እኛ ማነን

በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሥር የምንገኝ ሲታውያን መነኮሳን በአገራችን በአዲስ አበባ፣ በመንዲዳ፣ በሆሣዕናና በጎንደር ገዳማት ሲኖሩን፤ ዓላማችንም በወንጌል ላይ የተመሠረተውን የቅዱስ አቡነ ቡሩክ ደንብን (The Rule of St. Benedict) በመከተል ክርሰቲያናዊ የጥምቀት ጸጋችንን በምልአት በሲታዊ ትውፊት መኖር ነው።.....

ይህም በምንኩስና ሕይወታችን፤ በግላዊም ሆነ ማኅበራዊ ጸሎትና ሥራ በቀጣይነት እግዚአብሔርን የመፈለግና የማመስገን ሕይወት ነው። በአጭር ቃላት ሕይወታችን “ጸሎትና ሥራ” (Ora et Labora) በሚለው ዘመን ጠገብ ትውፊታችን ይገለጻል።

ለዚህም ግብ መሳካት “ከክርስቶስ ፍቅር ምንም ነገር ያለማስበለጥ” የሚለውን ደንባችንን በማሰላሰል ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ምስክርነት በጸጋው ተማምነን ለመኖር የወሰንን ነን።

በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እምነት መንፈሳዊ ትምህርቶች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ታሪክ፣ ሥርዓተ አምልኮ፣ ጸሎቶችና መንፈሳዊነትን ወደ ምንካፈልበት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ዜና ወደ ሚነገርበት፣ እንዲሁም በተቀደሰ ጋብቻም ሆነ በምንኩስና ሕይወት ወደ ቅድስና ጥሪ ለመጓዝ የሚያግዙ እውነታዎች ወደሚጋሩበት፣ የቅዱሳን ሕይወት፣ ሀብትና ትሩፋት ወደ ሚነገርበት፣ ባጠቃላይ የአምላካችን መልካም ዜና ወደሚታወጅበት ይህ ድረ ገጽ እንኳን በደህና መጡ!!

ከመ በኲሉ ይሴባሕ እግዚአብሔር!- እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይከብር ዘንድ፤ አሜን።1ጴጥ.4:11

Map St Joseph Cistercians

Top Panel

ዘምኩራብ፣ ዘመፃጉእ፣ ዘደብረ ዘይት፣ ዘገብር ኄር

Lent p2ዘምኩራብ                                                                      ዐቢይ ጾም 3ኛ ሳምንት

ንባባት፡- ቆላ 2፡16-23                     ሐ.ሥ. 10፡1-8

            ያዕ 2፡ 14-16                     ዮሐ 2፡13-25

መዝሙር “የቤትህ ቅንዓት በልታኛለችና፣ የሚሰድቡህም ስድብ በላይ ወድቋልና” (መዝ 69፡9)፡፡

የዐቢይ ጾም ሦስተኛ ሳምንት እሑድ ዘምኩራብ ተብሎ ይጠራል፡፡ ይህም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የአይሁድ ፋሲካ በዓል ለማክበር ወደ ኢየሩሳሌም መጥቶ በቤተ መቅደስ መግባቱንና በዚያም ይገበያዩ የነበሩትን አይሁድ ባየ ጊዜ የገመድ ጅራፍ አበጅቶ ሰዎች ሁሉ ከቤተ መቅደስ ማስወጣቱን የምናስብበት ሰንበት ነው፡፡

በዚህ ሰንበት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ባልሆነ ትርፍ ተግባር ተጠምደን እንዳንገኝ ያሳስበናል፡፡ በእግዚአብሔር ሥፍራ ሌላ ዓለማዊ ድርጊት እንዳይፈጸምበት ጌታችን በኃይለ ቃል ያስተምራል፡፡ ኢየሱስ በአይሁድ ቤተመቅደስ ገብቶ ያገኘው ነገር ከቤተመቅደሱ ዓላማ ጋር የሚጣጣም አልነበረም፤ የእግዚአብሔር መሆን የሚባው ነገር የሰው ሆኖ፣ የእግዚአብሔር ቤት ያለዓላማው ተይዞ ነበር፤ ስለዚህ ኢየሱስ የገመድ ጅራፍ አበጅቶ “ሰዎችን ሁሉ ከበጎችና ከበሬዎች ጋር ከቤተመቅደስ አስወጣቸው፤ የገንዘብ ለዋጮችንም ገንዘብ በተነ፣ ጠረጴዛዎቻቸውንም ገለባበጠ…” (ዮሐ 2፡15)፡፡

ይህ ሁኔታ ዛሬ ቤተክርስትያን ያለችበት ሁኔታ እንድንፈትሽ መልእክት ያስተላልፋ የእግዚአብሔር ቤት እንደስሟ ተገቢ ማንነቷን ጠብቃ መቆየቷን እና የእግዚአብሔር ባልሆነው ተርፍ ተግባር አለመጠመዷን መመልከቱ ተገቢ ነው፡፡ በቤተክርስትያን ልዩ ልዩ የኃላቺነት ሥፍራዎች የሚሰሩ ሰዎች ሁሉ አገልግሎቸው የእግዚአብሔርን ክብር የሚያንጸባርቅ ስመሆኑ ዘወር ብለው እንዲመለከቱ የዛሬው ወንጌል ጥሪ ያቀርባል፡፡ በየተሰማራንበት የስራ ዘርፍ የራሳችን የእውቀት ደረጃ፣ ዝና፣ ክብር ሁሉ የእግዚአብሔርን ክብር እና ሁሉን ቻይነት የሚጋርድ የትዕቢት ግድግዳ እንዳይሆን መጠንቀቅ እንዳለብን ኢየሱስ ይናገራል፡፡

በመጨረሻም በቤተመቅደስ ውስጥ ያለው ሁኔታ የእያንዳንዶቻችንን ሕይወት ይወክላል፤ ኢየሱስ ወደ እያንዳንዳችን ልብ ሲመጣ ልባችን የእግዚአብሔር ባልሆነው ትርፍ ነገር ተጠምዶ እንዳያገኘው የዛሬው ወንጌል ያሳስባል፡፡ ሁላችም በጌታ ኢየሱስ ክብር ደም የተገዛን የእግዚአብሔር አብ ውድ ልጆች እና የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደሶች እንደመሆናችን መጠን ልባችን ለእርሱ ጠብቀን ማቆየት ይገባናል፡፡ ኢየሱስ ማን መሆኑን ያላስተዋለው የቤተ መቅደሱ የገበያ ሁካታ በእያንዳንዳችን የዕለት ተዕለት ሕይወት ውስጥ ለኢየሱስ ተገቢ ቦታ የማይሰጠውን ጥድፊያ እና ሁካታ ያመለክታል፡፡ ኢየሱስ በዚህ ወጀብ መካከል ተገኝቶ ማዕበሉን ጸጥ በማሰኘት ታንኳይቱን ያረጋጋት ዘንድ ለእርሱ እናስረክብ፤ እርሱ በሁሉ ነገር ተገቢውን ቦታ ይያዝ፤ ይህ ሆኖ ሲገኝ እግዚአብሔር በእኛ ይከብራል፤ ቤተመቅደሱም ቅድስናውን ጠብቆ የበረከት ምንጭ ይሆናል፡፡

ዘመፃጉዕ                                                               ዐቢይ ጾም አራተኛ ሳምንት

ንባብ፡- ገላ 5፡14-20 ፤ ሐ.ሥ 3፡1-11 ፡ ዮሐ 5፡ 1-24

መዝሙር   እግዚአብሔር በደዌው አልጋ ሳለ ይረደዋል፤ መኝታውንም ሁሉ በበሽታው ጊዜ ያነጥፍለታል፤ በጠላቶቹም እጅ አያሳልፈውም፤እኔስ አቤቱ ማረኝ አልሁ›› (መዝ 41፡ 2-4)

የዐብይ ጾም አራተኛ ሳምነፍት ዘመፃጉዕ ተብሎ ይጠራል፡፡ ይህ ሰንበት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሽተኞችን የፈወሰበትን እና ወደ ሕሙማን ቀርቦ ከእነርሱ ጋር የተወያየበትን የፈውስ ተግባር የምናስብበት ሰንበት ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰላሳ ስምንት ዓመት በሕመም ይሰቃይ ወደነበረው ሰው ቀርቦ ጠየቀው፡፡ በዚያ ሁሉ ዓመታት ይህንን ሰው ወደ ፈውስ ውኃ የሚያስገባው ዘመድ አልነበረውም፤ አሁን ግን የፈውስ ባለቤት የሆነው አምላክ መጥቶ ‹‹መዳንን ትወዳለህን? ብሎ ይጠይቀዋል፡፡ ሰውየው ወደ ውኃው የሚያስገባው አለመኖሩን ይናገራል፡፡ የእርሱ ፈውስ በውኃው ዘንድ ብቻ መሆኑን አምኗል፡፡ ኢየሱስ ግን  ‹‹አልጋህን ተሸክመህ ሒድ ›› አለው፡፡ ሰላሳ ስምንት ዓመት በሕማም ሲሰቃይ የነበረው ሰው በቤተ መቅደስ ከወንድሞቹ ጋር ለመቆም በቃ፡፡ አልጋውን ተሸክሞ ኢየሱስ እንዳዳነው እየመሰከረ ሔደ፡፡

ይህ ሰንበት ዘመፃጉዕ ተብሎ ሲጠራ ሁላችንም ወደ ውስጣችን ቁስል በጥልቀት ተመልክተን ኢየሱስን እንድንጠራው ያሳስበናል፡፡ ሥጋዊና መንፈሳዊ ቁስሎቻችንን ለእርሱ በማቅረብ እንድንፈወስ ‹‹እናንተ ሸክም የከበደባችሁ ወደ እኔ ኑ እኔም አሳርፋችኋለሁ›› (ማቴ 11፡28) ያለውን ጌታ በማመን ወደ እርሱ እንጩህ፡፡ እያንዳንዳችን ለማንም የማናካፍለው ቁስል፤ እንዲህ ሆንኩ ብለን ለመናገር የማያስደፍረን ሕማም ፤ማንነት፤ በሱስ እሥራት ባርያ የሆንበት ነገር፤ ከሰው ተደብቀን የምንገዛለት እሥራት ወ.ዘ.ተ ይኖረናል፡፡ ኢየሱስ ይህንን አይጠየፍም፤ ታሪካችንን ሰምቶ ከጀርባችን አያወራም፤ ነገር ግን የእርሱ አመለካከት የተለየ ነው፡፡ ያ በውኃ አጠገብ ተኝቶ የነበረውን ታማሚ ባየው ጊዜ ‹‹ኢየሱስ እስከ አሁን ለብዙ ዘመን እንዲህ እንደነበረ ዐውቆ ልትድን ትወዳለህን›› (ዮሐ 5፡6) አለው፡፡

ለእያንዳንዳችን ሕማም፤ ቁስል፤ ባርነት፤ እሥራት ወ.ዘ.ተ የኢየሱስን ጥያቄ ይህ ነው ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ‹‹ልትድኚ ትወጃለሽን? ›› የእኛ ፋንታ እሺ ብሎ መዳን ነው፡፡ እሺ ብሎ መዳን! ስለዚህ ወደ ኢየሱስ ቀንበን ከእርሱ ዘንድ ለመፈወስ ጊዜው አሁን ነው፤ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በበለጠ እንዲህ እያለ ያበረታታናል ‹‹በተወደደ ሰዓት ሰማሁህ፤ በመዳንም ቀን ረዳሁህ ይላልና፤ እነሆ የተወደደው ሰዓት አሁን ነው፤እነሆ የመዳን ቀን አሁን ነው›› (2ኛ ቆሮ 6፡2) የመፃጉዕ ሰንበት እንግዲህ በሥጋዊ ዐይን ስለምናያቸው ሕሙማን የምናስብበት እኛን የማያጠቃልል በዓል ሳይሆን የራሳችንን ሥጋዊና መንፈሳዊ ቁስሎችና ሕማም ይዘን በኢየሱስ ፊት በትህትና በመቆም ፈውስ የምንለምንበት ጊዜ ነው፡፡

ደብረ ዘይት                                                                        ዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት

ንባባት፡- 1ኛ ተሰሎንቄ 4፡13-18 ፤ 2ኛ ጴጥ 3፡ 7-14፤ ሐ.ሥ 24፡ 1-21፤ ማቴ 24፡ 1-35

መዝሙር፡- ‹‹አምላካችን ይመጣል ዝምም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይቃጠላል፤በዙርያውም ብዙ ዐውሎ አለ›› (መዝ 50፡3)

ዐብይ ጾም አምስተኛ ሳምንት ደብረዘይት ተብሎ ይጠራል፡፡ የጾም እኩሌታ በመሆኑ እኩለ ጾም እየተባለ ይጠራል፡፡ ይህ ሰንበት ክርስቶስ በደብረዘይት ተራራ ሳለ ለሐዋርያቱ ስለዳግም ምፃቱ በግልጽ የተናገረበት እና ስለ ጊዜው ምልክቶች የሰበከበት ሰንበት ነው፡፡ ጌታችን በዚህ ወቅት የሁሉ ነገር ፍፃሜ እንደቀረበ ለሐዋርያቱና ለደቀመዛሙርቱ ይነግራቸዋል የእግዚአብሔር መንግስት በኃይል እና በክብር እንደሚገለጥ ሲያስተምራቸው ከእርሱ በፊት መከራ እና ጥንቅ እንደሚመጣ፤ አሳሳቾች እንደሚነሱ፤ታላላቅ ተዓምራቶች እንደሚደረጉ ወዘተ እየነገረ ከዚህ ሁሉ ተጠበቁ ይለናል፡፡

ይህ የደብረ ዘይት ሰንበት ጽኑ የሆኑት የእግዚአብሔር ልጆች ከብዙ መከራና ስቃይ በኋላ የእግዚአብሔር ልጅ በክብሩ ሲገለጥ እንደሚመለከቱት የሚያረጋግጥ የኢየሱስ ስብከት የምናሰላስልበት ሰንበት ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ስብከቱ በእርሱ ስም አማካኝነት በዓለም ሁሉ ፊት የተጠላችሁ ትሆናላችሁ ይላል፡፡ በዚያን ጊዜ ኢየሱስ ስም ሲጠራ አሜን የሚል ስደትና ሞትን ለመቀበል የደፈረ ጽኑ ሰው መሆን አለበት፡፡

አሜን ማለት ዋጋ የሚያስከፍልበት ዘመን እንደሚመጣ ኢየሱስ ይናገናል፡፡ አሜን ማለት ዛሬ አይደለም፤ነገር ግን የኢየሱስ ስም የጠላት ስም፤የጥፋት ስም፤የሞት ቅጣት ስም የሚሆንበት ዘመን ላይ አሜን ማለት ይቻል ይሆን? ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእነዚያ ጊዜያት”ከዐመጽ ብዛት የተነሳ የብዙ ሰዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች” እያለ ስጠነቅቃል፡፡ በፍቅር የሚጸና፤ ለመዳን ብሎ ሁሉን ታግሶ የሚጸና ብዙ ሰው እንደማይኖር ያስተምራል፡፡

ስለዚህ በዚህ በደብረዘይት ሰንበት ጌታችን”እነሆ አስቀድሜ ነገርኳችሁ” (ማቴ 24፡25) ይላል፡፡ የክርስትና ሕይወት የሚያስከትለውን ውጊያ አይተናል፤ ክርስቲያን መሆን የሚያስከፍለውን ዋጋ አውቀናል፤ የምንሸከመውን መስቀል ሽራፊ ተመልክተናል፤ የምናገኘውንም ድል አውቀናል ስለዚህ መወሰን አለብን! ክርስቲያን ነኝ ወይም ክርስቲያን አይደለሁም! መኃል ሰፋሪ መሆን የለም፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ስላደረገው የሕይወት ምርጫ ሲናገር “ከክርስቶስ ጋር ተሰቅያለሁ” (ገላ ፡ 20) እያለ ለገላትያ ክርስቲያኖች ምሥክርነቱን ይሰጣል፡፡ የመስቀሉ ኑሮ ምን እንደሚመስል ሲናገር“እኔም አሁን ህያው ሆኜ አልኖርም፣ ክርስቶስ ግን በእኔ ይኖራል፤ አሁንም በስጋ የምኖርበት ኑሮ በወደደኝና ስለ እኔ ራሱን በሰጠው በእግዚአብሔር ልጅ ላይ ባለ እምነት የምኖረው ነው” (ገላ 2፡20) ይላል፡፡ ክርስትያን መሆን በክርስቶስ ከክርስቶስ ጋር መኖር ማለት ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ክርስትና የኑሮ ዘይቤ ሲናገር “እኔ ባለሁበት አገልጋዬም በዚያ ይኖራል” (ዮሐ 12፡26) ይላል፡፡ ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጎ በአብ ቀኝ አለ፡፡ እሱ ባለድል ሆኖ ከነሙሉ ክብ በአባቱ ዘንድ አለ፡፡ የእያንዳንዱ ክርስትያን ድል ይህ ነው፡፡ በዚህ ድል በክርስቶስ ኢየሱስ ተመርጠናል፡፡ ነገር ግን ይህ ድል ምን አይነት ድል ነው?

ይህ የክብር ድል የመስቀል መንገድ ድል ነው፡፡ ኢየሱስ በመስቀል መንገድ ሔዶ የከፈተው የድል በር ነው፡፡ ማንም በዚህ የድል በር መግባት እና የእግዚአብሔርን መንግስት ወርሶ ከክርስቶ ጋር መንገስ ቢፈልግ  ኢየሱስ በግልጽ መመርያውን ይሰጣል፡፡”መስቀሉን ተሸክሞ ይከተለኝ” (ማቴ 16፡24)፡፡ ወዴት? ኢየሱስ መስቀሉን ተሸክሞ ወደሚሰቀልበት ሥፍራ ወጣ፡፡ የመስቀሉን ሥራ ፈጸመ፡፡ ሞተ፤ተቀበረ፤በሦስተኛው ቀን ሞትን ድል አድርጎ ተነሳ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን የመስቀል ጉዞ ሲያብራራልን “ሞቱን በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ከተባበርን፤ ትንሳኤውን በሚመስል ትንሳኤ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንተባበራለን” (ሮም 6፡5) ይላል፡፡ ስለዚህ ያለ ስቃይ ክብር፤ያለ መስቀል አክሊል፤ያለውጊያ ድል የለም፡፡

ደብረዘይት ሰንበት ቀደም ሲል እንደተመለከትነው የጾም እኩሌታ በመሆኑ እኩለ ጾም ተብሎ ይጠራል፡፡ ጾማችንን ማጋመሳችን ፤ ወደ ትንሳኤው መቅረባችንን የሚያሳስበን ሰንበት ነው፡፡ስለዚህ ያለፉት አራት ሰንበቶች እንዴት አለፉ?ብለን የምናሰላስልበት አጋጣሚ ነው፡፡ አንድ ወር ያህለ የዓብይ ጾም ውስጥ ስንቆይ ምን አተረፍን? ከውጊያው አፈግፍገን ከሆነ የተዳከምንባቸው ምክናያቶች ምንድናቸው?እነዚህን ጥያቄዎች አበክረን በመጠየቅ እንደ ጥንቁቅና ብልህ ነጋዴ ከእግዚአብሔር ጋር የምንተሳሰብበት ሳምንት ነው፡፡

 
እንዲሁም ደግሞ በቀጣዮቹ የዐብይ ጾም ሳምንታት የበለጠ ተጋድሎ በማድረግ የምንበረታበት ይሆን ዘንድ ታጥቀን የምንነሳበት ሳምንት ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለዚህ እያዘጋጀን መንገዱን ይጠቁመናል”በቀረውስ በጌታና በኃይሉ ችሎት የበረታችሁ ሁኑ፡፡ የዲያቢሎስን ሽንገላ ትቃወሙ ዘንድ እንዲቻላችሁ የእግዚአብሔርን የጦር ዕቃ ሁሉ ልበሱ” (ኤፌ 6፡10-11)  

                                                    

ሰኞ                                                                     ዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት

            የሉቃስ ወንጋል በ15ኛው ምዕራፍ ጠፍተው ስለተገኙ ሦስት ነገሮች በምሳሌ እያስተማረ እኛም ከጠፋንበት ሥፍራ እንመለስ ዘንድ ይጋብዘናል፡፡ እነዚህ ምሳሌዎች የሚያሳስቡን ዐብይ ቁምነገር አንድ ውድ የሆነ ነገር ከጠፋን ባለን ኃይል ሁሉ ተጠቅምን እስከምናገኘው ድረስ እንደምንፈልገው የሚገልጽ ነው፡፡ሰው የሚወደውን ነገር ሲያጣ የሚሰማው ስቃይ ከባድ ነው፡፡ እነግዲህ በሞት ከምንወደው ሰው ስንለያይ፤ በሕይወት አጋጣሚ ከወዳጆቻችን ስንራራቅ ወዘተ ከባድ ኃዘን ይሰማናል፡፡

            እግዚአብሔር አባታችን ልጆቹ በማወቅም ባለማወቅም ከእርሱ ሲርቁ ልቡ ያዝናል፡፡ ወደ እርሱ እንድንመለስ ይናፍቃል፡፡ ፀጋውን በመስጠት ወደ እርሱ እንቀርብ ዘንድ ዘወትር የልባችንን በር ያንኳኳል፡፡ ምንም ያህል ከእግዚአብሔር ርቀን የተጓዝን ብንሆንም ወደ እርሱ ለመመለስ የሚያስፈልገው አንድ እርምጃ ብቻ ነው! ይህ የዐብይ ጾም ጊዜ በእግዚአብሔር ምሕረት በመተማመን ወደ እርሱ ለመመለስ፤አንድ እርምጃ ወደእርሱ ለመቅረብ የምንወስንበትና የምንራመድበት ወቅት ነው፡፡ ስለዚህ “አንተ የምታንቀላፋ ንቃ፤ ከሙታንም ተነስ፤ክርስቶስ ያበራልሃል” (ኤፌ 5፡14)

ማክሰኞ                                                                         ዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት

            የሉቃስ ወንጌል ስለጠፋው ልጅ የሚያደርገው ትረካ ሁለት መልሶች የያዘ ነው፡፡ የመጀመሪያው በልጁ መመለስ የተደሰተው አባት ያደረገው ነገር ሲሆን፤ሁለተኛው ደግሞ በወንድሙ መመለስ የተበሳጨው ታላቁ ልጅ የፈጸመው ተግባር ነው፡፡

ይህንን ሓሳብ በጥልቀት ስናስተነትን እኛ  ከፈጣሪያችን ጋር ሊኖረን ስለሚገባው ጤናማ ግንኙነት እንደሚናገር ማየት ይቻላል፡፡ በተለይ በዚህ በዐብይ ጾም ልናከናውነው የሚገባንን ነገር ያሳስበናል፡፡ ይህ ታላቁ ልጅ ዘወትር የሚኖርበትን የአባቱን ቤት ጠዕም አጣጥሞ አያውቅም፡፡ የአባቱን ቤት ጣዕም፤ በአባቱ ቤት ያለውን ክብር ለማስተዋል ልቦናው ተዘግቶ ነበር፡፡ በቤትህ ያለውን የፍቅር ጣዕም ማጣጣም ካልቻልክ በአካል በቤት ውስጥ ብትገኝም በልብህ ግን የከፋ ስደት ላይ ነህ፡፡

            ሰው በቤቱ፤ በትዳሩ፤ በሥራው፤ በመንፈሳዊ ሕይወቱ የእግዚአብሔርን ጣዕም መቅመስ ካልቻለ፤ የእግዚአብሔርን ለዛ ማጣጣም ካልቻለ በመንፈሱ ሙት ነው፡፡ ሕይወቱም የስደት ሕይወት ነው፡፡ስለዚህ በዐቢይ ጾም በእግዚአብሔር ቤት ባለን ሕይወት የእግዚአብሔርን ለዛ እያጣጣምን ነውን? በአባታችን ቤት ያለውን ፍቅር፤ሰላም፤ደስታ፤ተስፋ፤ በትዳራችን፤በልጆቻችን መካከል፤ በሥራ ገበታችን በመንፈሳዊ ሕይወታችን ምን ያህል ተጠቅመንበታል? ብለን ራሳችንን እንድንመረምር ይጋብዘናል፡፡

                      

ረቡዕ                                                                                 ዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት

            ታናሹ ልጅ ወደ ሩቅ ሀገር ተሰደደ፡፡ በዚያም ያለውን ነገር ሁሉ አባከነ፡፡ ሥራውም በሙሉ ትርፍ አልነበረውም፡፡ ገንዘቡን አጥፍቶ እስከምጨርስ ድረስ ብዚ ወዳጆች በዙርያው ነበሩ፤ነገር ግን ገንዘቡ ባለቀበት ጊዜ ማንም አብሮት አልቆየም፡፡የዕለት ቁራሽ እንጀራ የሚሰጠው ሰው ሰላጣ ወደ አሳማዎች ዘንድ እንደሄደ ወንጌል ይናገራል፡፡

            በመጽሐፍ ቅዱስ አአነጋገር አሳማ የተዋረደ ሕይወት ምሳሌ ነው፡፡ ልጁ ከአባቱ ቤት ከወጣ ጀምሮ ምን ያህል የአባቱ ክብር እንደጎደለውና ሕይወቱ ዋጋ እንዳጣ ያስገነዝበናል፡፡ በእኛም ሕይወት ዛሬ የእግዚአብሔር ክብር ጎድሎ ይሆን? በብዙ ቦታ ወጣቶች በሱስ፤በአጸያፊ ፊልሞች፤በኢ-ግብረገባዊ ባሕርያት ምርኮኛ ሆነው ለእግዚአብሔር ልጆች በማይገባ የተዋረደ ሕይወት ይኖራሉ፡፡ ኢየሱስ ግን እነዚህን ወጣቶች ነፃ ሊያወጣቸው ይፈልጋል፡፡ ከባርነት ቀንበር አላቅቆ የእግዚአብሔርን ክብር ሊያለብሳቸው ይፈልጋል፡፡

            ታናሹ ልጅ ወደ ደአባቱ ቤት ለመመለስ ቁርጥ ፈቃድ አድርጎ ጉዞ እንደጀመረ ሁሉ እኛም በዚህ በዐብይ ጾም ቁርጥ ፍቃድ ልናደርግባቸው የሚገቡንን የሕይወት ዘርፎች በመመርመር መመለስ ያስፈልጋል፡፡ የተማረክንባቸውን ውጊያዎች እንደጋ ተዋግተን ድል በመንሳት የእግዚአብሔር ልጆች ክብር እንድንወርስ ቁርጥ ፈቃድ አድርገን እንነሳ፡፡

ሐሙስ                                                                               ዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት

            በዚህ በደብረዘይት ሳምንት ኢየሱስ በተራራ ላይ ለደቀመ መዛሙርቱ ምሥጢሩን እንደገለጠላቸው ወንጌል ይናገራል፡፡ እነዚህ ደቀ መዛሙርት ለብቻቸው ወደ እርሱ ቀርበው የትምህርቱን ትርጉም እነደጠየቁት አንብበናል(ማቴ 24፡3)፡፡ ለብቻቸው ወደ ኢየሱስ መምጣታቸው ላይ አተኩረተን ስንመለከት ወደ ራሳችን ሕይወት ይመልሰናል፡፡ በግል የጸሎት ሕይወታችን ከኢየሱስ ጋር የልብ ለልብ ውይይት ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን ያሳየናል፡፡ ይህ የልብ ለልብ ልውውጥ የሕይወታችንን ምሥጢራዎ ነገሮች በግልጽ የምናስተውልበት መልካም አጋጣሚ ነው፡፡

            በዚህ የዐብይ ጾም ጊዜ ቅዱስ ቁርባን የመጎብኘትና በጽሙና ከኢየሱስ ጋር የመወያየት መንፈሳዊነት በመለማመድ የጸሎት ሕይወታችን የበለጠ ፍሬአና እንዲሆን ማድረግ አለብን፡፡ በቅዱስ ቁርባን ፊት በጽሞና ከኢየሱስ ጋር የሚደረገው ውይይት ብዙ በረከት የሚያስገኝ በመሆኑ ይህንን መንፈሳዊ ኃብት በሚገባ ልንጠቀምበት ያስፈልጋል፡፡ ኢየሱስ በቅዱስ ቁርባን ሆኖ የእኛን መምጣት በመጠባበቅ ድንዲህ ይላል”ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ” (ዮሐ 7፡37)

ዘገብረ ኄር  የዐብይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት

ንባባት፡- 2 ጢሞ 2፡1-15፤ 1 ጴጥ 5፡ 1-11፤ ሐ.ሥ  1: 6-8፣ ማቴ 25፡14-30

መዝሙር “አምላኬ ሆይ ፈቃድህን ለማድረግ ወደድሁ፤ ሕግህም በልቤ ውስጥ ነው” (መዝ 40፡8)

ሰንበት ዘገብረ ኄር ከእግዚአብሔር የተቀበልነውን ጸጋ የምናሰላስልበት ሰንበት ነው፡፡ በቀላሉ ይህንኑ ሰንበት የመክሊት ሰንበት ነው ማለት እንችላለን፡፡ እያንዳንዳችን ወደዚህ ምድር ስንመጣ የየራሳችንን የጸጋ ሥጦታ ወይም መክሊት ተሰጥቶናል፡፡ በዚህ በተሰጠን ጸጋ አምላክንና የሰው ልጆችን እንድናገለግል ግዴታ አለብን፡፡ ይህንን ጸጋ ከፍቅሩ የተነሳ የሰጠን አምላክ አንድ ቀን እንደ ጥንቁቅ ገበሬ ምርቱን ሊሰበስብና ከእኛ ጋር ሊተሳሰብ እንዲመጣ ወንጌል ይናገራል፡፡

የገብረ ኄር ሰንበት ወደ ፋሲካ እየተቃረብን መሆኑን ያመለክተናል፡፡ ከሁለት ሳምንት በኋላ ሰሙነ ህማማት ይጀምራል፡፡ ስለዚህ የእስከዛሬው ጉዟችንን በተመለከተ መለስ ብለን መፈተሸ ይገባናል፡፡ በየተሰጠን የጸጋ ስጦታ ምን እያደረግንበት ነው? ሕይወታችን ምን ይመስላል? ከወንድሞቻችንና ከእህቶቻችን ጋር ያለን ግንኙነት እንዴት ነው? ጾማችን ምን ይመስላል? በተለይ በየተጠራንበት የሕይወት ጥሪ፣ በየተሰማራንበት የአገልግሎት መስክ በተሰጠን ጸጋ አትራፊዎች መሆን አለመሆናችንን መፈተሸ እንዳለበን የገብረ ኄር ሰንበት ያሳስበናል፡፡ ጾማችን እየተገባደደ፣ ወደ ትንሳኤው ክብር እየቀረብን በመሆኑ የትንሳኤው ጌታ “አንተ ታማኝና ደግ አገልጋይ!” በሚል ስም ይጠራን ዘንድ በተጋችን የምናፈራበት ጊዜ አሁን ነው፡፡ የእግዚአብሔር ክብር ተካፋዮች ለመሆን ፍሬ ሊገኝብን ግድ ነው፡፡

የዛሬው የመጀመርያው ንባብ ይህንን በግልጥ የሚያረጋግጥልን ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለወጣቱ አገልጋይ ለጢሞቲዎስ የሚያቀርብለት ምክር “በክርስቶ ኢየሱስ ባለው ጸጋ በርታ” (2 ጢሞ 2፡1) የሚል ነወ፡፡ በጸጋህ ለማገልገል የሚተጥሙህ ውጣ ውረዶች በሙሉ በኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ለምታደርገው ሱታፌ ምስክሮች በመሆናቸው እንደ ቅድስና መሰላል ተመልከታቸው እያለ ያበረተታዋል፡፡ በዚህ አይነት በመክሊታችን ለማትረፍ የምናደርገው ነገር ሁሉ ቀላል እንዳልሆነ እንመለከታለን፡፡ በጸጋ ፍሬ አፍርተን ለመገኘት በውጊያ ብርቱዎች መሆን ይገባናል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን መንፈሳዊ ውጊያ በግልጽ በማመልከት “የእውነትን ቃል በቅንነት የሚናገር የሚያሳፍርም ሠራነተኛ ሆነህ የተፈተነውን ራስህን ለእግዚአብሔር ልታቀርብ ትጋ” (2ጢሞ 2፡15) ይላል፡፡ ይህ ውጊያ ታድያ ትርፉ ምንድነው ብለን ብንጠይቅ የዚህ ውጊያ ሽልማት በእግዚአብሔር መንግሥት ከክርስቶ ጋር ወራሽ ሆነን መክበር ነው፡፡

“ብንጸና ከእርሱ ጋር ደግሞ እንነግሳለን” (2ጢሞ 2፡12)፡፡ ሰው ሁሉ የተከበረ ነገር ለማግኘት ይመኛል፡፡ የተሻለ ኑሮ፣ የተሻለ ደመወዝ ወዘተ እነዚህን ነገሮች ለማግኘት በሥራ ፍለጋ፣ በትምህርት ራስን በማሻሻል፣ በትርፍ ጊዜ ሳይቀር በመስራት ወ.ዘ.ተ. በርካታ ትግል እናደርጋለን፡፡ አማራጭ የሆኑ ነገሮችን ሁሉ እንሞክራለን፡፡ ይህንን ሁሉ ስናደርግ መነሻችን ሁልጊዜ እጃችን ላይ ያለን ነገር ነው፡፡ እጃችን ላይ ያለን ገንዘብ፣ ዕውቀት፣ የተሻለ ሀሳብ ወ.ዘ.ተ. በእርሱ ተጠቅመን ለማደግ ለመለወጥ በርካታ እናደርጋለን፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በውስጣችን ያለውን ጸጋ እንድንመለከት፣ በእርሱም ፍሬ እንድናፈራ አደራ ይለናል፡፡ “የተቀበላችሁትን ጸጋ በከንቱ አታስቀሩት (2 ቆሮ 6፡1) በማለት በጸጋችን፣ በመክሊታችን ለነፍስና ለስጋ የሚሆን ፍሬ እናፈራ ዘንድ ያበረታታናል፡፡ በመክሊታችን በመስራት ለስጋ እና ለነፍስ የሚተርፍ ፍሬ እናፈራ ዘንድ ተጠርተናል፡፡ ለዓለማዊው ክብርና ዝና፣ የተሻለ ሕይወት ለማግኘት ወ.ዘ.ተ. ይህን ያህል ከለፋን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል የተሰጠንን ዘላለማዊ ሕይወት ለመውረስ ምን ያህል በብርቱ መጋደል ይኖርብናል፡፡ ነገር ግን ምንም ያህል ውጊያው ኃይለኛ ቢሆንም ከእኛ ጋር ያለው እግዚአብሔር በመንገዳችን ከሚገጥሙን ነገሮች ሁሉ ይበልጣል፡፡

በዚህ መንፈሳዊ ውጊያ ላይ መሪዎች ለሆኑት ደግሞ የእግዚአብሔር ቃል ይናገራል፡፡ በህዝበ እግዚብሔር መካከል ኢየሱስ ክርስቶስን በመወከል እንደመገኘታቸው መጠን እግዚአብሔር ከእነርሱ ብዙ ይጠብቃል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የሐዋርያት አለቃ ሆኖ፣ የመንግስተ ሰማያት ቁልፎች በእጁ የተሰጠው ሆኖ ሳለ (ማቴ 16፡13-18) በእግዚአብሔር ህዝብ መካከል እረኛ የሆነበትን ተግባር በጥንቃቄ እንደሚፈጽም በማስታወስ “በእናንተ ዘንድ ያለውን የእግዚአብሔር ጸጋ ጠብቁ፣ እንደ እግዚአብሔር ጸጋ በውድ እንጂ በግድ ሳይሆን፣ በበጎ ፈቃድ እንጂ መጥፎውን ረብ በመመኘት ሳይሆን ጎብኙት” (1ጴጥ 5፡2) ይላል፡፡

የእረኝነት ተግባር ሚዛን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ ነው፡፡ የእረኝነት መለኪያውን ሲናገር “መልካም እረኛ ህይወቱን ስለ በጎቹ አሳልፎ ይሰጣል (ዮሐ 10፡ ) ይላል፡፡ በተለያየ የቤተክርስትያን ህይወት ዘርፍ የእረኝነት ተግባር ለሚፈጽሙ ሁሉ ሐዋርያዊ ቅዱስ ጴጥሮስ ጥሪውን ያቀርባል “ለመንጋው ምሳሌ ሁኑ እንጂ ማህበሮቻችሁን በኃይል አትግዙ” (1ጴጥ 5፡3)፡፡ ምክንያቱም የእረኞች አለቃ ሂሳቡን ሊያወራርድ ወደ እናንተ ደግሞ ይመጣል፡፡ “ራሳቸውን ለሚያሰማሩ ለእሥራኤል እረኞች ወየውላቸው!... እነሆ በእረኞች ላይ ነኝ፤ በጎቼንም እፈልጋለሁ” (ሕዝ 34፡2፤10)፡፡ በዚያን ጊዜ መልካም ፍሬ አፍርተው የሚገኘ እረኞች ደግሞ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ እንደሚያረጋግጠው “የእረኞች አለቃ በሚገለጥበት ጊዜ የማያልፈውን የክብር አክሊል ይቀበላሉ” (1ጴጥ 5፡4)፡፡

ወደ ወንጌሉ ስንመለስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተከታዮቹ በጸጋቸው ፍሬ ያፈሩ ዘንድ በምሳሌ ሲያስተምራቸው እንመለከታለን፡፡ ይህ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ የእያንዳንዳችንን ህይወት የሚመለከት ነው፡፡ የጸጋ ስጦታ ሳይኖረው የተወለደ ማንም የለም፡፡ መክሊት ክርስትያን በመሆን የሚገኝ ሽልማት ሳይሆን እግዚአብሔር “ሰውን በአርአያችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር” ባለ ጊዜ (ዘፍ 1፡26) በሰው ልጆች ሁሉ ውስጥ ያኖረው እንደመፈጠራችን መጠን ከእግዚአብሔር ሁሉን ቻይነት እንደ አቅማችን ስጦታ ወስደናል፡፡

የዛሬው ወንጌል የኢየሱስ ምሳሌ ማቅረብ ሲጀመር “ለእያንዳንዱ እንደ አቅሙ ሰጠ” ይላል (ማቴ 25፡14)፡፡ እንደ አቅሙ የሚለው ቃል መሰረታዊ ነው፡፡ እያንዳንዳችን እንደ አቅማችን ተሰጥቶናል ማለት የእኔ መክሊት በአቅሜ ተለክቶ የተሰጠኝ በመሆኑ ከእኔ የሚተበቀው በእርሱ ፍሬ ማፍራት ብቻ ነው፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ቁምነገሩ “ፍሬ ማፍራት” የሚለው ነው እንጂ “የፍሬው መጠን” አይደለም፡፡ ብዙ ጊዜ እኔ እንደ እገሌ ይህ ስጦታ ቢኖረኝ፣ ያንን ማድረግ በቻልኩ ወ.ዘ.ተ. እያልን እራሳችንን እናነፃፅራለን፡፡ ይህ ትክክል አይደለም፡፡ የእያንዳንዳችን ስጦታ በእግዚአብሔር ፊት እጅግ የከበረ እና በአንድ ልጁ የደም ዋጋ የሚመን ነው፡፡ እግዚአብሔር በጸጋ ስጦታው አያወዳድርም፣ አየሰበላልጥም  ስለዚህ የእኛ ቁልፍ ተግባር በጸጋችን ፍሬ ማፍራት ነው፡፡

ሶስቱ አገልጋዮች በጌታቸው ፊት በቀረቡ ጊዜ እንደ አቅማቸው ተጠየቁ እንጂ ለምን አንተ እንደዚህኛው አላፈራህም አልተባሉ፡፡ የእኛ መክሊት ምንም ይሁን ምን ለእግዚአብሔር እጅግ ውድና የከበረ ነው፡፡ ዋጋው በሰጪው ዘንድ ነው እንጂ በተመልካች ዘንድ ባለመሆኑ ሥጦታችንን ከማንም ጋር ማነፃፀር አይገባንም፤ ይልቁንም ለጸጋ ስጦታው ታማኝ በመሆን እንበርታ፡፡ የጸጋ ስጦታ የተሰጠን “የእግዚአብሔርን ቤተክርስትያን ለማነጽ ነው” ስለዚህ በዚህ ውስጥ ሁላችንም ድርሻ አለን፡፡ ቅድስት እማሆይ ትሬዛ እንደሚሉት “የእኛ አስተዋጽኦ በውቅያኖስ ውስጥ ጠብታ ውሀ እንደመጨመር ሊመስለን ይችላል፤ ነገር ግን ጠብታውን ባለመጨራችን ውቅያኖሱ ይጎድላል”፡፡ ስለዚህ እያንዳንዳችን በኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ እንበርታ፡፡

ከወጣት ሳምሶን ደቦጭ - ቅ.ዮሴፍ ቁምስና ዘሲታውያን - አ.አ.

አድራሻችን

logo

                 ገዳመ ቅዱስ ዮሴፍ ዘሲታውያን

                    ፖ.ሳ.ቁ. 21902
                 አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ
             Phone: +251 (116) 461-435

              Fax +251 (116) 458-988

               contact@ethiocist.org

             https://www.ethiocist.org

 
 

ለድረ ገጻችን የሚሆን ጽሑፍ ካለዎ

1- የኢሜል አድራሻችንን webpageorganizers@gmail.comን ተጠቅመው አሊያም

2- ይህን ሲጫኑ በሚያገኙት CONTACT FORMበሚለው ቅጽ ላይ ጽሑፍዎን ለጥፈው ወይም 

3-facebook አድራሻችን https://www.facebook.com/ethiocist.org በግል መልእከት ይላኩልን

በተጨማሪም የሚያካፍሉት ጠቃሚ የድረገጽ አድራሻ ካለዎ ይላኩልን።   

መልእክት ከር.ሊ.ጳ. ፍራንቼስኮስ

pope"ይቅርታን እና ምሕረትን ማድረግ የሰላማዊ ሕይወት መሠረት ነው"።

“ይቅር ማለት እና ምህረትን ማድረግ የሕይወት ዘይቤያችን ቢሆኑ ኖሮ፥ ስንት ጦርነት፣ ስቃይ እና መከራን እናስቀር ነበር! በግንኙነቶቻችን ሁሉ ይቅርታን የሚያደርግ ፍቅር ያስፈልጋል። ይኸውም በባል እና ሚስት፤ በወላጆች እና በልጆች መካከል እንዲሁም በአካባቢያችን፣ በማኅበረሰባችን እና በፖለቲካውም ማለት ነው። እንዲሁም ይቅርታን ለማድረግ ጥረት የማናደርግ ከሆነ፥ ይቅር አይባልልንም” ማለታቸው ተገልጿል።

ምንጭ - ቫቲካን ራድዮ አማርኛ ዝግጅት