የነፍስ ኄር አባ ጥዑም ተስፋይ አጭር የሕይወት ታሪክ
- Category: ዝክረ ሙታን
- Published: Thursday, 20 February 2014 15:10
- Written by Super User
- Hits: 1238
- 20 Feb
የነፍስ ኄር አባ ጥዑም ተስፋይ አጭር የሕይወት ታሪክ
በየካቲት 2: 2006 ዓ.ም. በትግራይ ክልል በምብራቃዊ ዞን በኢሮብ ወረዳ በልደታ ለማርያም ካቶሊክ ቤተ ክርቲትያን ስርዓተ ቀብራቸው የተፈጸመ ነፍሰ ኄር ኣባ ጥዑም ተስፋይ ከወላጆቻቸው ኣቶ ተስፋይ ደበሳይና ከእናታቸው ወ/ሮ ባህጉ ወልደ በኢሮብ ወረዳ ልዩ ስሙ ዳውሃን በተባለችው መንደር በታህሳስ 17: 1947 ዓ.ም. ተወለዱ::
ነፍሰ ኄር ኣባ ጥዑም ተስፋይ ኣንደኛ ደረጃ ትምህርታቸው ከ1960 – 1965 ዓ.ም. በልደታ ለማርያም ተከታትለዋል:: በ1966 ዓ.ም. የሰባተኛ ክፍል ትምህርታቸው በሲታውያን ገዳማዊያን ማኅበር በመግባት በአሥመራ ተከታትለዋል:: ከ1968 -1969 ዓ.ም. በመንዲዳ በሲታዊያን ማኅበር 8ኛና 9ኛ ክፍል ተምረዋል:: በ1970 ዓ.ም. በማኅበሩ ሕግ መሠረት በመንዲዳ የአንድ ተመክሮ ዓመት ፈጽመዋል:: በ1971 ዓ.ም 10ኛ ክፍል በአዲስ አበባ ካቴድራል 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ካጠናቀቁ በኋላ 11ኛ ና 12ኛ ክፍል ከ1972-1973 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ዘርአ ክህነት አጠናቅቀዋል::
ከ1974 – 1976 ዓ.ም. በኣሥመራ በአቡነ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን ታዕካ ጥበብ የነገረ መለኮትና ፍልስፍና ተቋም የሁለት ዓመት ፍልስፍናና የአንድ ዓመት ትምህርተ መለኮት ተምሯል:: ከዚህም በኋላ ከ10 ዓመታት የሲታውያን ማኅበር ቆይታ በኋላ ወደ ዓዲግራት አገረ ስብከት ዐቢይ ዘርአ ክህነት ቀይረው
ከ1977 -1979 ዓ.ም. በአዲግራት ከፍተኛ መንፈሳዊ ኮለጅ ለሶስት ዓመት የትምህርተ መለኮት ትምህርት ከተከታተሉ በኋላ በሚያዝያ 18: 1979 ዓ.ም. ከሶስት የትምህርት ጓደኞች ጋር የአገረ ስብከቱ ካህን በመሆን በብጹዕ አቡነ ኪደነማርያም ተክለኃይማኖት እጅ ሢመተ ክህነትን ተቀብለዋል::
ነፍሰ ኄር ክቡር አባ ጥዑም ተስፋይ መዓርገ ክህነት እንደ ተቀበሉ በዓሊቴና የልደታ ማርያም ቆሞስ ተሰይመው ከ1980 -1989 ዓ.ም. ከፍተኛ መንፈሳዊ አገልግሎት አበርክተዋል::
በ1990 ዓ.ም. ለከፍተኛ ትምህርት ወደ ሮማ ተልከው ከ1990 -1994 ዓ.ም. በዮሃንስ ላተራን ጳጳሳዊ ዩንቨርስቲ ፓስቶራል ቴዮሎጂ አጥንተው በማስትረይት ድግሪ ተመርቀዋል:: ትምህርታቸውን በብቃት ከፈጸሙ በኋላ ወደ ትውልድ አገራቸው ተመልሰው በአድግራት ሃገረ ስብከት የምእመናንና የወጣቶች መሪ ካህን በመሆን ከ1995 -2000 ዓ.ም. እያገለገሉ ቆይተዋል:: በመቀጠልም የአመራር ብቃታቸው ታይቶ በአድግራት ሃገረ ስብከት ካቶሊክ ጽህፈት ቤት ምክትል አስተዳደሪና የሐዋርያዊ ሥራ መሪ ሆነው እስከ እለተ ህልፈታቸው ጥር 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ክህነታዊ አገልግሎታቸውን በብቃትና በታታሪነት እየተዋጡ ቆይቶዋል::
በአገልግሎት ዘመናቸው በኢትዮያና በዩጋንዳ ከሃለፍነታቸው ጋር የሚስማሙ በርከት ያሉ ስልጠናዎች እንደ ወሰዱ የግል ማህደራቸው ሲያመለክት ነፍሰ ኄር ኣባ ጥዑም ተስፋይ ከመደበኛ ሥራቸው በሻገር የአገር አቀፍ የአብያተ እምነቶች ተቋማት ጥምረት የብሄራዊ ኮሚቴ አባል በመሆንና በትግራይ ክልል የአብያተ እምነቶች ጥምረት ኮሚቴ አባል በመሆን በኀብረተ ሰብ መካከል ለላም ለማስፈን ጥረት እያደረጉ የቆዩ ታታሪ ካህን እንደነበሩ በቅርብ የሚያውቋቸው የሚመሰክሩላቸው ሀቅ ነው:: ከዚህ በተጨማሪም "ፍትህና ሰላም በኅብረተሰብ ውስጥ ማስፈን" ከሚለው የካቶሊክ ቤተ ክርስትያን መርሆ በመነሳት የአድግራት ሀገረ ስብከትን በመወከል ከኦርቶዶክስ ቤተ ክርስትያን፣ ከእስልምና ሃይማኖት፣ ከህብረተሰብ የተመረጡ የእድሜ ባለፀጋዎችና ከመንግስት መዋቅር የተወከሉ የሕግ ባለሟያዎች ጋር በኮሚቴ ሊቀመንበርነት በመምራት በርከት ያሉ የእርቅ ሥነ ስርዓቶች በመፈጸም ኅብረተሰቡ ከግጭትና ሁከት ተላቆ ሰላማዊ ሕይወት እንዲመሩ ያደረጉ ታላቅ የሰላም ሐዋርያ እንደነበሩ ባለፉት ሶስት ዓመታት ባሳዩት የአገልግሎት እንቅስቃሴያቸው አስመስክረዋል:: {jathumbnail off}
ነፍሰ ኄር አባ ጥዑም በመላዪቱ የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ከጫፍ እስከ ጫፍ በመለያየት በሐዋርያዊ ሥራዋ ለሚደረጉ መነቃቃቶችና ልዩ ልዩ የስልጠና ዝግጅቶች ከፍተኛ ሚናን ያበረከቱ በመሆናቸው ከአዲግራት ሀገረ ስብከት ውጪም በመላ አገሪቱ በብዙ ካቶሊካውያን ታዋቂና ተወዳጅ ካህን ናቸው። የሳሆ፣ ትግርኛ፣ አማርኛ፣ እንግሊዘኛና ጣሊያንኛ ቋንቋዎች ችሎታ የነበራቸው ነፍሰ ኄር ኣባ ጥዑም ተስፋይ ለፍትህና ሰላም ልዩ ትኩረት የነበራቸው ፤ ሰው አክባሪ፣ ትሁት፣ ቅኑ ፣ ፈገግታ ከፊታቸው የማይለያቸውና ፍቅር ሰጥቶ ፍቅር የመቀበል ችሎታ የነበራቸው እስከ ድንገተኛው የኅልፈት እለታቸው ድረስ በቤተክርስትያንና በኅብረተሰብ እጅግ ተወዳጅና ባለመልካም ባህሪ ካህን ነበሩ::
እኝህ ታታሪና አመለ-ወርቅ ካህንን ላጣችው ቤተ ክርስትያን፣ ለቤተሰብ፣ ጓደኞችና ኅብረተሰብ ፅናት እየተመኘን ለነፍሰ ኄር ኣባ ጥዑም ተስፋይ እግዚአብሔር በዘለዓለማዊ መንግስቱ እንድያሳርፍልን እንጸልያለን::
ካቶሊክ ቤተ ጳጳስ ዘመንበረ አዲግራት
02. 06.2006 ዓ.ም.
ከጥቂት ጭማሪዎች ጋር ምንጭ፡ http://irrob.org/news/abba-teum-tesfays-biography/