እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

ዘዮሐንስ (አዲስ ዓመት)

ቅዱስ ዮሐንስ (አዲስ ዓመት)

 2ቆሮ. 6:1-10 -- ያዕ. 5:8-10 -- የሐዋ. ሥራ 5:12-16 -- ማቴ. 11:1-19 

የታጨቁ የእግዚአብሔር ስጦታዎች

flower-field-summer1ጊዜያትና የዘመናት ጌታ አምላካችን ክረምት ብለን በጋ እንድንልና የወቅቶችን ዑደት አይተን እንድናመሰግነው ስላደረገን የተመሰገነ ይሁን! የምናመሰግንበት ዋነኛ ምክንያት ራሳችን እንዲመቸን ያደረግናቸው የቀናት ቁጥሮች ስለተቀያየሩ ሳይሆን ዛሬ ላይ ቆመን ቸርነቱን አስበን ይበልጥ ወደርሱ መቅረብን እንድንወስን የሚያግዝ ወቅት ላይ ስላደረሰን ነው።

ዳዊት <<ነፍሴ ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኪ፥ አጥንቶቼም ሁሉ፥ የተቀደሰ ስሙን። ነፍሴ ሆይ፥ እግዚአብሔርን ባርኪ፥ ምስጋናውንም ሁሉ አትርሺ፤ ኃጢአትሽን ሁሉ ይቅር የሚል፥ ደዌሽንም ሁሉ የሚፈውስ፥ ሕይወትሽን ከጥፋት የሚያድናት፥ በምሕረቱና በቸርነቱ የሚከልልሽ፥ ምኞትሽን ከበረከቱ የሚያጠግባት፥ ጕልማስነትሽን እንደ ንስር ያድሳል…እንደ ኃጢአታችን አላደረገብንም፥ እንደ በደላችንም አልከፈለንም።>> (መዝ.103) በማለት አምላኩን ላለማመስገን ሰብብ እንዳጣ ይገልጽልናል። ምናልባት አዲስ ዓመት ብለን እግዚአብሔርን ለማመስገን ስናስብ ያለፈውን ዓመት በሙሉ በዓይነ ኅሊናችን ለመቃኘት እንሞክርና ብዙም አዲስ ነገር የለም፤ የተወሰነ ነገር ነው…እንደውም ብለን ደግሞ ጥሩ አልሆኑልንም ብለን የምናስባቸውን ነገርም እንደረድርና <<መጥፎ>> ነገሮቻችን ሚዛን የደፉ ይመስለን ይሆናል። ግን በአንድ ዓመት ሳይሆን በአንድ ቀን ውስጥ የታጨቁትን የእግዚአብሔር ስጦታዎች ለማየትና ለመቁጠር ልቦናችን ቢፈቅድና ብንወስን ለማመስገኑ ባተሌዎች አንሆንም።

በመሠረቱ ጊዜ ሲለዋወጥ የተለመደ ሁኔታ ስለሚመስለን አዲስ ነገርም የመጠበቅ ጉጉታችን ይዳከማል። ከሰኞ በኋላ ማክሰኞ እንደሚመጣ ስለምናውቅ እንደ አንድ አዲስ የጊዜ ስጦታ አንቆጥረውም። አሁንም አዲስ ዓመት ሲባል በፊታችን አንድ ዓመት ተሰጠን ማለት አይደለም፤ ሊሆንም ላይሆንም ይችላል። ርግጠኛ መሆን የምንችለው አሁን ያለንባት ሰዓት ላይ መሆናችንን ነው። እውነቱ ያ ከሆነ ደግሞ ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ ያለን ጊዜ አሁን ነው ማለት ነው።

ቶማስ ሜርተን (ሲታዊ) ይህን እውነት በአንድ መጽሐፉ ሲገልጸው ከሰው በስተቀር ሌሎች ፍጥረታት ሁሉ <<ጊዜ>> የሚባል ግንዛቤ (ሰዓት ወይም ካላንደር) ስለሌላቸው እያንዳንዷ ቀን ለነሡ ዳግም የመፈጠር ያህል ነው። ስለዚህም በማለዳ ጎሕ ሳይቀድ ከእንቅልፍ ሲነቁ ካለመኖር ወደ መኖር መጥተዋልና ፈጣሪያቸውን ያመሰግናሉ። ሰው ግን ገና ማታ ሲተኛ ነገ የሚያደርገውን ነገር ስለሚያውቅ ጠዋት ሲነሣ የጠበቀውን ጊዜ የሚቀጥል እንጂ አዲስ ጊዜ እንደተሰጠው ብዙም አያስተውልም ስለዚህም ከማመስገን ወደ ኋላ ይላል በማለት የእግዚአብሔርን ስጦታ በዘልማድ እንደምንወስዳቸው ያስረዳል። ይህ ሀሳብ ከተረዳን አሁንም መዝ.148 ላይ ዘማሪው ከመላእክት ጀምሮ ፀሐይ፣ ከዋክብት፣ ጨረቃ፣ ብርሃናት፣ ሰማየ ሰማያት፣ የሰማያት በላይም፣ ተራራና ኮረብታ፣ አመዳይና ውርጭ፣ እሳትና በረድ…አራዊትና ወፎች፣ የምድር ነገሥታት አሕዛብም ሁሉ፥ አለቆች የምድርም ፈራጆች ሁሉ፥ ጕልማሶችና ቈነጃጅቶች፥ ሽማግሌዎችና ልጆች፤ <<እርሱ ብሎአልና፥ ሆኑም፤ እርሱም አዝዞአልና፥ ተፈጠሩም፤ የእግዚአብሔርን ስም ያመስግኑት>> በማለት እያንዳንዷ ቀን በእግዚአብሔር ፈቃድ እንደምትሰጠንና ለዚያም ውለታ ቢሶች መሆን እንደሌለብን ዘምሯል።

እግዚአብሔር ጊዜን የሰጠኝ ለምንድነው ብለን እያንዳንዳችን እናስብ። በአዲስ ዓመት በዓላችን የምናከብረው ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቁ ለርሱ ጊዜ የተሰጠው ስለእውነት ለመመስከርና ለመሞት ነበር። ይህን ታላቅ ቅዱስ በዓመቱ መጀመሪያ ላይ ስናከብረው ጥልቅ ትርጉም ይሰጠናል፤ የተሰጠን ጊዜ ለትልቅ ዓላማ መሆኑን ከርሱ መማር መቻል አለብን። ይህ ሊሆን የሚችለው በእግዚአብሔር ትምክህታችን ሲበዛ ነው። በእግዚአብሔር የሚመካ ሰው እሱን ያመሰግናል። ወደ ውስጣችን ከገባን እግዚአብሔርን እንዳናመሰግንና ለርሱ እንዳንቆም የሚያግደን ነገር ውጫዊ ነገሮች ስለጎደሉን አይደለም፤ ይልቁንስ መንፈሳዊ ሕይወታችን በሆነ ነገር ስለታነቀ ነው። ውስጣችንን የያዙትን ነገሮች በንስሐ ለማስወገድ እግዚአብሔር ዳግም ጊዜን ሰጥቶናልና የተመሰገነ ይሁን።

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት