እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

ዘፍሬ

ዘፍሬ - ምድርኒ ወሀበት ፍሬሃ፤ ወይባርከነ እግዚአብሔር አምላክነ፤ ወይባርከነ እግዚአብሔር። ምድር ፍሬዋን ሰጠች፤ እግዚአብሔር አምላካችንም ይባርከናል፤ እግዚአብሔር ይባርከናል። መዝ. 66:6-7 - ንባባት፡- 2ቆሮ.9:1-15,  ያዕ.5:1-9, ሐዋ. ሥራ 19:21-40, ማር. 4:24-3

ሕይወታችን የሁለት ገበሬዎች የእርሻ ማሳ ናት።
 
Meskel-Flowersበአዲስ ዓመት መጀመሪያ አካባቢ ላይ እንደመገኘታችን መጠን ይህንን ሁለተኛ ሰንበት ቤተ ክርስቲያን <<ዘፍሬ>> ብላ ሠይማዋለች። በርግጥ ፍሬ መጨረሻ ላይ የሚታፈስ፣ የሚለቀምና የሚሰበሰብ ሲሆን መጀመሪያ ላይ ስለፍሬ ማውራቱ ምን ትርጉም ሊኖረው ይችላል? ብለን ካሰብን ለዚህ መልስ እንዲሆነንና ለአስተንትኗችን እንዲያግዘን በዕለቱ ወንጌል ውስጥ የተካተቱ ክርስቶስ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት የተናገራቸውን ሁለት ምሳሌዎች እንይ።
የመጀመሪያው ምሳሌ ምዕ.4:26-29 ሲሆን የሚዘራ ገበሬ ከዘራ በኋላ <<ሌሊትና ቀን ይተኛልም ይነሣልም፥ እርሱም እንዴት እንደሚሆን ሳያውቅ ዘሩ ይበቅላል ያድግማል። ምድሪቱም አውቃ በመጀመሪያ ቡቃያ ኋላም ዛላ ኋላም በዛላው ፍጹም ሰብል ታፈራለች። ፍሬ ግን ሲበስል መከር ደርሶአልና ወዲያው ማጭድ ይልካል።>> ይለናል። ይህን ከክርስቲያናዊ ሕይወታችን አቅጣጫ ካየነው ክርስትና በሁለት ጽንፎች መካከል የሚገኝ መሆኑን ያሳየናል። ማድረግ የሚገባንን ማድረግና እግዚአብሔር ብቻ ሊሠራው በሚችለው ነገር ደግሞ ያለመጨነቅ ወይም ለርሱ መተው።
ገበሬው ሳይዘራ እንደማያጭድ ሁሉ በመመኘት ብቻ ፍሬ አይሰበሰብም፤ በተቃራኒውም ደግሞ በመጣጣርና ሁሉን እኔ አደርገዋለሁ በማለት ፍሬን ማሳደግና ማብቀል አንችልም - ምክንያቱም ገበሬው ከዘራ በኋላ ማለትም ለዘሩ ማድረግ የሚገባውን ካደረገ በኋላ ይተኛል ይነሣል እርሱም እንዴት እንደሚሆን ሳያውቅ ዘሩ ይበቅላል ያድግማል ይላል ወንጌል። በሌላ አባባል በእምነታችን የእግዚአብሔርን መንግሥት እንደተቆጣጠርን ሆነን መመጻደቅ አንችልም ምክንያቱም ባለቤቱ ራሱ እግዚአብሔር ነውና፤ እንዲሁም እሱ የማድረግንና የመኖርን ኀላፊነት ሰጥቶናልና ክርስትናችንን በእምነትና በተግባር መካከል ሚዛን ጠብቀን መኖር አለብን። በልቤ አምናለሁ በቃ! ወይም መልካም ነገር አደርጋለሁ፣ ለሰው ክፉ አልሆንም ሌላ እምነት፣ ሃይማኖት…አያስፈልገኝም ማለት አንችልም። ሕይወታችን እኛና እግዚአብሔር ተጋግዘን የምንሠራባት የሁለት ገበሬዎች የእርሻ ማሳ ናት።
ሁለተኛው ምሳሌ በምዕ.4:30-32 ውስጥ ሲሆን የእግዚአብሔር መንግሥት በጣም ደቃቃ በሆነችው በሰናፍጭ ዘር ተመስላ ኋላም ይህች ሚጢጢ መስላ የምትታየው ነገር በጊዜዋ ትልቅ ዛፍ ሆና ለሌሎች ማረፊያና ከለላ እንደምትሆን ያስረዳናል። በትንሹ ታማኝ የሆነ በትልቁ ታምኝ ይሆናል እንደሚለው ሉቃ. 16:10 ክርስትና በትንሽ ነገር ነው የሚጀመረው።
በመጀመሪያው ምሳሌ ውስጥ እምነትን ስለመኖር አይተናል፤ ያ ማለት ግን ትላልቅ ጀብዱዎችን ወይም ተአምራትን መፈጸም ማለት አይደለም ይልቁንም የተናቁ የሚመስሉ ነገሮችን በየዕለታዊ ሕይወታችን መለማመዱ ነው ቁም ነገሩ። ይህ በየቀኑ ስለክርስትናችን ማለትም ስለክርስቶስ ብለን የምናደርገው ነገር ከክርስቶስ ጋር እያተሳሰረን ይሄዳል። በተቃራኒውም ክፉ ነገሮችን ብናይ ተመሳሳይ አካሄድ ነው ያላቸው። ማንም ሰው በአንድ ቀን የሱስ ባሪያ አይሆንም። ትንሽ በትንሽ በየጊዜው ያደርገዋል መጨረሻ ላይ መውጣት እስከማይችል ድረስ በሱስ ይጠመዳል።
ስለዚህ በውስጣችን እያደገ ያለውን ዘር ማየትና የኛንም ትብብር ማስተዋል አለብን። የጊዜ ሂደት በራሱ ወደ አንድ ፍጻሜ ያደርሰናል፤ ያ ፍጻሜያችን ግን የዛሬ አናኗራችን ድምር ነውና የተራ ነገሮች ባሪያ ከሚያደርጉን ነገሮች ርቀን የእግዚአብሔር ባሪያ ሊያደርጉን የሚችሉት ትናንሽ ተግባሮችን ለማድረግ በእምነት እንጣር።

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት