እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

ዘስብከት 1ኛ

ሰው እግዚአብሔርን ሲንቅ እግዚአብሔር ሰውን ሲያከብር! - ዘስብከት 1ኛ - 1ዮሐ.:1-14/ዕብ.1:1-14/2ጴጥ.3:1-9/ሐዋ.3:17-26/ዮሐንስ 1፡ 43-51

Advent 1በሥርዓተ አምልኳችን አካሄድ መጪዎቹ ሦስት ሰንበቶች ስብከተ ገና ማለትም የጌታችንን ሰው መሆን ለምናከብርበት ወቅት መዘጋጃ የሚሆን ወቅት ነው። ኃያል፣ ቅዱስ፣ ሰማያዊው አምላክ እኛን መምሰል ሳይሆን እኛን መሆኑን የምናስታውስበት ልዩ ወቅት ነው። ስብከተ ገና የእሱ በዓለም ታሪክ ውስጥ መግባት የዓለምን አቆጣጠር ወደ ዓመተ ምሕረት እንደቀየረው ሁሉ የእኛንም ሕይወት በምሕረቱ ሊሞላት በርሱ በኩል ሁሌም ዝግጁ መሆኑ የሚሰበክበት ወቅት ነውና የዛሬው ሰንበት "ዘስብከት" ይባላል።

ከዛሬው ወንጌል በፊልጶስ፣ በናትናኤልና በኢየሰኡስ መካከል የተደረገውን ንግግር እንውሰድ። ፊልጶስ በኢየሱስ ከተጠራ በኋላ ናትናኤልን ሲያገኘው፦ "ሙሴ በሕግ መጽሐፍ ነቢያትም በትንቢት መጻሕፍት ስለ እርሱ የጻፉለትን አገኘነው፤ እርሱም የዮሴፍ ልጅ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነው" አለው። ናትናኤል ግን "ከናዝሬት መልካም ነገር ከቶ ሊገኝ ይችላልን?" አለው። ፊልጶስም "መጥተህ እይ" አለው። ኢየሱስ ናትናኤል ወደ እርሱ ሲመጥ ኣአይቶ "እነሆ ተንኮል የሌለበት እውነተኛ የእስራኤል ሰው!" ሲል ስለ እርሱ ተናገረ(ቁ.44-47)። ጊዜ ሰጥቶ በማስተዋል ላሰበው ሰው በነዚህ ቁጥሮች ውስጥ በተለያየ መልኩ ይሁን እንጂ ዘወትር የሚደጋገም እውነት አለ። እግዚአብሔር ደካማ ሆኖ፣ በሥጋ ሰው ሆኖ፣ በማይመስለን መልኩ ሲገለጽ ሰው ደግሞ ሲንቀውና ሲጠራጠረው ይታያል። "ከናዝሬት መልካም ነገር ከቶ ሊገን ይችላልን?" - እግዚአብሔር ናዝሬትን መረጣት፤ በማይመስልና በሚናቅ ነገር መሥራት ልማዱ የሆነ አምላክ ከጥንት ጀምሮ እስከዛሬም ይህን እውነት ያደርጋል።

ክርስቶስ የሰው ልጅን ለማዳን ሰው መሆን ነበረበትና ይህን ለመተግበርም ከኃጢአት በስተቀር እንደሰው ተቆጠረ፣ ተወለደ፣ ተናቀ፣ ተንገላታ፣ ተራበ፣ ተጠማ፣ ተሰደደ፣ ታማ፣ ለሌባና ለነፍሰ ገዳይ የሚደረግ ፍትሕና እንክብካቤ ተነፍጎት ተሰቀለ - ሞተ። እሱ ፍጹም ሰው ነበርና እያንዳንዷ ስቃይ እኛን ከምታሰቃየን በላይ ብዙ እጥፍ እንደምታሰቃየው መገመቱ ከባድ አይደለም።

ይህ በክርስቶስ ላይ የተፈጸመው እውነታ "በአንድ ወቅት" የነበረ ክሥተት አይደለም። እግዚአብሔር ዛሬም ደካማ ነገሮችን የመምረጥ አሠራሩን አልቀየረም፤ የሰው ልጅም የእግዚአብሔር ድካም በሆኑ ነገሮች ውስጥ የሚገኘውን ጸጋ መናቁን አላቋረጠም። የሚገርመው ነገር ደግሞ ደካማው ኃያሉን ሲንቅና ኃያሉ ግን ደካማውን ሲይከብረው ማስተዋሉ ነው። ናትናኤል ስለ ኢየሱስ "ከቶ ምን መልካም ነገር ይገኛል" ሲል ኢየሱስ ግን ስለ ናትናኤል "እነሆ ተንኮል የሌለበት እውነተኛ የእስራኤል ሰው" አለው።

"ከኅብስትና ከወይን ከቶ የክርስቶስ ሥጋና ደም ሊገኝ ይችላልን?" የሚሉ ዛሬ ዛሬ ቁጥራቸው ጥቂት ላይሆን ይችላል። ምናልባትም በቃላት ባይሉትና ባይክዱትም በተግባር ግን በመራቅና ባለመሳተፍ ይህን ንቀት በአክብሮት ስም የሚያስተጋቡትን አካቶ ማለት ነው (የምናከብረውንና የምንወደውን ላለመራቅ የሚቻለልን እንጥራለንና ቅዱስ ቁርባንን ስለማከብርና ስለምወድ አልቀርበውም የሚል አባባል በራሱ የተጋጨና ትርጉም የለሽ አባባል ነው)። ክርስቶስ ግን "ሥጋዬን የሚበላና ደሜንም የሚጠጣ ሁሉ የዘላለም ሕይወት አለው" (ዮሐ.6:54) ይለናል። እንደ ወንጌሉ ዛሬም እኛ ስንንቀውና ስናርቀው እሱ ይጋብዘናል፣ ያከብረናል ይቀርበናልም። የእሱ አካል የሆነችውና እሱ ፈቅዶ በተለመደ አመራረጡ በደካማ ሰዎች ላይ የቆረቆራትን ቤተ ክርስቲያንን በተለያየ መልኩ ለማናቅና ለማወረድ ጥረት ባደረግን ቁጥር ለንስሐና ለቅድስና ዘወትር በራሷ በኩል ይጋብዘናል።

ይህን ሀሳብ የእሱን መወለድ ለማክበር በምናደርገው ዝግጅት ሂደት ውስጥ በጸሎት እያሰላሰልን ዛሬም እግዚአብሔር ደካማ በሚመስሉ ነገሮች የሚያደግልንን ጥሪ ተቀብለን በክርስትና ሕይወት ውስጥ ዳግም የምንወለድበትን ጸጋ አናሳልፍ።

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት