽሐፍ ፡ ቅዱስ ፡ ክፍል ፡ ጋር ፡ በማዛመድ ፡ ለመረዳት ፡ መሞከር (2 ነገ 4 ፡ 42-44) ፡፡
በመጨረሻም ፡ ይህንን ፡ ወንጌል ፡ በጊዜው ፡ የተጻፈለት ፡ የክርስቲያን ፡ ማኃበረሰብ ፡ በወቅቱ ፡ ይገኝበት ፡ የነበረውን ፡ ማኃበራዊ ፣ ሃይማኖታዊና ፡ ፖለቲካዊ ፡ የአኗኗር ፡ ዘይቤዎች ፡ የሚገልጹ ፡ ጽሑፎች ፡ አንብበን ፡ ከሆነ ፡ ወይም ፡ ከዚህ ፡ ጋር ፡ በተያያዘ ፡ መልኩ ፡ ፊልሞችን ፡ ተመልክተን ፡ ከሆነ ፡ ግንዛቤ ፡ ውስጥ ፡ ማስገባቱ ፡ እጅግ ፡ በጣም ፡ ጠቃሚ ፡ ነው ፡፡ ለምሳሌ ፡ የበርባንን ፡ ታሪክ ፡ ወስደን ፡ በአጭሩ ፡ ለማየት ፡ እንሞክር ፡፡

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት